የኢትዮጵያዊነት ልዩ ውበትና አንድነት እስከ ፖለቲካዊ፣ ኃይማኖታዊ፣ የመብት ጥያቄዎችና ተቃውሞዎች የተንጸባረቁበት 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ

Sports had the power "to change the world ... to inspire ... to unite people." - Nelson Mandela

ፍቅር ለይኩን

የ998ቱ በፈረንሳይ አስተናጋጅነት የተካሄደው የዓለም እግር ኳስ ዋንጫ በዓለም አቀፉ የፖለቲካ መድረክ ስፖርት ለሰላም፣ ለወንድማማችነት፣ ለአንድነት … ወዘተ ያለው አዎንታዊ ፋይዳ በግልፅ የታየበት መድረክ ሆኖ ነበር ያለፈው። በአንድ ቡድን ተደልድለው የተገናኙት በጥንታዊ ስልጣኔዋኗ እስከ አስር ሺህ ዘመን በሚመዘዝ ግዙፍ ታሪኳ፣ ታላቅ የሆነ ብሔራዊ ኩራትና ስሜት ያላት ጥንታዊቷ ፋርስ የዛሬዋ ኢራን ብሔራዊ ቡድን፣ ከአሜሪካ አቻዋ ጋር በተፋጠጡበት መድረክ፣ የትናንትነዋ ኃያል ኢራንና የዘመናችን ልዕለ ኃያል አገር አሜሪካን ያገናኘ ልዩ አጋጣሚ ሆኖ ነበር ያለፈው።

 

በእነዚህ ሁለት ባላንጣ አገሮች በአንድ ቡድን ተደልድለው የተገናኙበትን ጨዋታ/ፉክክር የአሜሪካው እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት በአጭር ቃል እንዲህ ሲሉ ነበር የገለጹት፦ “the mother of all games” በወቅቱም ስለ ሁለቱ አገራት ጨዋታ የዘገቡ ዓለም አቀፍ የመገናኛ ብዙኃን፣ የሁለቱ አገራት ፖለቲከኞች፣ ዲፕሎማቶች፣ የእግር ኳስ ባለሙያዎችና ተንታኞች ጨዋታው ከስፖርታዊ ውድድር ባለፈ ጠንከር ያለ ፖለቲካዊ አንድምታ እንዳለው ነበር ሲዘግቡ የነበሩት።

  

ይሁን እንጂ ከእግር ኳስ ፍክክሩ ባሻገር ፖለቲካዊ አንድምታው ጎልቶ በተነገረበት በዚህ የአሜሪካንና የኢራን ብሔራዊ ቡድኖች ጨዋታ፣ ሁለቱ አገሮች በስፖርቱ መድረክ ለሰላምና ለመልካም ግንኙነት ያላቸውን አዎንታዊ ፍላጎትና ስሜት የገለጹበት መልካምና ልዩ አጋጣሚ ሆኖ ነበር ያለፈው።

 

በተጨማሪም የሁለቱ አገሮች ደጋፊዎች በውድድሩ ወቅት ያሳዩት ሰላማዊነትና ጨዋነት፦ “ስፖርት ለሰላም፣ ለፍቅር፣ ለአንድነት፣ ለትብብር፣ ለወንድማማችነት …” የሚለውን የስፖርት መርህ ከፍ አድርጎ ለዓለም ሕዝብ ያሳየ ነበር። ጥቂት የማይባሉ የሁለቱ አገራት እግር ኳስ አፍቃርያንና ደጋፊዎች አንድ ጉንጫቸውን በአሜሪካን አንድ ጉንጫቸውን ደግሞ በኢራን ሰንደቀ ዓላማ ቀለማት በማስዋብ የእግር ኳስ ስፖርት በአገሮችና በሕዝቦች መካከል መቀራረብና ሰላም እንዲፈጠር የሚያስችል መድረክ መሆኑን በተግባር ለዓለም አሳይተውበታል።

 

ይህን የወቅቱን እውነታ ያስተዋለው የኢራኑ ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ የሆነው አፍሺህን የእግር ኳስ ስፖርት አገራትን በሰላምና በፍቅር መንፈስ ለማስተሳሰር ያለውን ጉልበት እንዲህ በማለት ነበር የገለጸው፦

 

There are two things that can bring this planet closer together: love and football.

