ስንት ዘንድሮ ያልፍብናል! (በስደት ከኢትዮጵያ መምህራን አስተባባሪ ኮሚቴ)

የአንባብያን ድምፅ: 5 / 5

Star ActiveStar ActiveStar ActiveStar ActiveStar Active

በስደት ከኢትዮጵያ መምህራን ማህበር አባላት አስተባባሪ ኮሚቴ

Coordinating Committee of Exiled members of Ethiopian Teachers Association

የተሰጠ መግለጫ

መጋቢት 24 ቀን 2004 ..

 

ስንት ዘንድሮ ያልፍብናል!

የኢትዮጵያ ሕዝብ የግፍ አግዛዙን ከጫንቃው ላይ አውርዶ በሕዝቡ ይሁንታ የሚመሠረት ሥርዓት ለመገንባት ብዙ መልካም አጋጣሚዎች ተከስተው እንደዋዛ አልፈዋል። አንደኛው የሕብረተሰብ ክፍል ላይ አደጋ ደርሶ ጩኸት ሲያሰማ ሌላው እንዳላየ፤ እንዳልሰማ እየሆነ ነግ በኔን ዘንግቷል ማለት ያስደፍራል። በእርግጥ ሕዝባዊ ትግሎች በየአቅጣጫው ተጀምረው ሲፋፋሙ ጠላቶቻችን በመረባረባቸው የሚፈለገው ድል ርቆብናል። ለድሉ መጨናገፍ ግን የጠላቶቻችን ጥንካሬ አልነበረም ወሳኙ። በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ የጠላቶቻችን አቅም ያጎለበትን ራሳችን መሆናችንን መካድ ከገሀዱ ዕውነት መሸሽ ይሆናል።

 

ወያኔ ኢትዮጵያን እንዲያፈርስ ውክልና ሰጥተው ባሰማሩት የውጭ ኃይሎች የሞራልና የማቴሪያል እገዛ እየተደረገለት ሲገሰግሥ ለንደን ላይ የተጀመረውን የይስሙላ ድርድር ስናስታውስና የወያኔ አገዛዝ 97 ትን ምርጫ በነማን እገዛ መና እንዳስቀረው ስናስብ የምናመሳክረው ብዙ ጉዳዮች አሉ። ዘረኛው የወያኔ ፓርቲ ዘረኝነትን በአዋጅ ከአረጋገጠ በኋላ የሥልጣን ማሟሻ ያደረገው ለግማሽ ምዕተ ዓመት የዳበረውን የኢትዮጵያ የመከላከያ ሠራዊት በማፍረስ ነበር። ከዚያም 80ሺህ በላይ የሕንጻ ኮንስትራክሽን ሠራተኞች፣የገጠር መንገድ ሰራተኞችእያለ ማፍረስ ቀጠለ፡፡ከሁሉም በላይ ታሪካዊ የነበረዉ የባሕር ትራንዚት ሰራተኞች በአብዮት (በመስቀል) አደባባይ ከሶስት ወራት በላይ የሌሊት ቁር የቀን ሐሩር እየተፈራረቀባቸው የመብት ጥያቄ እያነሱ ቆይተው በታጣቂ ኃይል በቆመጥ እየተደበደቡ፤ በጫማ እየተረገጡ ሲባረሩ ለምን ብሎ የጮኸላቸው ወገን አልታየም፤ ትብብርም አላገኙም ነበር። ወያኔም የልብ ልብ ስለተሰማው ወኔአችንን በዘንግ እየለካ እንደአስፈላጊነቱ ቅጣት ማውረዱን ቀጥሎ እስካሁን ደርሷል። እንደባህር ትራንስፖርት ሠረተኞች ሁሉ የባንክ ሠራተኞች ባሳዩት ብልህና ቆራጥ ርምጃ መታገዝ ሲገባቸው በምትካቸው ሠራተኛ ለመቅጠር ወያኔ ማስታወቂያ ሲያወጣ ራስ ወዳዶችና ኅሊና ቢሶች ለመቀጠር የባንኩን ቅጥር ግቢና አካባቢውን የድጋፍ ሰልፍ አስመሰሉት አሳፋሪ ድርጊትም ነበር። በሂደቱም የባንኩ ሠረተኞች አድማ ከሸፈ።

 

