ወለላዬ ከስዊድን ( This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. )

(ግጥሙን በፒ.ዲ.ኤፍ. አስነብበኝ!)

ተሹመሃል አሉ ሰማን …

እንደው ሥልጣንህ ምን ይሆን?

ስምህ ተለውጦ ተሾምክ?

ወይስ በዛው ላይ ደረብክ?

ከለወጡህስ ማን አሉህ?

በምንስ አጥበው አለቀለቁህ?

ለምንስ አንተን ፈለጉ?

እንዳይቀር ይሆን የሥልጣን ወጉ? 

 

ቃለ መላህንም ሰማን፣

ወሬ አይደበቅ ነገሩን

የሳቸውን ራዕይ ላሟሽ

ኢትዮጵያዊነትን ላኮላሽ

ዘለአለማዊ ሕይወታቸውን መስክሬ

ኃይልና ሥልጣናቸውን አክብሬ

በሳቸው ድርጅት እጠለላለሁ

እንደጻፉልኝ አነባለሁ

እንዳሳደሩኝ ውዬ አድራለሁ

ብለህ ነው አሉ የሾሙህ

ይሄ ነው አሉ መኃላህ

አጀብ! ጉድህን ሰማንልህ

 

ይሄን ታዲያ ምን ብዬ ለእናታችን ላውራት?

እንዴት ብዬ ልንገራት?

በዕድሜዋ የመጨረሻ ዘመን፣

አንተን በመውለዷ እንዴት ትዘን፣

እንዴትስ ይሄን ጉድ ተሸክማ፣

መቃብር ትውረድ እማማ

እባክህን ስሟን ብቻ ተውላት፣

የሱ እናት ናት አታስብላት

እንኳን እሷ የሞተው አባባ፣

ባንተ ተግባር ስሙ በመቃብር ቢጠነባ፣

ዛሬ ነው የሞተው ተብሎ ፈሰሰለት ትኩስ ዕንባ

አዎን! ዛሬ ነው የሞተው፣

አጥንቱን ሳይቀር አስወቀስከው።

 

 

እኔም ወንድሙ ነው መባሉ፣

እያቅለሸለሸኝ ነው ቃሉ፣

እንዳተው ስደበቅ፣

እንዳተው ሰው ስርቅ

ኮርቶ ነው ይሄ ብጣሻም ተባልኩ፣

በምኔ ነው የምኮራ፣

አሳፍሮኝ እንጂ ባንተ ስም ስጠራ

እናም ሁሉም ይቅርብኝ፣

ወንድምነትህን ተወኝ፣

ስጋነትህን ፋቅልኝ

 

 

ያንተን ስም ማንሳት የጠሉት፣

እናንተ እኮ እያሉኝ በድፍረት

በጦር ዓይናቸው አጥንቴን ሳይቀር ወጉት

ከፊሉም ትቶኛል አኩርፎ፣

ያንተ ወንድም መሆኔን ተጠይፎ

አንዳንዱ ደግሞ አላጋጭ፣

ገና ሲያገኘኝ በግላጭ፣

እንደሰላምታ ትከሻዬን ገጭቶኝ፣

ወይም የመንከስ ያህል ስሞኝ፣

እንዴት ነው ቤት ቀየርክ?

መኪና ገዛህ ለወጥክ?

ልጆችህን ውጭ ላክ?