 

የተባበሩት መንግሥታት ድ/ት ዋና ጸሐፊ የሆኑት ባንኪሙን በስዊዘርላንድ ጄኔቫ እ.ኤ.አ ግንቦት 11/2011 ዓ.ም ስፖርት ለሰላምና ለልማት ያለው አስተዋጽዖ በሚል ባደረጉት ንግግራቸው እንዳረጋገጡትም፤ ስፖርት በዓለም አቀፍ ደረጃ የአገሮችን ድንበር ተሻግሮ የዘር፣ የጎሳና የኃይማኖት ልዩነቶች ሳይገድበው፣ የዓለም አቀፍ ቋንቋ መሆን እንደቻለና ስፖርታዊ ውድድሮች ለሰው ልጆች ሰላም፣ አንድነትና እድገት እየተጫወቱ ያለውን ቁልፍ ሚና እንዳለው እንዲህ በማለት ነበር የገለጹት፦

 

“Sport has become a world language, a common denominator that breaks down all the walls, all the barriers. It is a worldwide industry whose practices can have a widespread impact. Most of all, it is a powerful tool for progress and development.”

 

የደቡብ አፍሪካው የነፃነት ታጋይና የሰላም አባት የሆኑት ኔልሰን ማንዴላም በዓለም አቀፉ የስፖርት መድረክ ለሰው ልጆች ነፃነትና መብት ባደረጉት ትግል፣ ስፖርታዊ ውድድሮች በረጅሙ ዘመን የእርሳቸውና ሕዝባቸው እልህ አስጨራሽ የፀረ-አፓርታይድ የነፃነት ተጋድሎአቸው ወቅት “ሰላማዊ የትግል ስልት” መሆኑን ላሳዩበት ፖለቲካዊ ብቃታቸው በተሰጣቸው ዓለም አቀፍ ሽልማት ላይ በዳረጉት ንግግራቸው ስለ ስፖርት እንዲህ ነበር ያሉት፦

 

Sports had the power to change the world ... to inspire ... to unite people.

 

ስፖርታዊ ውድድሮች የሰላም፣ የወንድማማችነትና የፍቅር መድረክ ናቸው ቢባሉም አልፎ አልፎም ቢሆን የዘረኝነት መንፈስ የሚንጸባረቅባቸው፣ የሌሎችን ክብርና ነፃነት የሚጋፋ ኃይማኖታዊ መልእክቶች፣ ፖለቲካዊ ተቃውሞችና እስከ ጠብና ግጭት የሚዘልቁ ክስተቶችን ማስተናገዳቸው አልቀረም።

 

እንግሊዝና አርጀንቲና፣ የላቲን አሜሪካኖቹ የኤልሳልቫዶርና የሆንድራስ በእግር ኳስ ጨዋታ ምክንያት የተፋጠጡበትንና ጦር የተማዘዙበትን አጋጣሚዎች ስናስብ የስፖርቱ መድረክ አልፎ አልፎም ቢሆን ከፖለቲካዊ የሆኑ አጀንዳዎች እንደማያጣው ያስገነዝበናል።

 

ለአብነትም ያህል በአንድ ወቅት ከናይጄሪያ ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን ጋር ባደረግነው ጨዋታ ናይጄሪያዎቹ “ኢትዮጵያን ራብተኞች ናችሁ” በሚል ክብርን በሚነካ መልኩ ለኢትዮጵያን ተጫዎቾችና ደጋፊዎች ዳቦ የወረወሩበት አጋጣሚ ስናስብም ስፖርት የሰላም፣ የፍቅር፣ የወንድማማችነት … ወዘተ መድረክ ነው የሚለው መርህን በጥቂቱም ቢሆን ጥያቄ ውስጥ ማስገባታችን አይቀርም።