አንድ ሕዝብ፣ አንድ አገር፣ ፍትህና ነፃነት፣ የሕግ የበላይነት፣ እኩል የትምህርትና የሥራ ዕድል፣ ከዚሁ ጋር ዴሞክራሲያዊና ሰብአዊ መብቶች ይከበሩ የምንል ከሆነ በአንድ የህብረተሰብ አካል ላይ የሚቃጣው ጥቃት የሌላውም ሆኖ ሊሰማን ይገባል። ያንዱ የሙያ /የሥራ መስክ ለሌላው መስተጋብራዊ ጥቅም ያለውን ያህል ችግሩም በዚያው አንጻር ተወራራሽ መሆኑ አያጠያይቅም። በእኛ ዘመን ላይ ጀምሮ እያደገ የመጣ አጉል ባህል ወይም አስተሳሰብ በሌላው መሰዋእትነት መልካም ሥርዓት ግንባታ ዕደገት ብልጽግና ፍትህ ወዘተርፈእንዲፈጠሩ የመፈለግ አዝማሚያ ነው። የበኩሌን ምን ላበርክት ለሚለው ጥያቄ መልስ

 

ለእያንዳንዱ ዜጋ የሚተው ቢሆንም ተጨባጩ ሐቅ ግን እኔን አይመለከተኝም የሚል ይመስላል። ይኸ አመለካከት መቆም አለበት።

 

ኢትዮጵያውያን ሳይቃጠል በቅጠል የሚለውን ቁም ነገር ወደተግባር ለመለወጥ ባንድነት ቆመን ርምጃ ለመውሰድ ዳተኞች እየሆንን ተቸግረናል። ብዙውን ጊዜ የወያኔ ማወናበጃ ፕሮፓጋንዳ አደንዝዞ ወርቃማ አጋጣሚዎች እንዲያልፉን አድርገናል። የጋራችን የሆኑና ልንቆምላቸው በሚገቡ ጉዳዮች ዙሪያ አደጋ ሲያንዣብብ በየግላችን ላይ የማይደርሱ አየመሰለን የጥቃቱ ሰደድ አሳት አገሪቱን በመላ አዳርሶ ዘር፣ሃይማኖት፣ፆታ፣ወጣት፣አረጋዉያን፣አርሶ አደር፣ ሠራተኛ፣ ተማሪ፣ መምህር ወዘተሳይለይ እየለበለበ ይገኛል። ባጠቃላይ የአገሪቱ ሕልዉና አደጋ ላይ ነዉ።

 

የማያጠግብ እንጀራ ከምጣዱ ያስታውቃል እንዲሉ የወያኔን የዘረኛነት ፖሊሲና አምባገነናዊ አካሄድ ከመነሻው የተረዱት ኢመማና መምህራን መራራ ትግል አካሂደው ዙሪያ ገብ መስዋእትነት ከፍለዋል። ወያኔ በማህበራቸው የውስጥ ጉዳይ እየገባ የማተራመስ ተግባሩን እንዲያቆም በኃይማኖት አባቶች፤ ያገር ሽማግሌዎች ሳይቀሩ አበክረው መጠያቃቸውን እናስታውሳለን። በዕውን የታየው ግን አገር በቀል ከሆኑት ድርጅቶችና ግለሰቦች የበለጠ የሞራልና የማቴሪያል ድጋፍ ይገኝ የነበረው ከአገር ውጪ ካሉ ግለሰቦች፣ ከዓለም አቀፍ የትምህርት ድርጅት (Education International- EI) ከአለም አቀፍ ሰራተኖች ማህበር (International labor organization – ILO) ከዓለም አቀፍ የሠራተኞች ኮንፌዴሬሽን (International Confederation of Trade Union- ICFTU) ከሂውማን ራይትስ ዎች (Human Rights Watch) አምነስቲ ኢንተርናሽናል (Amnesty International) ነበር። መምህራን የሙያ ክብራቸውን፤ የትምህርቱን ጥራት፤ የመደራጀት ነፃነታቸውን ለማረጋገጥ በሚያደርጉት ግብግብ በተወሰነ ደረጃ ዜጎች ከጎናቸው መቆማቸው ባይካድም የትምህርት ጥራትና የተተኪው ትውልድ ዕጣ ፋንታ ያለ ሕዝብ ሁለገብ እገዛ ግቡን ይመታል ብሎ መጠበቅ ስህተት ነው። መምህራን የወያኔ የትምህርት ፖሊሲትውልድ ገዳይነው ብለው ሲሟገቱ ሕዝቡ ጩኸታቸውን አዳምጦ፤ ወደትግሉ መቀላቀል በትምህርቱ ላይ የተደቀነውን ደባ አቅጣጪያውን ማስቀየር የሚጠበቅ ነበር። ነገር ግን ይህ አልሆነም።

