Tikur Sew, ጥቁር ሰውዘነበ በቀለ

ምንም እንኳ የባህል ሙዚቃ በዋናነት መለኪያው ሀገራዊ የግንዛቤ ስልት ቢሆንም አንድን ሙዚቃ ለመገምገም በርካታ መለኪያዎችን ማስቀመጥ የሚያስፈልገው መሆኑ ግን ሀቅ ነው። በዚህም ምክንያት የቴዲን ሙዚቃ ስንገመግም መለኪያዎቻችንን በግልፅ ማስቀመጥ ግዴታ ነው። እንዲያው በደፈናው ደስ ይለኛል፣ አይለኝም፣ ብሎ መደምደም ይቻል ይሆናል፣ ነገር ግን እንደመገምገሚያ መሳሪያ ተደርጎ ሊወሰድና ወደ ትክክለኛም ግንዛቤ ሊመራ ይችላል ብሎ መገመት ስህተት ነው።

 

በአውሮጳውያኑ ሙዚቃ አገማገም ስልት መሰረትነት ላይ ስንነሳ በመለኪያነት የምናስቀምጣቸው ነገሮች አሉ ከነዚህም መሃል የሚከተሉት ይገኛሉ። 

 

  1. ባህላዊ የግምገማ ዘዴ፡ ይህ አይነቱ ግምገማ በተናጠል ዜማ ይዘት ላይ ተመስርቶ የሚፈርጁት ነው። በሞዳል ሴሰትሙ ንብረት ላይ እንጂ! በሲስተሙ ጠባዮች ላይ የሚደረግ ግምገማ አይሆንም።
  2. ሼንኬሪያን የግምገማ ዘዴ፡ በኖታዎቹ ዝምድና ላይ የሚያተኩር ነው።
  3. ፎርማል የሆነ የግምገማ ዘዴ፣ የሙዚቃውን ክፍሎች ለያይቶ መመልከት ነው
  4. አንፃራዊ የግምገማ ቴክኒክ፣ በተለያዩ ቶኖች ውስጥ /ፍሪኮንሲዉን/ ማነፃፀር፣ ነው። ወዘተ ...

 

የቴዲ አፍሮን "ጥቁር ሰው" ሙዚቃ ስንመለከተው ከነዚህ መለኪያችው አንደኛውን ብቻ ወስደን ይኸ ነው ማለት ያስቸግራል። ነገር ግን ሁለንተናዊ ገፅታውን ለመመልከት ዜማውን፣ ሪትሙን፣ ግጥሙንና፣ አቀራረቡን ባጠቃላይ መልኩ ተመልክተን የምንፈርጀው ይሆናል።

 

በኢትዮጵያ ሙዚቃ ውስጥ ቅኔ ስር የሰደደ አሰራር ስልት አለው። አፈታቱም እንደ አድማጩ አተረጓጎም ችሎታ የሚለካ ነው። ሲመሰገን ተሰደብኩ ብሎ የሚገነፍል፣ ሲሰደብ ተመሰገንኩ ብሎ የሚዝናና ሊኖር የመቻሉ ምክንያት የቅኔው ወርቃማ ክፍል በሰማዊ ሸማ ተጀቧቡኖ መቅረቡን ያመለክታል። ክንብንቡን ገልጦ ለማየት ሁለገብ የሆነ የግምገማ ዘዴ ያስፈልገዋል።

 

አንዳንዱ የባህል ሙዚቃ በግጥሙ ላይ ሲያተኩር ሌላው ደግሞ በሪትሙና በአለባበሱ ላይ መሰረት ያደርጋል። ይህ ማለት የራስ ጎፈር አድርጎ የሚታይ ሰው፣ ትዝታን ሊያንጎራጉር ነው ብሎ መጠበቅ የሚቻል አይሆንም። እስክስታ መውረድም የዜማውን ባህርይ ሊከተል ስለማይችል ትርጓሜው ስህተት ይሆናል። ትክክለኛው ግን ሊያቅራራ እንደሆነ መጠበቅ ነው። በዚህ ምክንያት ጨዋታዎችን ከባህላዊው አለባበስ ባህርይ መረዳት ይቻላል ማለት ነው።

 

በአማርኛውና በትግሪኛው ባህላዊ ሙዚቃ ውስጥ ይህ አይነቱ አሰራር የተለመደ ይሆናል። ይኸው አለባበስ በኦሮምኛ ባህላዊ ሙዚቃ ውስጥ /ረገዳ/ን የሚከለክል አይሆንም። ወይም በወላይትኛና በሌሎች ቋንቋ ተናጋሪዎች ሙዚቃዊ ባህል ውስጥ /ጭፈራን/ ላይከለከል ይችላል። ስለዚህም ባህላዊ መሰረትነት ያላቸውን ሙዚቃዎች በተናጠል መፈረጅ ያስፈልጋል። ነገር ግን እንደ ቴዲ ሙዚቃ ያለውን ዘመናዊ ዜማ መመልከት የሚቻለው በሁለገብ የዜማ መስፈሪያ ስልት ውስጥ ነው። 