 

በዘንድሮው በደቡብ አፍሪካ እየተካሄደ ባለው 29ኛው የአፍሪካ እግር ኳስ ዋንጫ ውድድር አዎንታዊም ሆነ አሉታዊ በሆነ መልኩ ትላንትና የነበሩ፣ ዛሬም የቀጠሉና እንዲሁም ወቅታዊ የሆኑ አንዳንድ ፖለቲካዊና ኃይማኖታዊ አጀንዳዎችን ያነገቡ ወገኖቻችንን ተቃውሞዎችንና ጥያቄዎችን አስተውለናል።

 

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን/ዋልያዎቹ ወደ ደቡብ አፍሪካ የገቡበትን አጋጣሚ ተከትሎ የታየው ፖለቲካዊ አጀንዳዎችና ተቃውሞዎች በመጠኑም ቢሆን በእኛም ሆነ በተጫዋቾቻችን መካከል አሉታዊ ስሜቶችን ፈጥሯል። በርካታ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችንም ሰላማዊ በሆነ የስፖርቱ መድረክ ለመንግሥት ያላቸውን ተቃውሞና ጥያቄዎቻቸውን በተለያየ መልክ ለመግለፅ ሲሞክሩም ታዝበናል።

 

የኢትዮጵያውያኑ ተቃውሞው በዋነኝነት ያነጣጠረው መንግሥት ስፖርታዊ ውድድሩን ለራሱ ፖለቲካዊ አጀንዳ ሊጠቀምበት አቆብቁቧል ከሚል ፍራቻ የተወለደ ነው። በአንፃሩም ደግሞ የተቃውሞው ሌላ መልክ እንደቀድሞው ሁሉ ከባንዲራ እስከ ኃይማኖት ነፃነት፣ ከሰብአዊ መብቶች ረገጣ እስከ ዲሞክራሲና ፍትሃዊ ምርጫ፣ ከሕገ-መንግሥቱ ይከበር እስከ የራስን ዕድል በራስ ከመወሰን እስከ መገንጠል የመሳሰሉት ፖለቲካዊ አጀንዳዎችና ጥያቄዎች የተነሱበትና የተራገቡበት ነበር።

 

ኢትዮጵያውያን በኦሊቨር ታምቦ ለዋልያዎቹ አቀባበል ለማድረግ
ኢትዮጵያውያን በኦሊቨር ታምቦ ለዋልያዎቹ አቀባበል ለማድረግ

 

ለአፍሪካና ለጥቁር ሕዝቦች ሁሉ የነፃነትና የልዑላዊነት ምልክት ተደርጎ በሚቆጠረው በአረንጓዴ፣ ቢጫውና ቀዩ ባንዲራችን ላይ የኢህአዴግ መንግስት በአገራችን ያሉ ብሔር ብሔረሰቦች ነፃነትና መብት መከበር እንዲሁም ሕዝቦች እርስ በርሳቸው በወንድማማችነትና በእኩልነት ላይ ለተመሰረተ ግንኙነታቸው መገለጫ ይሆናል ብሎ ባስቀመጠው የኮከብ ምስል ላይ ተቃውሞ ያላቸው ግለሰቦችና ቡድኖች ይህንን ባንዲራ ላለመያዝና ሌሎችም እንዳይዙት ለማድረግ ሲያደርጉት የነበረውን ቅስቀሳ ሰምተናል፣ ተመልክተናልም። የዚህ የባንዲራችን ጉዳይ ውዝግብም በአገር ውስጥም ሆነ ኢትዮጵያን ባሉበት በውጭ ዓለምም መፍትሔ አልባ ሆኖ እንደቀጠለ ነው።

 