 

በመምህራንና በሙያ ማህበራቸው በኢመማ ላይ የሚድርሰው ወከባና እንግልት ሳያቋርጥ እስካሁን መዝለቁን ከፍ ብሎ ጠቅሰነዋል። ለዚህም ነው ከቅርብ ወራት ጀምሮ መምህራን በኑሮ ውድነት እጅግ በመደቆሳቸው እርዛቱ፤ ረሃቡና ከዚህ ጋር ተያያዥ የሆኑት የጤንነት፤ የሞራል፤ የመብት ጥያቄ ሊያነሱ የተገደዱት። የኢትዮጵያ መምህራን እንደቀድሞው መከበርና ያለስጋት መኖር የቅንጦት ጥያቄ ያህል እየተረሳ መጥቷል። የትምህርቱ ጉዳይ ዋጋ ማጣት የመምህሩ ሙያና ክብር መርከስና መዋረድ ነፀብራቅ ሊሆን ችሏል። ቢያንስ እንደሌላው የመንግሥት ሠራተኛ ተመጣጣኝ ደመወዝ እየተከፈለን መኖር እንችል ብለው ላነሱት ጥያቄ የካድሬና የወያኔ ባለሥልጣናት መሣለቂያ እየተደረጉ ነው። በጣም የሚያሳዝነው ያለ መምህራን ምርጫ በማህበሩ አመራር ላይ የተቀመጡ ተለጣፊዎች በድሬደዋ ከተማ በተደረገ ጉባዔ ተብዬ ለመምህሩ የቆሙ መስለው ስለደሞዝ ጭማሪ ጥያቄ ለመለስ ዜናዊ አቅርበው ነበር። ምላሹ በመዘግየቱና የመምህራንም የኑሮ ውድነት ከሚችሉት በላይ አሻቅቦ ስለአንገፈገፋቸው ዴሞክራሲያዊና ሠላማዊ የሆነውን መብታቸውን በመጠቀም የሥራ ማቆም አድማ መምታት ተገደዱ። ወያኔም እንደ ልማዱ የሽንገላና የማጭበርበር ሥራውን ጀመረ። ተለጣፊዎችም በበሉበት መጮሀቸውን ቀጠሉ። ለመምህራን የተፈቀደው የደሞዝ ጭማሪ ተገቢ ነው ሲሉም የአይጥ ምስክር ድንቢጥ ሆኑ። ይህ ደግሞ ይበልጥ የመምህራኑን ሆድ አስከፋው። የተቃውሞውንና የሥራ ማቆም አድማሱን እያሰፋው መጣ።ባለፈው

 

በስደት የኢትዮጵያ መምህራን ማህበር አባላት አስተባባሪ ኮሚቴ ባወጣው መግለጫ ሰለተለጣፊው ማህበር አፈጣጠርና ባህርይ ጥቂት ተብሎ ነበር።መምህራንን አስተባብሮና የነርሱን ፍላጎት አንግቦ ለመራመድ እንደማይችል፤ ይልቁንስ መምህራን በራሳቸው ተነሳሽነት እየተሰበሰቡ ትግሉን እንዲያጠናክሩ አሳስቦ ነበር። ችግሩ በየትኛውም የአገሪቱ ክፍል ያለ ስለሆነ በክልል፤ በከተማና በገጠር በሚል የሚታጠር ሳይሆን ከዚያም በላይ ሕዝባዊ ተሳትፎ እንዲጎለብት ተደርጎ የትግሉ ወላፈን ቦግ እልም የሚል ሳይሆን እስከድል ድረስ የሚጫጫስ፤ የሚንቀለቀል እንዲሆን ጠቁሞ ነበር። አሁንም መደረግ ያለበት ነው።

 

አዎ አሁን ውቅቱ የሕልውና ጥያቄ ጉዳይ ሆኗል፤ ትውልድ የማዳን ጉዳይ ሆኗል፤ አገር የማዳን ጉዳይ ሆኗል። መምህራን ደግሞ ለዚህ ግምባር ቀደም ሆነው መሰለፍ ይጠበቅባቸዋል። በእርግጥም ምልክቶቹ የቀድሞ ታሪኩን የሚያድሱ ይመስላሉ። የኮከብ ጽባሕ ሁለተኛ ደረጃ /ቤት መምህራን ስብሰባ ተቀምጠው ያወጡት ያቋም መግለጫ የትም ቦታ ያለውን መምህር ሁኔታ የሚያሳይና የሚያኮራ ነው። ለተግባራዊነቱ ከሁሉም መምህራንና የህብረተሰብ ክፍል መተባበርና መታገል ደግሞ ራሱን የቻለ አዎንታዊ ክንዋኔ ይሆናል።

