"የማምነው ነገር፣ የሀገሪቷ ችግር ሲፈታ፤ እስክንድርም አብሮ እንደሚፈታ ነው"

"የስደት ህይወት ሁሉንም ነገር ከዜሮ ያስጀምርሃል"

"የእስክንድር ፅናት እና ብርታት ከፈጣሪ የተሰጠው ፀጋ አድርጌ እመለከተዋለሁ"

"በሀገራችን ጉዳይ ላይ ለመሳተፍ የግድ ፖለቲከኛ መሆን አይጠበቅብንምሰርካለም ፋሲል (ጋዜጠኛ)

Eskinder Nega, Serkalem Fasil and Nafkot Eskinder
በአንባቢያን ዘንድ ታዋቂ የነበሩት "አስኳል"፣ "ሚኒሊክ"ና "ሳተናው" ጋዜጦች አንዷ አሳታሚ ነበረች። የ97 ምርጫን ተከትሎ በተፈጠረ ግርግር ለእስር ከተዳረጉት ጋዜጠኞች እና አሳታሚዎች መካከልም አንዷ ነች - ጋዜጠኛ ሰርካለም ፋሲል። በሀገራችን የግል ፕሬስን በመጀመር ፈር ቀዳጅ የሆነው የጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ባለቤት ሰርካለም ልጃቸው ናፍቆትን የወለደችው በቃሊቲ እስር ቤት መሆኑ ይታወቃል። 

ከእስር ከተለቀቁም በኋላ እስክንድር የጋዜጣ ፍቃድ ቢከለከልም ሀገሬን ጥዬ አልመሄድም በሚል አቋሙ በመጽናቱ ጽሑፎቹን በተለያዩ በውጭ ሀገር ባሉ ድረ-ገጾች ላይ ማቅረብ ቀጠለ። በሀገር ውስጥ የግል ጋዜጦች ላይም ቃለ-ምልልስ በማድረግ የግል ሀሳቡን በድፍረት በማቅረብ ላይ ሳለ ነበር በሽብርተኝነት ወንጀል ተጠርጥሮ መስከረም 03 ቀን 2004 ዓ.ም ለእስር የተዳረገው። በፍርድ ሂደትም 18 ዓመት ጽኑ እስራት ተፈረደበት። በዚህ ሁሉ ውጣ ውረድ ውስጥ ባለቤቱ ሰርካለም ከጎኑ ነበረች።

ሰርካለም በአሁኑ ወቅት በስደት አሜሪካ ሀገር ትገኛለች። የዚህ ሳምንት የ"ፍቱን" እንግዳ የሆነችው እ.አ.አ በ2007 ዓ.ም ከዓለምአቀፍ የሴቶች ሚዲያ ፋውንዴሽን “Courage in Journalism Award” የሚል ሽልማት ካገኘች በኋላ የሽልማት ገንዘቡን ለአምነስቲ ኢንተርሽናል ተቋም ድጋፍ እንዲውል ያደረገችው ጋዜጠኛ ሰርካለም ፋሲል ነች። ጋዜጠኛ ኤልያስ ገብሩ የተወሰኑ ጥያቄዎችን (ስደትን፣ እስክንድርን፣ ልጃቸው ናፍቆትን በተመለከተ) በማንሳት እንዲህ አነጋግሯታል።

በቅድሚያ ለቃለ-መልልሱ ፈቃደኛ በመሆንሽ በ"ፍቱን" መጽሔት ስም እናመሰግናለን።

እኔም ለቃለ-ምልልሱ ዕድሉን ስለሰጣችሁኝ በአንባቢዎቻችሁ እና በራሴ ሥም አመሰግናለሁ።

ሰርካለም፣ ከሀገር ከወጣሽ ምን ያህል ጊዜ ሆነሽ? ለምን እንደወጣሽም በአጭሩ ንገሪን?