በረጅሙ ዘመናት ታሪካችን በሰንደቀ ዓላማችን ላይ በአንድ ወቅት የአንበሳና የመስቀል ምልክቶችን የተካተቱበትን ጊዜያትም እናስታውሳለን። እስከ አሁንም ድረስ አንበሳ ያለበትን ባንዲራ የሚይዙ አንዳንድ ኢትዮጵያውያን፣ አፍቃሪ ኢትዮጵያ የሆኑ ራስ ተፈሪያውያን፣ አፍሪካ አሜሪካውያንና ጃማይካዎችም መኖራቸውን አሳምረን እናውቃለን።

 

በሰንደቀ ዓላማችን ዙሪያ ያለው ውዝግብ መፍትሔ አልባ ሆኖ በአንድ አገር ስም የተሰለፉ ሕዝቦች ባለ ምልክትና ምልክት አልባ ባንዲራ በሚል ሁለት ዓይነት ባንዲራዎችን ለማውለብለብ ተገደዋል ወይም ተገደናል። ብሔራዊ ቡድናችን በተጫወቱባቸው መድረኮችም ሁሉ ደጋፊዎች ይኸው ስሜታቸውን ሲያንጸባርቁ ነው ያስተዋልነው።

 

ይኸው የባንዲራችን ውዝግብም በተደጋጋሚ በዚህ በአገራችንም ሲንፀባረቅ ታዝበናል። ምንም እንኳን መንግሥት በአዋጅና በሕግ አስደግፎ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ከዚህ ባለ ኮከብ ከሆነው ባንዲራ ውጭ ማንም እንዳይጠቀም ቢወተውትም ያሰበውን ያህል አድማጭ ያገኘ አይመስልም።

 

“የኢህአዴግ ባንዲራ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን አይወክልም!” በሚል ስሜት ምልክት አልባ የሆነውን ባንዲራ አንግበው ብሔራዊ ቡድናችንን ለመቀበል በጆሐንስበርግ ኦሊቨር ታምቦ ዓለም አቀፉ አየር መንገድ የተገኙ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻን ዋልያዎቹን በቅርብ ርቀት አግኝተው ፍቅራቸውንና ስሜታቸውን ሊገልጹላቸው አልቻሉም። ይህ የሆነበት ምክንያት ደግሞ የብሔራዊ ቡድኑ መሪዎች ተጫዋቾቻችንን በሌላ በር ይዘዋቸው በመውጣታቸው መሆኑን በቅሬታ ውስጥ ሆነው ገልጸዋል።

 

ይኽም ይላሉ እነዚሁ ኢትዮጵያውያን ወገኖች፦ “መንግሥት ሰላም፣ ፍቅር፣ አንድነት፣ ወንድማማችነት … በሚሰበክበት በስፖርቱ መድረክ እንኳን ሳይቀር የተለመደ የመከፋፈል፣ የጎሰኝነትና እኩይ ፖለቲካዊ አጀንዳውን እያራመደ መሆኑን ያስረገጠበት አሳፋሪና ተራ ፖለቲካዊ ቁማር ነው።” በማለት አስተያየታቸውንና ምሬታቸውን ሲሰጡ ተሰምተዋል።

 

በኢትዮጵያ ሰንደቀ ዓላማ ላይ ገና የልተፈታ ጥያቄ ያላቸው ወገኖቻችን በአብዛኛው በስታዲዮም ውስጥ ይዘው የገቡት ምንም ምልክት የሌለበትን ባንዲራ ነበር። በአንፃሩም ደግም ባለ ኮከብ ምልክቱን ባንዲራ ሲያውለበልቡ የነበሩ በርከት ያሉ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን በስታዲየሙ ውስጥ እንደነበሩም ተመልክተናል። ይኽ እውነታም በአገር ቤትም ጭምር በተደጋጋሚ የተስተዋለና የምናስተውለው ነው።

 