 

በሰሜን ጎንደር በተለያዩ /ቤቶች የታየው የመምህራን እንቅስቃሴ በፈር ቀዳጅነት የትግሉን አዲስ ምዕራፍ የከፈተና የሚደነቅ ከመሆኑም በላይ በአገሪቱ በመላ ሊሸጋገር የሚገባ እንቅስቃሴ ነው።

 

ከላይ አልፎ አልፎ እንደተጠቆመው ያሁኑ የመምህራን ትግል የችግሩ መንስኤ የሁሉም ኢትዮጵያዊ ነው። በቅርቡ በቴሌኮሙኒኬሽን ሠረተኞች ላይ ወያኔ የወሰደውን የጭካኔ ርምጃ ማስታወስ በራሱ በቂ ነው። የኑሮ ውድነት ያልነካው ቢኖር ወያኔና ግብረ አበሮቹ ብቻ ናቸው። ወያኔ በኢትዮጵያ ሕዝብ ስም ከተለያዩ አገሮች ገንዘብ ተበድሮ ሕዝብን ዕዳ ተሸካሚ ከሚያደርግበት ለመላቀቅ ገበሬዎች ለዘመናት ከኖሩበት ቀዬ እየተወገዱና እየተሰደዱ ይዞታቸው የነበረ መሬት ለውጭ ባለሀብቶች ወያኔ ከሚቸበችብበት ተግባሩ ለመከላከል፤ በቁማችን በኑሮ ውድነት እንድናልቅ ወያኔ ከሚያደርግበት ሁኔታ ለመከላከልና ባጠቃላይ የአገሪቱን ሕልውና አዳክሞ የዜጎችን መብት ከሚረገጥበት ለመከላከል በጋራ እንነሳ። ስንት ይለያል ዘንድሮ ያልፍብናል? አናፈግፍግ።

 

በአሁኑ ጊዜ የኢትዮጵያ መምህራን እያደረጉ ካሉት የሥራ ማቆም አድማ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል ሠራተኛው፤ ገበሬው፤ ታክሲ ነጂው፤ ምሁሩ፤ ተማሪው፤ ነጋዴው፤ ወላጅ ከመምህራን ጎን ቆመው በመተባበርና በመሳተፍ ሕዝባዊ ትግሉን እንዲያቀጣጥሉ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን።

 

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ !

 

ድር ቢያብር አንበሳ ያስር!

 

የመምህራን ትግል ግቡን ይመታል!

 

 

ሁሉም ለመብቱ ዘብ ይቁም !

 

በስደት የኢትዮጵያ መምህራን ማህበር አባላት አስተባባሪ ኮሚቴ

 

መጋቢት 24 ቀን 2004 ..

 

ለበለጠ መረጃ This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. በመጻፍ ሊገናኙን ይችላሉ

የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ የተሠጠ መግለጫ

የአንባብያን ድምፅ: 4 / 5

Star ActiveStar ActiveStar ActiveStar ActiveStar Inactive

በሀገሪቱ ውስጥ እየደረሰ ያለው የመብት ጥሠት እና የህጋዊ ሥርዓት መናጋት በእጅጉ አሳሳቢ ሆኗል

ከኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ (መድረክ) የተሠጠ መግለጫ

 

ገዢው ፓርቲ አገሪቱን ከተቆጣጠረበት ጊዜ አንስቶ እስከአሁን ባለው ሁኔታ የዜጎች የመብት ጥሰት ከእለት ወደ እለት ከመሻሻል ይልቅ እየባሰ የመቀጠሉን ሁኔታ መድረክ በከፍተኛ ትኩረት እየተከታተለው ነው፡፡ ከነዚህ መረጃዎች በመነሳትም በሀገሪቱ ውስጥ የህግ የበላይነት አለ ለማለት ይቸግራል፤ ኢትዮጵያ ውስጥ ለመብት ጥሰት ሳይጋለጡ በሠላም ለመኖር የገዢው ፓርቲ አባላት መሆን የግድ እየሆነ የመጣ መሆኑንም ሲገነዘብ ታላቅ ቁጭት ያሳድርበታል፡፡ ምክንያቱም በኢህአዴግ ካድሬዎች ከሕግ አግባብ ውጭ ዜጎች ይታሰራሉ፡፡ ከሥራ ይፈናቀላሉ፡፡ ንብረታቸውን ይነጠቃሉ፤ ባጠ ቃላይ አለአግባብ ግፍና በደል ይደርስባቸዋል፡፡ ይህንን በገዢው ፓርቲ አካላት በዜጎች ላይ የሚፈፀመውን በደል መድረክ ሲመለከተው፣ ህግ የታለ? በወረቀት ላይ የመኖሩ ፋይዳው ምንድነው? እንዲል ያስገድደዋል፡፡ ለዚህ የመድረክ ድምዳሜ ለናሙና ያህል ጥቂት ማስረጃዎችን እንጠቅሳለን፡፡