ከሀገር ከወጣሁ አንድ ዓመት ከስድስት ወር አካባቢ ሆኖኛል። ከሀገር የወጣሁትም በግሌ ወስኜ ሳይሆን፣ ከእስክንድር ጋር ለረጅም ጊዜ ተነጋግረንበት፣ በጋራ በደረስነው ውሳኔ መሰረት ከሀገር ልወጣ ችያለሁ ምክንያቱ ደግሞ፣ ማንም እንደሚያውቀው ልጃችን ናፍቆት የተወለደው እኔ እስር ውስጥ ሆኜ ነው። በ1998 ዓ.ም የአንድ ወር ተኩል ነብሰ ጡር ሆኜ ነበር የታሰርኩት። የወለድኩትን ልጅ ማቀፍም ሆነ ማጥባት ሳልችል ነው ከልጄ ጋር የተለያየሁት። ከእስር ስንፈታ፣ ልጃችን አንድ ዓመት ሊሆነው የአንድ ወር ዕድሜ ሲቀረው ነበር ዳግም የተገናኘነው። በአጠቃላይ የልጃችን ታሪክ ከእስር እና ከመከራ ጋር የተያያዘ ነው። በአሁኑ ሰዓት ካለአንዳች ወንጀል፣ በሀሰት ክስ እስክንድር በግፍ 18 ዓመት ተፈርዶበት ቃሊቲ ይገኛል። ትላንት ቃሊቲ የተወለደው ናፍቆት ዛሬ ነብስ አውቆ፣ የልጅነት መቦረቂያ ጊዜውን አባቱ ጋር እየተመላለሰ ማሳለፍ ዕጣ ፈንታው ሆኖ ነበር። እስክንድርም ከእስሩ በላይ የልጁ መንከራተትና ስቃይ በየዕለቱ እረፍት እንደነሳው በተደጋጋሚ ይገልጽልኝ ነበር። ከዚህም ባሻገር "ይህ ህፃን ጥላቻ ይዞ ማደግ የለበትም፣ ቂም ይዞ ማደግ የለበትም" በሚል መነሻ ናፍቆትን ይዤ ከሀገር ለመውጣት ተገድጃለሁ።

የስደት ሕይወትን እንዴት አገኘሽው?

የስደትን ህይወት እንዲህ በቀላሉ መግለጽ እቸገራለሁ። የስደት ህይወት ሁሉንም ነገር ከዜሮ ያስጀምርሃል። የእውነት ሀገርህ የሚናፍቅህ፣ የእውነት መንደርህ የሚናፍቀው በስደት ዓለም ውስጥ ነው፤ በተለይ እንደእኔ በማኅበራዊ ህይወት ትስስር ቁርኝት ላደገ ሰው።

አሜሪካ በርህን ዘግተህ ጎረቤት አታውቅ፣ ጎረቤትህ አያውቅህ፣ መንገድ ላይ ረጅም መንገድ ብቻህን ብትሄድ አንድም ሰው ላታይ በምትችልበት ሀገር፣ ራስን ከዚያ ጋር ማላመዱ ትንሽ ያስቸግራል። ሀገርህ ላይ ያለው ማኅበራዊ ህይወት ቢናፍቅህም፣ በሌላ ጎኑ ያለው ነፃነት ደግሞ እጅግ ያሥገርማል። የሰውን መብት እስካልነካህ፣ ያሻህን ብትሆን ቀና ብሎ የሚመለከትህ እና የሚያስፈራራህ አንዳችም ሀይል የለም። "ስጋት ውስጥ ይጥለኛል" ብለህ የምትጠነቀቀው ወይም የምታስበው አይኖርም። አሜሪካ የሁሉም ነች። ሁሉም እኩል ይስተናገድበታል። ሁሉም እኩል መብት አለው። ...ይህ ግን የሥደትን ህይወት ጣፋጭ አያደርገውም። ...ከነምናምኗ ሀገርን የመሰለ ምንም ነገር የለም።

ባለቤትሽ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ በሽብርተኝነት ወንጀል 18 ዓመት ተፈርዶበት በቃሊቲ እስር ቤት ይገኛል። አንቺም ከማዕከላዊ እስከ ቃሊቲ በነበረው እስሩ በጥየቃ አብረሽው ነበርሽ። አሁን ከልጃችሁ ናፍቆት ጋር በአሜሪካ ቨርጂኒያ ትገኛላችሁ። ባለቤትን ከጎን አጥቶ ሕይወትን መኖር እና ልጅን ለብቻ ማሳደግ እጅግ ከባድ መሆኑ ይታወቃል። እስኪ በዚህ ጉዳይ ላይ ያለሽን ስሜት አጋሪን?