በሌላ በኩል ደግሞ በስታዲም ውስጥ የኦነግ አባላት የሆኑ ሰዎችም በተለየ ባንዲራ ራሳቸውን ለመግለጽ መሞከራቸውን በቴሌቪዥን መስኮታችን ታዝበናል። በደቡብ አፍሪካ ኦነግ ናችሁ በሚል ሰበብ ከምድራችን ተፈናቅለናል የሚሉ በርካታ ኦሮሞዎች አሉ። እነዚህ ኦሮሞ ብሔር ተወላጆች “አቢሲኒያ የኦሮሚያ ቅኝ ግዢ ናት”፣ ከቅኝ ግዛት ለመውጣት የምናደርገውን ትግል መንግሥት ከሽብርተኝነት ፈርጆ እኛንና ነፃነት ፋላጊ የሆነውን ሕዝባችንን እያሰረ፣ እያንገላታና ሰብአዊ መብታቸውን እየገፈፈ ነው በሚል መንግስትን አጥበቀው ይከሳሉ፣ ይኮንናሉም።

 

እነዚሁ የተለያየ አጀንዳና ጥያቄ ያላቸው የመንግሥት ተቃዋሚዎች በዚህ በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ይኸው ፖለቲካዊ ጥያቄያቸውን ይዘው በስታዲየሙ መገኘታቸው ግርምትን አጭሯል።

 

በተመሳሳይም ደግሞ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞችም መንግሥት ከኃይማኖታችን ላይ እጁን ያንሳ በሚል Free our Leaders የሚል ቲ-ሸርት ለብሰውና በአበሽ አንጠመቅም፣ መሪዎቻችን ይፈቱ፣ ገዳዮች ለፍርድ ይቅረቡ … ወዘተ የመሳሰሉትን መፈክሮች አንግበው በስታዲየም ውስጥ መታደማቸውንም በአግራሞት ውስጥ ሆነን ታዝበናል።

 

የአገር ቤቱ ፖለቲካዊ ትኩሳትም ወደ ውጭ ዘልቆ በስፖርት መድረኩም እንኳን ሳይቀር ፖለቲካዊና ኃይማኖታዊ አጀንዳዎቻችን መንጸባረቃቸው የነገ ዕጣ ፈንታችን ምን ሊሆን ይችል ይሆን የሚል ጥያቄን እንዳነሳና በአንፃሩም ደግሞ የኢትዮያዊነት የአንድነት መንፈስና ውብ የሆነ አብሮነታችን የተጋረጠበትን አደጋ በስጋት ውስጥ ሆኜ እንዳስብ አስገድዶኛል።

 

በዘንድሮው ከሰላሳ ዓመታት በኋላ ተሳታፊ በሆንበት በደቡብ አፍሪካ የእግር ኳስ ዋንጫ የሆነውና የታየው ነገር ገና በመካከላችን ሰላምን፣ ፍቅርን፣ አንድነትን፣ እርቅንና መግባባትን ለማስፈን ረጅም ጉዞ እንደሚጠብቀን ያሳየ ነው ብል ብዙም ከእውነታው የራቅኹ አይመስለኝም።

 

ለዚህ ጉዞአችን መሳካትና ውጤት ደግሞ ሀገራዊ/ብሔራዊ ራእይ፣ ጠንካራና በምንም ዓይነት ሁኔታ ውስጥ ቢሆኑ የማይናወጽ ጽኑ መንፈስ ያላቸው፣ ከዘረኝነት፣ ከጥላቻና ከአድልዎ የጸዱ ኢትዮጵያውያን ማንዴላዎች፣ ጋንዲዎች፣ ሉተሮች … ወዘተ በእጅጉ እንደሚያስፈልጉን አስባለሁ።

 

በሌላ በኩል አዎንታዊ በሆነ መልኩ በዚህ በዘንድሮው በደቡብ አፍሪካው የ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ያስተዋልኳቸው በእጅጉ ደስ ያሰኙኝና ልቤን የነኩኝ አንዳንድ መልካም አጋጣሚዎችም ነበሩ። ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን በየአገራቸው ሰንደቀ ዓላማ በአንድነት ሆነው ለዋልያዎቹ ያላቸውን ድጋፍና መልካም ምኞታቸውን ለመግለፅ በስታዲየሙ ውስጥ በመገኘት ያሳዩት ፍቅርና የወንድማማችነት መንፈስ በእጅጉ ሊጠቀስና ሊመሰገን የሚገባው ነው።