ብሎ በአበሻ ወግ ሽሙጡ፣

ይለመጥጠኛል በቅጡ

ሌላውማ አያድርስ ከቶ፣

አንተን ያገኘ ይመስል ደሙ ፈልቶ፣

ሊዘለዝለኝ ያምረዋል፣

ሊከታትፈኝ ይዳዳዋል

ምነው! አንተን አግኝቶ በገላገለን፣

የስምህ ክርፋት ከሚጠነባን፣

ሞትህ ነበር የሚሻለን።

ወይም ያኔ ድሮ ድሮ፣

የያዘህ በሽታ አሳርሮ፣

ምናለበት በገላገለህ በገላገለን ኖሮ።

ከለጠፍክብኝ አጉል ስም፣

ይሻለኝ የነበር የሟች ወንድም

አሁንም ከዚህ ስምህ አውጣኝ፣

ወንድምነትህን አንሳልኝ፣

ምንህንም አንፈልግ እኔና እናቴ፣

ከስምህ ብቻ አድነን በሞቴ

እኛን እኮ ነን ባንተ ጥፋት ህዝብ የሸነቆጠን፣

ባላጠፋን የቀጣን ባልበደልን የረገመን፣

አሁንም እባክህን ለኛ ስትል፣

አጎብዳጅነትህን እንቢ በል

ደግሞስ ያንተ ሹመት ለማነው የሚሆነው ተስፋ፣

እንዲህ በሃገርና በውጪ ስምህ እየከርፋ

እናታችንን ልታይ ስትመጣ በድብቅ፣

ጎረቤቱን አፍረን ከምንሳቀቅ

ምነው የደም ጮማህ ቀርቶብን በበላን አሹቅ

 

 

እናታችን ስሟ ተከብሮ፣

ሰዉ ወዷት እንደድሮ፣

እየበላች ሌጣ ሽሮ፣

መኖሩ ነው የሚሻላት፣

ካገር ከሰው አትነጥላት፣

እባክህን ስሟን ተዋት።

ትንሹ ልጃችን እንኳን ትምህርት ቤት፣

የእከሌ ልጅ እኮ ነው እያሉት፣

ሊጫወት ሲል እየሸሹት፣

እንዳዋቂ ነገር ገብቶት፣

ፈዞ ቀርቷል ጨምቶ፣

ልጅነቱን ተቀምቶ

 

 

እናም በቁሜ ነው የገደልከኝ ወንድሜ፣

በስምህ ተቀብቼ አለስሜ

ለኔና ለቤተሰባችን፣

ስምህን አንሳልን ከላያችን

እንደቢጤአችን እንኑር፣

ደስ ብሎን እንቸገር

ወንድምነትህ ላያኮራ፣

ሹመትህ ለሐገር ላይሰራ፣

እስከስምህ ተለየን፣

አንጠጋህ አትጠጋን

እንለያይ ወንድሜ፣

ይሻለኛል ደሃ ስሜ

ለናታችንም ስሟን መልስላት፣

የዛ እናት ናት አታስብላት፣

ካገር ከሰው አትነጥላት

የሥልጣንህ ክርፋታም ፍግ

መደበቂያ መሄጃ ጥግ፣

ከሚያሳጣን እኛን ተወን፣

ከህዝብ ጋር የኖርን ነን።

 

ይሄውና ወዳጅ ዘመድ፣

ና ካላልነው ጠርተን በግድ፣

እንዳያየን ፊቱን ዞሮ፣

ያልፍ ጀመር በኛው ጓሮ

የስም ክፉ ጥፈህብን፣

እንደኮሶ ተጣብተኸን፣

አድባር ሸሸን፣ ቆሌ እራቀን፣

እባክህን ስምክን ተወን።

ያልተወለደችህ እንኳን ባለቤቴ፣

በደወለች ቁጥር ያንተ እሜቴ

ድምጿን መስማት እየፈራች፣

እያለችም እቤት የለች።

እንደዚህ ነው ያሳፈርከን፣

መግቢያ መውጫ ያሳጣኸን

 

 

እናም ወዶ ገቡ ወንድሜ፣

የጎለትከኝ አለስሜ፣

እንደጫኑህ ሰቅለው ከቆጥ

እስኪያወርዱህ በመዘርጠጥ

እኛን ቀድመህ አትግደለን፣

ካገር ጉያ አታግልለን፣

ስማችንን ብቻ ተወን።


ወለላዬ ከስዊድን (

This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. )

 

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