እስክንድር "አሸባሪ" የሚል የሀሰት ታርጋ ተለጥፎበት ከታሰረ አራት ዓመት ሊሞላው ትንሽ ወራቶች ይቀሩታል። እስክንድር ሀገሩን እና ወገኑን የሚወድ ኢትዮጵያዊ እንጂ፣ ተሸባሪዎቹ እንደሚገልጹት "አሸባሪ" ወይም ህዝብና ሀገርን የሚጎዳ አንዳችም ነገር አድርጎ እንደማያውቅ የኢትዮጵያ ህዝብ ብቻ ሳይሆን፣ እነጆን ኬሪ በአደባባይ የመሰከሩለት ሀቅ ነው። የኢህአዴግ መንግሥት በግፍ፣ ማዕከላዊ ውስጥ (ለጊዜው ስማቸው ይቆየን) በሃላፊዎች ደረጃ ንፅህናው እየተነገረው ግን "ከአቅማችን በላይ ነው"፣ "ይታሰር ተብሏል፣ ትዕዛዝ ነው" እየተባለ የታሰረ የግፍ እሥረኛ ነው። እስክንድር ላመነበት ነገር የሚያስከፍለውን ሁሉ ለመቀበል የተዘጋጀ ጠንካራ ሰው በመሆኑ፣ እኔም ለብቻዬ ልጃችንን ለማሳደግ በብዙ ማይልሶች ርቀት ላይ ብገኝም፣ ከሁለታችንም በኩል ጥንካሬ ብቻ እንደሚጠበቅብን አምናለሁ። በተለይ የእኛ ጥንካሬ፣ ለእስክንድር ሞራል እንደሚሆነው ስለማውቅ ልጅን ለብቻ ማሳደጉንም ሆነ ተለያይቶ በመኖሩ ጊዜያዊ አድርጌ ነው የምቆጥረው። ደግሞም እግዚያብሄር ይችላል!

 በስደት ዓለም ሆናችሁ፣ ሰዎች ስለእስክንድር እና ስለእናንተ ያላቸው ያላቸው ቦታ …

… ከእኔ ልጀምር፣ "በእጅ የያዙት ወርቅ እንደመዳብ ነው" ይላል የሀገሬ ሰው። እስክንድር በውጪ ዓለም በዚህ ደረጃ አድናቂ እና ተከታይ እንዳለው በጭራሽ አላውቅም። በተጓዝንበት ሥፍራ ሁሉ፣ ለእስክንድር ያላቸውን ክብር የሚገልጹ ሥደተኛ ወገኖቼ፣ ለእኔ እና ለናፍቆት የተለየ እንክብካቤና ፍቅር እያደረጉልን ይገኛሉ። ሁልጊዜ አዲስ ነው የምንሆንባቸው።

እስክንድር በእስር ላይም ሆኖ፣ መንፈሰ ጠንካራነቱ ወደር አይገኝለትም። ጠያቂ ሊያበረታታው ሄዶ ጠያቂውን አበረታቶ የሚመልስ ኢትዮጵያዊ ጋዜጠኛ ነው። ስለእስክንድር የዓላማ ጽናት፣ ውስጣዊ ጥንካሬና ብርታት እሱን ለምታውቂው አንጻር ይህ ብትታቱ እነና ጽናቱ ከምን የመነጨ ነው?

የእስክንድር ፅናትና ብርታት ከምን የመነጨ እንደሆነ ለመግለፅ፣ ለመናገር ከቃላት በላይ ነው። በአጭሩ ማለት የምችለው፣ ከላይ (ከፈጣሪ) የተሰጠው ፀጋ አድርጌ ነው የምመለከተው። ምክንያቱም የሰው ልጅ የሆነ ቦታ ላይ ሲደክመው ወይም ተስፋ ሊቆርጥ ይችላል። እስክንድር ግን ብዙ መከራና ግፍ፣ እንግልት፣ በየጊዜው ቢደርስበትም፣ ለአንዲትም ቀን "አሁንስ ደከመኝ" የሚል ነገር አስቦ አያውቅም። አካላዊ ስጋው ቢጎዳም መንፈሱ ግን ሁልጊዜ አዲስ፣ ሁልጊዜ ጠንካራ፣ ከራሱ አልፎ ሌላውን የሚያበረታታ ምርጥ የኢትዮጵያ ልጅ ነው። የእሱ መከራ መቀበል ከቆመለት ዓላማ ትንሽም እንደማያነቃንቀው በተግባር ያሳየ የዘመኑ ጀግና ነው። ሞራሉን ለመግደል በሀሰት ተወንጅሎ 18 ዓመት ቢፈረድበትም፣ "ለዴሞክራሲ መከፈል ያለበት ዋጋ ነው" ብሎ ውስጡ ፀፀት እንደሌለበት አውቃለሁ። ውስጡ ትልቅ ሰላም እንዳለውም አውቃለሁ። ላመነበት ነገር የሚከፍለው ዋጋ ጥንካሬ እንጂ፣ ቁጭትን እንደማይፈጥርበት አውቃለሁ። ከምንም በላይ በሀሰት የተፈረደበት በመሆኑ፣ ለአሳሪዎቹን እንጂ የእሱ ጭንቅላት ነጻ በመሆኑ የጥንካሬው ምንጭም ሊሆን ይችላል - የሚፀፀትበትን ነገር ባለመፈፀሙ።