 

እነዚህ በባህል፣ በታሪክ፣ በኃይማኖት፣ በቋንቋና በደም የተሳሳሩ ሕዝቦች በመንግሥቶቻቸው መካከል ያለውን የጠላትነት መንፈስ ወደጎን ትተው በስፖርቱ መድረክ ለሰላም፣ ለፍቅር፣ ለአንድነትና ለወንድማማችነት … ያላቸውን አዎንታዊ ስሜትና ፍላጎት የገለጹበት ሁኔታ በእውነት ደስ የሚያሰኝ ነው።

 

በተቃራኒው እስካሁን ድረስ እያሰገረመኝ ያለው ነገር ደግሞ በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ፦ “ከኤርትራ ጋር ለመደራደርና ሰላምን ማውረድ አስመራም ድረስ ቢሆን እንኳን እሄዳለሁ።” ባሉ ማግስት፣ “በዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ሁለቱ አገራት የሚያድረጉትን ጨዋታ በሌላ ሦስተኛ አገር እንጂ በአስመራ ለማድረግ ፈቃደኛ አይደለንም” የሚለውን መረር ያለውን መግለጫ ሳስብ ደግሞ የመንግሥታችን የሰላም አቋም ግራ ያጋባኛል።

 

እናም “ሰፖርት ለሰላም፣ ለፍቅር፣ ለወንድማማችነትና ለአንድነት …” የሚለው መርህ በመንግሥት ባለስልጣኖቻችንና በስፖርቱ ኃላፊዎች ዘንድ ትርጓሜው ምን እንደሆነ በግልፅ ያስረዱን ዘንድ እንድንጠይቃቸው እንደዳለን፤ ሊያውም ደግመን ደጋግመን ነዋ!

 

የኢትዮጵያን ቡድን በጋር ለመደገፍ የወጡ ኤርትራውያንና ኢትዮጵያውያን እህትማማቾች
የኢትዮጵያን ቡድን በጋር ለመደገፍ የወጡ ኤርትራውያንና ኢትዮጵያውያን እህትማማቾች

በተመሳሳይም ከሁለት አስርተ ዓመታት የእርስ በርስ ጦርነት፣ መፈራረስና ኹከት በኋላ ዳግም እንደ አገር በሁለት እግሯ ለመቆም ጉልበቴ በርታ በርታ እያለች ያለችው የቅርብ ጎረቤታችን የሆኑት ሶማሊያኑም ልክ እንደ ኤርትራውያኑ ሁሉ የዋልያዎቹን ማልያ ለስብሰው ብሔራዊ ቡድናችንን ለመደገፍ ከኢትዮጵያን ወገኖቻችን ጋር የተገኙበት አጋጣሚ ይኸው ስፖርቱ በዓለም አቀፍ መድረክ በአገራትና በሕዝቦች መካከል ሰላምን፣ አንድነትንና፣ ወንድማማችንትን በማሰፈን ረገድ ያለውን አዎንታዊ ተጽእኖ እንድንታዘብ ያደረገ ልዩና ተወዳጅ አጋጣሚ ነበር።

 

አገራችን ኢትዮጵያ በቀደመ ታሪኳ በስፖርቱ መድረክ አፍሪካውያን ነፃነታቸውን እንደዲቀዳጁና ከጭቆና ቀንበር እንዲላቀቁ ድምፅዋን ከፍ አድርጋ ያሰማች አገር ናት። በዓለም አቀፉ መድረክም ስፖርት ከዘረኝነት፣ ከአድሎና ከጭቆና የፀዳ የሰላምና የወንድማማችነት መድረክ እንዲሆንም በብርቱ የታገለች አገር መሆኗን የታሪክ መዛግብት በሰፊው ይጠቁማሉ።

