ጥቅምት 15 ቀን 2005 ዓ.ም. በአዳማ ከተማ ፔቲሽን ተፈራርመው

ለምርጫ ቦርድ ጥያቄዎቻቸውን ከአቀረቡ 33ቱ ፓርቲዎች የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

ኢህአዴግ መራሹ መንግሥት በሕገ-መንግሥቱ የሰፈሩትን ለሕዝብ የተሰጡ መብቶች እንደፈለገውና እንዳመቸው በማንአለብኝነት ሲጥስና ሲደፈጥጠው ለመኖሩ ያለፉት ተግባራቱና በዚህ ሹመት ያየነው ድርጊቱ የሚመስክሩት ሐቅ ነው።

 

 

የሕገ-መንግሥቱ አንቀጽ 9 (1) “ሕገ-መንግሥቱ የአገሪቱ የበላይ ሕግ ነው ማንኛውም ሕግ ልማዳዊ አሠራር እንዲሁም የመንግሥት አካል ወይም ባለሥልጣን ውሳኔ ከዚህ ሕገ-መንግሥት ጋር የሚቃረን ከሆነ ተፈፃሚነት አይኖረውም” ይላል። በአንቀጽ 75 እና 76 ደግሞ ሀገሪቱ የሚኖራት አንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር መሆኑን ለትርጉም በማያሻማ በአማርኛም በእንግሊዝኛም በግልጽ አስፍሯል።

 

ይሁን እንጂ ፓርላማው ህዳር 20 ቀን 2005 ዓ.ም ባደረገው ስብሰባ ያገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ቀድመው ከተሾሙት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር በተጨማሪ ሁለት ባለስልጣናትን በምክትል ጠቅላይ ሚኒስርት ማእረግ ለፓርላማው አቅርበው አፀድቀዋል። ይህ ጠቅላይ ማኒስትሩ የህገ-መንግሥቱን አንቀጽ 75 በመጣስ ያቀረቡት ሲሆን ፓርላማውም የሕገ-መንግሥቱን አንቀጽ 9(1) በማገናዘብ የቀረበለትን ሹመት ሳይመረምር ማጽደቁ የፓርላማው አሰራር በሕገ-መንግሥት የተሰጠው የህግ አውጭነት ስልጣን አተገባበር በሥራ አስፈፃሚው የሚመራ መሆኑን በግልጽ የሚያሳይ ነው። ይህ ባለፉት ጊዜያት በጥድፊያና ከህገ መንግስቱ ጋር በሚፃረር መልክ የወጡት- የፀረ ሙስና፣ የመያዶች፣ የፕሬስ እና የፀረ ሽብር አዋጆች ቀጣይ አካል እንጂ አዲስ ነገር አይደለም። በተጨማሪም የአጀንዳው አቀራረብም ሆነ የሹመቱ አፀዳደቅ ከፓርላማው የአሠራር ሥነ-ሥርዓት ጋር ያልተጣጣመና በተለመደው ጥድፊያ የተከናወነ ነው። አጀንዳው ለፓርላማው አባላት በተለመደው አሠራር መሠረት ያልተሰራጨ ከመሆኑም በላይ በሚመለከተው ቋሚ ኮሚቴ ከሕገ-መንግሥቱ አንፃር ሳይመረመርና ሳይታይ መጽደቁ ይህንኑ ያረጋግጣል።

 

የሕገ-መንግሥቱ አንቀጽ 9(3) ደግሞ “ በዚህ ሕገ-መንግሥት ከተደነገገው ውጭ በማንኛውም አኳኋን የመንግሥት ሥልጣን መያዝ የተከለከለ ነው” በሚለው መሠረት ተሿሚዎችም ስልጣኑን የተረከቡት ሕገ-መንግሥታዊ ባልሆነ መንገድ መሆኑን በግልጽ ያሳያል።

 

ከዚህ ሀቅ ስንነሳ ሕገ-መንግሥቱን አየናደ የሚገኘው መንግሥት በተቃራኒው ይህንኑ ሕገ-መንግሥት በመጥቀስ ተቃዋሚዎችን፣ የነፃውን ፕሬስ አባላት እና በቅርቡ ደግሞ መብታቸውን የጠየቁ የሙስሊሙ ማህበረሰብ መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላትን፣ ሕገ-መንግሥቱን እያጣቀሰ በፈጠራ ክስ ለወህኒ ሲዳርጋቸው በተደጋጋሚ ታይቷል። በመሆኑም ሕገ-መንግሥቱ ገዢው ፓርቲና መንግሥት ሲፈልጉ የሚረግጡት ሲያሻቸው ደግሞ የፈጠራ ወንጀል ማጣቀሻ አዋጆችን እያወጡ የሚያፍኑበት እንጂ በመንግሥትና ሕዝብ መካከል የሚኖረውን ሚዛናዊ የመብትና ግዴታ ግንኙነት የሚወስን የሁላችን የጋራ ሠነድ ሆኖ እያገለገለ ያለመሆኑን መረዳት አዳጋች አይደለም።

 

ገዢው ፓርቲና መንግሥት ለተፈጠረው ኢ-ህገ መንገሥታዊ ድርጊት “ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮች ሳይሆኑ የተሾሙት በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የሚሰሩ ኃላፊዎች ናቸው” የሚለው መከራከሪያ የቋንቋና የቃላት ጨዋታ ከመሆን አያልፍም። ይህ ደግሞ ችግሩን የሚፈታ ሳይሆን ይበልጥ የሚያወሳስበው ይሆናል። አዲስ ተሿሚዎቹ የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርነት ማዕረግ ሳይሰጣቸው በሚኒስትርነት ማዕረግ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የየዘርፎቹ አማካሪዎች መሆን አይችሉም ነበርን? ሕመሙን የደበቀ መድህኒት የለውም እንደሚባለው ሁሉ እውነተኛና ትክክለኛ የአሿሿሙ ምክንያቶች ከተደበቁ መፍትሔውም በቀላሉ የማይገኝ ስለሆነ ሁኔታውን እንደ ገና በጥሞና ማየቱ ይጠቅማል።

 

ስለሆነም መንግሥት ማለትም አስፈፃሚው አካልም ሆነ ፓርላማው ሕገ-መንግሥቱን አክብረው የማስከበር ኃላፊነት ያለባቸው በመሆኑ የተፈጠረውን ኢ-ሕገመንግሥታዊ አካሄድ በአስቸኳይ እንዲያርሙ እንጠይቃለን። በተመሣሣይ እኛም ይህን ጥያቄ የምናቀርበው ሕገ-መንግሥቱን የማክበርና የማስከበር መብትና ግደታችን መሠረት አድርገን በመሆኑ የጉዳዩ ባበት የሆነው የኢተዮጵያ ሕዝበም ሕገመንግሥቱና ሕገ-መንግሥታዊነት እንዲጠበቅ ከጎናችን ሆኖ እንዲታገል ጥሪያችንን እናቀርባለን።

 

የ33ቱ ፔቲሽን አቅራቢ ፓርቲዎች ጊዜያዊ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት

 1. አቶ አሥራት ጣሴ - ሰብሳቢ

2. አቶ ወንድማገኘሁ ደነቀ - ም/ሰብሳቢ

3. አቶ ግርማ በቀለ - ፀሐፊ

4. አቶ ስለሺ ፈይሳ - ም/ፀሐፊ

5. አቶ አለሳ መንገሻ - አባል

6. አቶ ኤርጫፎ ኤርዴሎ - አባል

7. አቶ ለገሠ ላንቃሞ - አባል

ህዳር 28 ቀን 2005 ዓ.ም.

አዲስ አበባ

 

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