 

1. የመድረክ ከአባል ድርጅቶቹ አንዱ የሆነው የአረና ትግራይ አባላት የደረሰባቸውን ግፍና በደል በመዘርዘር ባወጣው መግለጫ እንደተገለፀው በአረና ትግራይ አባላት ላይ እየደረሰ ያለው ግፍና በደል፣ በሀገሪቱ ህገ-መንግሥት የተደነገጉትን የዜጎች መብቶች በእጅጉ የሚፃረር እንደመሆኑ ዜጎች የፈለጉትን የፖለቲካ መስመር ደግፈው ያልፈለጉትን ተቃውመው በሠላም መኖር የማይችሉበት ሁኔታ ላይ መድረሱን ያሳያል የኢህአዴግን የፖለቲካ መስመር የሚቃወም ድርጅት አባል መሆን ለሕገ-ወጥ እስራት፣ ድብደባና ሕይወት ማጣት ድረስ ላለመጉዳት የሚዳርግ ከመሆን በተጨማሪ እንደሙያው ዜጎች ተቀጥረው መስራትና ይህ ለሚያስገኘው ጥቅማ ጥቅም ባለመብት አንዳይሆኑ አድልዎና መገለል የሰፈነበት ሥርዓት በሀገሪቱ መንገሱን ያሳያል፡፡

 

2. ከመድረክ አባል ድርጅቶች አንዱ የሆነው የኦሮሞ ፌዴራሊስት ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ኦፌዴን) በስፋት በሚንቀሳቀስበት አካባቢ ካገኘው መረጃ መድረክ እንደተረዳው በዜጎች ላይ እየተፈፀመ ያለው በደል እጅግ ዘግናኝ ነው፡፡ ድርጅቱ በሚንቀሳቀስበት በኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት በቄለም ወለጋ ዞን በሀዋ ገላንና በሀዋ ወለል ወረዳዎች በሚገኙ ቀበሌዎች ውስጥ ዜጎች ሌቦች ናቸው፣ በማለት በፖሊሲና በሚሊሺያ ያለ ፍርድ ቤት ትእዛዝ ከያዙዋቸው በሁዋላ፣ ፖሊስ ጣቢያ በመውሰድ ከባድ ድብደባ እንደፈፀሙባቸው ተረድተናል፡፡ ለምሳሌ በሀዋ ወለል ወረዳ አውሳ ሰመራ በተባለ ቀበሌ 1ኛ ሰንበቶ ወዬሳ፣ 2ኛ ይልቅ እስራኤል፣ 3ኛ ደገፉ ሲራጋ፣ 4ኛ ወሰኑ ዲሳሳ የተባሉ ሠላማዊ ዜጎች በፖሊስ ጣቢያ ከተፈፀመባቸው ድብደባ በተጨማሪ ሰብአዊ ከብራቸውን በማዋረድ፣ በድንጋይ ዳቦ ዘመኑ በኋላ ቀር የቅጣት መፈፀሚያ ዘይቤ ገበያ ውስጥ እያዞሩ በሕዝብ ፊት የመግረፋቸው ሁኔታ ኢሕአዴግ በ21ኛ ምእተ ዓመት ይችን ሀገር ወደኋላ ቀሩ ጥንታዊ (Primitive) ሥርዓት እየወሰዳት ነው ወይ? እንድንል ያስገድደናል፡፡ እንደዚሁም፣ በዚሁ በሀዋ ወለል ወረዳ ጉራቴ ወለል በተባለ ቀበሌ ነዋሪ የሆነ ረጋሳ ቲቾ የተባለ ሰው በየካቲት ወር በቶጆ ወረዳ ፖሊስ ተይዞ ተደብድቦ ህይወቱ ማለፉን ተረድተናል፡፡ ከዚያም ሬሳውም ወደ ተገቢው ህክምና ተቋም ተልኮ መመርመር ሲገባው፣ የወንጀል ድርጊቱን ለመሸፈን ሲባል ያለምርመራ እንዲቀበር መደረጉ ድርጊቱን ለመሸፈን የተወሰደ እርምጃ መሆኑም ግልጽ ነው፡፡ ይህ መሠረታዊ የሆነ የህግ ጥሰት ዜጎች በኢህአዴግ መንግሥት የፍትሕ ሥርዓት ላይ እምነት ያሳጣ ስለመሆኑ የሟቹ ረጋሳ ቶቹ ባለቤት ወ/ሮ ተመስጌ ለሙ በድርጊቱ ተበሳጭታ ባሏ በሞተ እለት በመኖሪያ ቤቷ እራስዋን በመስቀል ህይወቷ በአሳዛኝ ሁኔታ ማለፉ ጉልህ ማሳያ ነው፡፡ የዜጎች የሰብአዊ መብት ጥሰቱ በእጅጉ የተንሰራፋ ስለመሆኑ ተጨማሪ ማስረጃ የሚሆነው ደግሞ ከሟች ረጋሳ ቱቾ ጋር በወቅቱ በፖሊስ ጣቢያ ውስጥ የነበሩት 1ኛ ሰንበቶ ወዬሳ፣ 2ኛ ገመቹ ፈጠነ፣ 3ኛ አማና ጨዋቃ የተባሉ ንፁሃን ዘጎች ከባድ ድብደባ ተፈጽሞባቸው ሀኪም ቤት ተኝተው እየታከሙ መገኘታቸው ነው፡፡