 

እንደእነ ይድነቃቸው ተሰማ ያሉ የአፍሪካ የእግር ኳስ አባትና መስራች፤ ስፖርቱ የሰላም፣ የአንድነት፣ የወንድማማችነት፣ የትብብር … ወዘተ መድረክ እንዲሆን በብርቱ የሰሩና የታገሉ መሆናቸውንም ማስታወስ ይኖርብናል።

 

በተደጋጋሚ በአፓርታይድ ዘረኝነት መዳፍ ስር ስትማቅቅ ለነበረችው ደቡብ አፍሪካ ነፃ መውጣት ከፖለቲካው መድረክ ባሻገር በስፖርቱ መድረክ ድምፅዋን ያሰማችውና በብርቱ የተሟገተቸው አገራችን ኢትዮጵያ፣ በዋልያዎቹ አማካኝነት ለአፍሪካ አገሮች ሁሉ ነፃነት ምልክት የሆነው አረንጓዴው፣ ቢጫና ቀዩ ሰንደቀ ዓላማችን በደቡብ አፍሪካ ሰማይ ላይ ከፍ ብሎ መውለብለቡ አገራችን ለአፍሪካ አገሮች ነፃነት ያደረገችውን ታላቅ አስተዋጽኦ ዳግም እንድናስታውስ የሚያደርገን ነው።

 

ከግማሽ ምዕተ ዓመታት በፊት እምቢ ለነፃነቴ፣ እምቢኝ ለሕዝቤ፣ እምቢኝ ለእናት ምድሬ መከራና ግፍ፣ እምቢኝ ለዘረኝነትና ለጭቆና. . . በማለት እረ ጥራኝ ዱሩ፣ እረ ጥራኝ ጫካው በማለት በቀደሙ አባቶቻችን የኢትዮጵያዊነት ወኔና የአይደፈሬነት ጽኑ መንፈስ መንፈሳቸው የሸፈተባቸው፣ የአፍሪካ ብርቅዬ ልጅና ነፃነት አርበኛው ማንዴላ የከተሙባት ኢትዮጵያችን፤ ዛሬ ደግሞ በዋልያዎቹ አማካኝነት፣ በማንዴላና በሕዝቦቻቸው የአይበገሬነት መንፈስና ትግል ፍሬ ነፃነቷን ተጎናጽፋ በዓለም መድረክ Rainbow Nation በሚል ቅፅልን ባገኘችው በደቡብ አፍሪካ መገኘታቸው ልዩ የሆነ ታሪካዊ አጋጣሚ ነው ለማለት እደፍራለኹ።

 

በዚህ ቡድናችን ከሰላሳ ዓመታት ልፋት፣ ድካም፣ ቁጭትና እልህ … በኋላ ደቡብ አፍሪካ ባዘጋጀችው የ29ኛው አፍሪካ ዋንጫ ተሳታፊ ለመሆን ልዩና ታሪካዊ የሆነ ዕድልን ላገኘው ብሔራዊ ቡድናችን፣ በአፍሪካም ሆነ በዓለም አቀፉ መድረክ የበለጠ ብቃቱን የሚያሳይበት መልካም ዕድል እንዲገጥመው እመኛለኹ።

 

የስፖርቱ መርህ የሆነው “ሰላም፣ ፍቅር፣ ወንድማማችነት፣ አንድነት …” ጽንፈኝነትና ጥላቻ በሚያይልበት በአገራችን የፖለቲካ ሜዳ ላይ የጥላቻ፣ የመወጋገዝና የጠላትነት አረምና ጭንገፋ ከስሩ ተንቅሎ የፍቅር፣ የሰላም፣ የአንድነትና የወንድማማችነት … ፍሬ አፍርቶ የምናይበት እውነተኛ የትንሳኤና የህዳሴ ዘመንን ለእናት ምድራችን ኢትዮጵያ ይሁን! አሜን! ይሁን!!

ሰላም! ሻሎም!

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