በባለሽበት ስቴት፣ በቅርብሽ ጋዜጠኛ ሲሳይ አጌና፣ ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ከልጇ ሃሌ ጋር አሉ። በ1997 ዓ.ም ምርጫን ተከትሎ በተፈጠረው ችግር፣ ከሁለቱም ጋር በቃሊቲ አብራችሁ ታስራችሁ ነበር። አሁን ደግሞ በስደት ዓለም አብራችሁ ትገኛላችሁ። አጋጣሚውን እንዴት ታይዋለሽ?

እንዳጋጣሚ ሆኖ ጋዜጠኛ ሲሳይ አጌና፣ ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ፣ ንግሥት ገብረህይወት (የቅንጅት ማዕከላዊ ኮሚቴ) ... አሁን ደግሞ የቀድሞው የመንግሥት ጉዳዮች ኮሙኑኬሽን ሚኒስትር ደኤታ የነበሩት አቶ ኤርምያስ ለገሰ በአንድ አካባቢ እንገኛለን። ይህ ደግሞ፣ ቅርበታችንን ከጓደኝነት አልፎ ቤተሰብ እስከመሆን አድርሶናል። አንዳችን ሌላኛችን ቤት ለመድረስ ከአምስት ደቂቃ በላይ አይጠበቅብንም። በስደት ሀገር እንደዚህ ከምታውቀው እና ከምትግባባው ሰው ጋር አንድ አካባቢ መኖር፣ ውስጥህ ያለውን ብቸኝነት በትልቁ የሚቀርፍ ነው። በአጋጣሚ በአንድ አካባቢ መገኘታችን ለእኔ ትልቅ ደስታ ሰጥቶኛል።

በማኅበራዊ ድረ-ገጽ ላይ በንቁ በመሳተፍ እመለከትሻለሁ። ብዙ ጊዜ መረር ያሉ የቁጭት፣ የሀዘንና ልብን የሚነኩ ጽሑፎችን ትጽፊያለሽ። የጠቀስኳቸውን ስሜቶች ምን ፈጠራቸው?

በማኅበራዊ ድረ-ገፅ ላይ የሚጠበቅብኝን ወይም በምፈልገው መጠን እየተንቀሳቀስኩ እንዳልሆነ ይታወቀኛል። የዚህም ምክንያቱ፣ ልጄን በብቸኝነት ለማሳደግ የምሮጠው የህይወት ሩጫ በመጠኑም ቢሆን ገድቦኛል። ልጅ ትምህርት ቤት ማመላለስ፣ የልጄን ትምህርት በአግባቡ መከታተል እንዲሁም ለመኖር የሚያስችለንን የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ መከወን በዋናነት የሚጠቀሱ ናቸው። ይህ ማለት ግን፣ ተሳትፎዬ ይቀንስ እንጂ፣ የሀገሬን ማንኛውንም ነገር ከመከታተል ወደ ኋላ ብዬ አላውቅም። ለተጠየኩት ጥያቄ መልሴ ግን፣ ባለችኝ ጊዜ የምፅፋት ነገር ምሬት እንደሚበዛባት አውቃለሁ። የዚህ ምሬት ምክንያት ደግሞ፣ ከሀገሬ መራቄ አንዱ ምክንያት ነው። ከሀገርህ ርቀህ ዜጎች ላይ የሚደርሰውን ጭቆና ማድመጥ በጣም ያማል። ምናልባትም ከመላመድ ብዛት፣ ውስጡ ሆነህ (ሀገርህ ላይ) እምብዛም አይታወቅም ራቅ ስትል ግን፣ "እንደዚህ ለምን ይሆናል?"፣ "..እስከመቼ?" የሚለው ነገርን ነገር በተደጋጋሚ እንድታስበው ያደርግሃል። በትንሹም ቢሆን የእኔም መረር ያለ ፅሁፍ ከዚህ የመነጨ ነው ብዬ አስባለሁ።

በአሜሪካ ሆነሽ፣ እስክንድርን በተመለከተ ምን እያደረግሽ ነው?

