ሪፖርተር ጋዜጣ (በታምሩ ጽጌ)

የፌዴራል የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማኅበራት ኤጀንሲ እንዳያንቀሳቅሱ ያገደባቸውን ገንዘብ በሚመለከት፣ ለፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ብለው የነበሩት የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ጉባዔ (ኢሰመጉ) እና የኢትዮጵያ ሴት የሕግ ባለሙያዎች ማኅበር (ኢሴሕባማ) ይግባኛቸው ውድቅ ሆኖ ከ16 ሚሊዮን ብር በላይ እንዲወረሱ ጥቅምት 9 ቀን 2005 ዓ.ም. ተወሰነ።

 

ኢሰመጉ ኤጀንሲው ገንዘቡን የማገድ መብት እንደሌለው ለበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማኅበራት ኤጀንሲ ቦርድ ባቀረበው አቤቱታ ገንዘቡን የሰበሰበው ኤጀንሲው በአዋጅ ከመቋቋሙ በፊት መሆኑን በመጥቀስ ቢሆንም፣ ቦርዱ የሰጠው ምላሽ ግን ኤጀንሲው የወሰደው ዕርምጃ ትክክል መሆኑን ነው። የቦርዱ ምላሽ ያልተዋጠለት ኢሰመጉ፣ ጉዳዩን ወደ ፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ወስዶት ነበር። ፍርድ ቤቱ የሁለቱንም ወገኖች ክርክር ከመረመረ በኋላ ኤጀንሲው የወሰደው ዕርምጃ ትክክለኛ መሆኑን በማረጋገጥ የኢሰመጉን ክስ ውድቅ አድርጎበታል።

 

ተስፋ ያልቆረጠው ኢሰመጉ የሥር ፍርድ ቤት መሠረታዊ የሕግ ስህተት ፈጽሟል በሚል ለፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት አቤቱታ ሲያቀርብ፣ ማመልከቻውን የመረመረው ፍርድ ቤቱ “ትክክል ነህ ያስቀርባል” ብሎት ነበር። ፍርድ ቤቱ በቀረበው አቤቱታ ላይ ሁለቱን ወገኖች አከራክሮ የመጨረሻ እልባት ለመስጠት አምስት ቀጠሮዎችን ከሰጠ በኋላ፣ ጥቅምት 9 ቀን 2005 ዓ.ም. ኤጀንሲው የወሰደው ዕርምጃ ትክክል መሆኑንና የሥር ፍርድ ቤት የሰጠው ውሳኔም ተገቢ መሆኑን በማረጋገጥ ሲከራከርበት የነበረውን ስምንት ሚሊዮን ብር እንዲወረስ ወስኗል።

 

በተመሳሳይ ሁኔታ ከስምንት ሚሊዮን ብር በላይ ታግዶበት የነበረው የኢትዮጵያ ሴት የሕግ ባለሙያዎች ማኅበርም ተመሳሳይ ውሳኔ ተላልፎበታል።

 

ኢሰመጉ ከ18 ዓመታት በፊት ከውጭና ከአገር ውስጥ ለጋሾች ያሰባሰበው ስምንት ሚሊዮን ብር፣ የኤጀንሲው ቦርድ በአዋጅ ቁጥር 621/2001ን መሠረት በማድረግ ያገደበት ሕግ ከሚፈቅደው ውጭ እንደሆነ በመግለጽ ከባንክ እንዳያንቀሳቅስ ማድረጉን መዘገባችን ይታወሳል።

 

ኤጀንሲውን ለማቋቋም የወጣው አዋጅ 621/2001፣ አንድ አገር በቀል የበጎ አድራጎት ድርጅት ከአሥር በመቶ በላይ የሚሆን ገቢውን ከውጭ አገር ለጋሾች ማግኘት እንደማይችል ቢደነግግም፣ ኢሰመጉ ደግሞ አብዛኛውን ገንዘብ የሰበሰበው ከአገር ውስጥ መሆኑን፣ ከውጭ አገር ቢሆንም እንኳን አዋጁ ከመውጣቱ በፊት በመሆኑ እንደማይመለከተው ሲገልጽ ቆይቷል።

ምንጭ፦ ሪፖርተር ጋዜጣ

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