 

ሙዚቃዊ ድርሰቱ ዘመናዊ ስልትን የሚከተልና ባህላዊ ልባስ ያለው መሆኑን እናያለን። ባውራጁና በተቀባዩ መካከል ያለው /ኢሚቴሽናል ዲስፖኒ/ ጎልቶ መውጣት ያለበትን ቃል በመደጋገም መጫወትና /ፕሮግሬሲቭ/ ማለትም /ሶሎይስቱ/ ከዋናው ዜማ ውጭ በመቀያየር የሚጫወተው ነገር እንዳለ ይስተዋላል።

 

በአጠቃላይ ካንድ ቋንቋ በላይ የሆነ ዜማ ማቅረብ እየተለመደ የመጣ ቢሆንም፣ የቴዎድሮስ ካሳሁንን /ጥቁር ሰው/ ሙዚቃ ከብዙ አኳያ መመልከት ይቻላል። በዜማው በኩል የአማራውን /የሙሾ/ ባህል ዜማ የወሰደ መሆኑ /ሆ! ሆ - ሆሆ/ እያለ የሚቀበለው /ኮረስ/ ያሳያል። በዚህም የመልዕክቱን አሳዛኝነት ለማብሰር የተደረገ ይመስላል። ከዚህም ሌላ በሴት ድምፅ የሚቀርበው /ኢቲሬቲቭ/ የሆነ የዜማ አጀብ፣ የደቡብን ካኖኒክ ፎርም ሙዚቃ አሰራር ቴክኒክ ይከተላል። ከመሳሪያው ጋር የሚያደርገውም /ሞቴት/ መሰል ስታይል፣ ከሚታጀብበት የደቡብ  ሪትም ጋር ተደባልቆ /ሲንክሮናይዝድ/ በሆነ መልኩ ሲቀርብ የዜማው ባህርይ ኢትዮጵያዊ እንደሆነ ተንፀባርቋል።

 

በግጥሙ በኩል አውራጁ የመረጣቸው ባህርያት አሉ። እነዚህም ለምሳሌ የባልቻ አባ ነፍሶንና የፊት አውራሪ ሀብተጊዮርጊስ ዲነግዴን ተሳትፎ ቴዲ አፍሮ በተለይ አጉልቶ ለማሳየት የሞከረበት ምክንያት፣ አንድ ወጥ አመራር ብቻ የአድዋን ጦርነት ከድል እንዳላደረሰው ለማሳየት ይመስላል። በአመራሩ ውስጥ የነበረው ሁለገብ ተሳትፎ ኢትዮጵያዊነት የሚንፀባረቅበት በመሆኑም ጭምር ነው እንጂ! አንደኛውን ከአንደኛው ለማስበለጥ፤ አልያም የአንዱን ገድል ረስቶ የሌላውን ገንብቶ ለማሳየት ያቀደው አይመስለኝም።

 

የዜማ ግጥሞች ብዙ ጊዜ ዜማውን መጥነው መሄድ ስላለባቸው በራሳቸው አቀራረብ ላይ የተሟላ ሀሳብ ላይዙ ይችላሉ። ቴዲን ከሁሉም ዘፋኞች በላይ ከፍ አድርጎ የሚያሳየው ነገር ቢኖር አንደኛ እራሱ የድርሰት ሰው መሆኑ ሲሆን፣ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ወጣቱ አርቲስት የሙዚቃውን ባህርያት ጠንቅቆ የሚያውቅ መሆኑ ነው። በአጨዋወት ስልቱ ውስጥ አስገብቶ የግጥም፣ የዜማ፣ ውህደትን በጥንቃቄ የመያዝ ችሎታ ያለው በመሆኑ ነው። በዚህ በኩል አርቲስቱ ብቃት ያለው ዘመናዊ ሙዚቀኛ እንደሆነ አስመስክሯል። ቴዲ አፍሮ በዘመናችን የተገኘ እዚህ ቀረህ የማይባል ታዳጊ አርቲስት ነው። የመድረክ ቁጥጥርን፣ የድምፅ ገደብ መረዳትን፣ የግጥም /ሲሌቢክ/ እና ፒች/ ጥምረትንና ውበትን፣ የባህል ቅርስ አጠቃቀምን፣ ጠንቅቆ ያወቀ ወጣት በመሆኑ፣ በእርግጥም ሊበረታታ፣ ሊደነቅና ሊከበር የሚገባው ወጣት አርቲስት ነው እላለሁ።

ቸር ይግጠመን!

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