ባለሁበት ሀገር፣ እስክንድርን በተመለከተ፣ ከተለያዩ አካላት ጋር እገናኛለሁ። ስቴት ዲፓርትመንት ከጎንግረስ ማኖች (Congress man)፣ ከሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች እንዲሁም የተለያዩ ተቋማት ስለእስክንድር የማያውቁት ነገር ባይኖርም፣ በተጨማሪ እኔም ስለሚገኝበት ሁኔታ እና በእስር ቤት ውስጥ ስለሚደርስበት የሰብዓዊ መብት ጥሰት አሳውቃቸዋለሁ። የሚገርመው ነገር በየሄድኩበት ትላልቅ ተቋማት በእስክንድር ጉዳይ ላይ ከበቂ በላይ መረጃ ያላቸው መሆኑን ነው። "እስክንድር አሸባሪ ነው" የሚለውን የሀሰት ፍረጃ ጠንቅቀው እንደሚያውቁ በተደጋጋሚ በአንደበታቸው ሲገልፁ ይሰማል። ከኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን በተጨማሪ፣ በትልቅ የኃላፊነት ቦታ ላይ የሚገኙ ባለሥልጣኖች ለእስክንድር ያላቸውን ክብር መስማት የተለመደ ነው። ...ገፍተው ሌላ ነገር ማድረግ ባይችሉም እስክንድርን የሚመለከቱት በተለየ መነፅር ነው። ለጊዜው በዚህ እንቅስቃሴ ላይ እገኛለሁ። ወደፊት ግን እስክንድርን በተመለከተ ለመስራት የታሰበ ሰፊ ሥራ አለ። ጊዜው ሲደርስ የምገልጸው ይሆናል።

በግልሽ እስክንድር ከእስር ወጥቶ በቅርቡ እንገናኛለን የሚል እምነት አለሽ?

እስክንድር የጊዜ ጉዳይ እንጂ ከእስር እንደሚፈታ ጥርጣሬ የለኝም። መቼ? ለሚለው ግን እስክንድር ከዚህ በፊት እንደገለጸው ጊዜው ሊያጥርም ሊረዝምም ይችላል። ነገ ይፈታል፣ ከነገወዲያ ይፈታል ብዬ የቀን ስሌት አላስቀመጥኩም። አንድ የማምነው ነገር፣ የሀገሪቷ ችግር ሲፈታ፣ እስክንድርም አብሮ እንደሚፈታ ነው። እስከዚያው ከጨለማው ስር የሚወጣውን ብርሃን እጠብቃለሁ።

በሀገር ጉዳይ ላይ፣ ከሴት እህቶቻችን ምን ይጠበቃል?

በሀገሬ ጉዳይ ላይ ከሴት እህቶቻችን ብቻ ሳይሆን ሁሉም ሀገር ወዳድ ወገኖቻችን ንቁ ተሳትፎ በሀገራቸው ጉዳይ ላይ ማድረግ አለባቸው እላለሁ። በሀገራችን ጉዳይ ላይ ለመሳተፍ የግድ ፖለቲከኛ መሆን አይጠበቅብንም። ከዚህ ባለፈ ሩቅ ሆኜ፣ እንዲህ ቢደረግ፣ እንዲያ ቢደረግ የሚል ነገር ለማስተላለፍ የሞራል ብቃቱ የለኝም። "እንዲህ አድርጉ" ለማለት ከህዝብ ጋር ሆነህ በሀገር ላይ ተቀምጠህ እንጂ፣ በርቀት ሆኜ የምናገረው አንዳችም ነገር የለም።

በሀገር ውስጥ ለሚገኙ (ለሚያውቁሽና ለማያውቁሽ) ወገኖችሽ ያለሽ መልዕክት …

በመጨረሻ ... ለሚያውቁኝ ወገኖቼ የማስተላልፈው መልዕክት፣ እስክንድር ከታሰረ ጀምሮ በሞራልም በገንዘብም ከጎናችን ላልተለያችሁን ወገኖቼ በያላችሁበት ሰላማችሁ ይብዛ የሚል ነው

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