ብልጽግና ፓርቲ የእውቅና ሰርቲፊኬት እንዲሠጠው ለምርጫ ቦርድ አመለከተ
ብልጽግና ፓርቲን የመሠረቱት ፓርቲዎች ፍቃድ ይሰረዛል
ኢዛ (ረቡዕ ኅዳር ፳፬ ቀን ፳፻፲፪ ዓ.ም. December 4, 2019)፦ በሦስቱ የኢሕአዴግ እኅት ድርጅቶችና በአምስቱ አጋር ድርጅቶች ውሕደት ላይ የተመሠረተው ብልጽግና ፓርቲ የእውቅና ሰርቲፊኬት (የምዝገባ የምስክር ወረቀት) እንዲሠጠው ለምርጫ ቦርድ ጥያቄውን አቀረበ።
ብልጽግና ፓርቲ ዛሬ ለምርጫ ቦርድ ያቀረበው ጥያቄ በአገሪቱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ሥነምግባር አዋጅ መሠረት ነው።
የእውቅና ምስክር ወረቀት ለማግኘት ካቀረበው ጥያቄ ጎን ለጎን፤ ምርጫ ቦርድ የብልጽግና ፓርቲን በውሕደት ለተቀላቀሉት ፓርቲዎች ከዚህ በፊት ሠጥቶት የነበረውን የምዝገባ የምስከር ወረቀት እንዲሰርዝ የሚጠይቅም ነው።
በውሕደት ለተመሠረተው ብልጽግና ፓርቲ በአዋጁ በተጠቀሰው መሠረት የእውቅናና የምዝገባ የምስክር ወረቀት (ሰርቲፊኬት) ለማገኘት የሚያስችሉትን መረጃዎች አቅርቧል ተብሏል። (ኢዛ)