Home ኪነ-ጥበብ ግጥም እኛም ቃል ገብተናል! (ወለላዬ)
 
እኛም ቃል ገብተናል! (ወለላዬ) Print E-mail
User Rating: / 17
PoorBest 
Art - ግጥም Poem

እኛም ቃል ገብተናል!

ወለላዬ -  This e-mail address is being protected from spambots, you need JavaScript enabled to view it  

ከልቧ ላይፋቅ ማንም ላያሽራት፣

ቡርቱካን፧ ቃልሽን ለውጪው አትበሏት።

እውነት ጨብጣ ነው ፊትም አነሳሷ፣

ከቃሏ ጋር አብራ ትሞታለች እሷ።

 

እንኳን ታክሎበት የሙያ ምግባሯ

በቃል የፀና ነው ወገናዊ ፍቅሯ።

ገና ከጅምሩ መድረኩን ስትረግጥ፣

ብርቱካን ምላለች ቃሏን ላትለውጥ።

የቃል ኪዳን ዕዳ ይዛለች አደራ፣

ላገሯ ነፃነት ልትቆም ልትሠራ።

እልቧ ያለውን ያን ቃሏን ቀምቶ፣

ሊወስደው አይችልም ማንም አስፈራርቶ።

ፍፁም ላያግዳት ላይበግራት እስር፣

ለቃሏ እንደምትሞት ተናግራ እኮ ነበር።

በሐሰት ውንጀላ እናንተው አስራችሁ፣

ሸምግሉን በማለት እናንተው ፈታችሁ፣

ያንን እኩይ ተግባር ያን የሐሰት ወንጀል፣

ከስር መሰረቱን እውነት ለማስመሰል፣

እንደልማዳችሁ ብታስሩ ብትገሉ፣

ስጋ ነው ፈራሹ ሞቶ አይቀርም ትግሉ።

ስለዚህ አትልፉ! ቃል ልታስለውጡ፣

ለሐሰት ቆማችሁ እውነት አትቀላውጡ።

መገኛ ቦታውን ስፍራውን ስታውቁ፣

ከእውነተኛ ሰዎች ሐሰት አጠብቁ።

ምንም ቢኮመጥጥ ባይጥማችሁ ቃሉ፣

እውነትን በሐሰት ለውጡት አትበሉ።

እንኳንስ በእውነት በሐሰት መለከፍ፣

ጸንቶ ባያጸናም ታይቷል ሲያክለፈልፍ።

ከእውነተኛ ዳኛ ያውም ከታጋይ ሴት፣

ልታገኙ አትችሉም ብትፈልጉ ውሸት።

እንዳሁኑ ጊዜ እንዲህ እንደናንተ፣

ለተንኮል ተውልዶ በተንኮል የሞተ፣

የፍጡር ጭቅቅት ጠባየ ጠምዛዛ፣

ወትሮም ከጥንት አሉ ቁጥራቸው ሳይበዛ።

ጊዜ ጊዜን ወልዶ ታሪክም ታሪክን፣

ዘመን እንዳስረዳን የመኖር ምስጢሩን፣

ካዳም ዘመን ወዲህ ዘርፉ ተያይዞ፣

እናንተ ላይ ደርሷል ተጉዞ ተጉዞ።

ነገር ግን እስካሁን በእጅጉም ብትለፉ፣

አትችሉም ካለም ላይ ሐቅን ልታጠፉ።

ብርቱካን ሚደቅሳም ያበራችው ሻማ፣

እንዲሁም የቴዲ የትግል ዓላማ፣

እንኳንስ በመለስ በነግርማ ፊርማ፣

በልዑል ዳኝነት የፍርድ ቁልመማ፣

በማንም የምድር ኃይል አይችልም ሊቀማ።

ስለዚህ ሁላችን በአንድነት ቆመናል፣

እወቁት እንግዲህ እኛም ቃል ገብተናል።


 

ወለላዬ ከስዊድን This e-mail address is being protected from spambots, you need JavaScript enabled to view it  

ታህሳስ 24 ቀን 2001 ዓ.ም. January 02, 2009

 

 

ተያያዥ

አዲስ ዜናዎችና ጽሑፎች

 

በጽሑፍ መሳተፍ ለምትፈልጉ በሙሉ!

በማናቸውም ጉዳይ ላይ ያለዎትን ሃሳብ፣ አስተያየት፣ ትችት፣ ግጥም፣ ልብወለድ፣ … በማይክሮሶፍት ወርድ ፕሮግራም በዩኒኮድ ፎንት ጽፈው ከራስዎ ኢ-ሜይል ሳጥን ጽሑፎትን አያይዘው በኢ-ሜይል አድራሻችን 

ethiopiazare@gmail.com ቢልኩልን ለሥራችን ቅልጥፍና ይረዱናል።

ኢትዮጵያ ዛሬ