 

1. የመንግሥት የፀጥታ ኃይል ሠራተኞች በቄለም ወለጋ ዞን በሀዋ ገላን ወረዳ፣ በየካቲት ወር 2ዐዐ4 ዓም በጎዳና ጨዋቃ ቀበሌ ነዋሪ በሆኑ ሰዎች ላይ ጨለማን ተገን አድርገው ዝርፍያ መፈፀማቸውና ተመሳሳይ ድርጊቶች በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች በኢህአዴግ የቀበሌ ባለስልጣን ካድሬዎች በሠላማዊ ዜጎች ላይ እየተፈፀሙ መሆናቸው፣

 

2. በደቡብ ክልላዊ መንግሥት በሀላባ ልዩ ወረዳ ቀበሌ፣ የቀበሌ ባለስልጣናት የስልጣን መቀራመት ሹክቻ ባስከተለው ግጭት የሰዎች ሕይወት ማለፈና ከፍተኛ ንብረት መውደሙ፡፡

 

3. በሀዲያ ዞን፣ በምሥራቅ ባደዋቾ ወረዳ በቀበሌዎች አከላለል ጉዳይ ላይ በሕዝቡ መሀከል ስምምነት በመጥፋቱ መንስኤነት በሰው ሕይወትና ንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳይ መድረሱ፣

 

4. በሱረማና የደዚ፣ ብሔረሰቦች መሀከል ሳይፈታ የቆየው የመሬት ይገባኛል ጥያቄ በኢህአዴግ ሥርዓት መልካም አስተዳደር ድቀት የተነሳ ወቅታዊና ፍትሓዊ ውሳኔ መስጠት ባለመቻሉ ቅራኔው ተባብሶ ወደ ግጭት በመሸጋገሩ የዘጎች ሕይወትና ንብረት በከፍተኛ ደረጃ መጥፋቱና በተለይም የሱርማውን አርብቶ አደር ሕዝብ ከመኖሪያ ቀየው እንዲሰደድ ምክንያት መሆኑ፣

 

5. ለጋምቤላ ክልል ጎደሬ ወረዳ በንፁሃን ዜጎች ላይ የደረሰው አሳዛኝ የጥቃት እርምጃ ይዚህ አይነቱ እንቅስቃሴዎች እየሰፋ እንዳይሄዱ መድረክን በእጅጉ ያሳስበዋል፡፡ ይኸውም በተለያዩ ፖለቲካዊ ማህበራዊና ኤኮኖሚያዊ ምክንያቶች መብቶቻቸው ያልተከበሩላቸው ወገኖች በሥርዓቱ ላይ ያላቸውን ጥላቻና ተቃውሞ ለማስተላለፍ ሲሉ ንፁሃንና ዜጎችን ጭምር ወደ ሚጎዳ አፍራሽ እርምጃዎች ውስጥ እንዳይገቡ መድረክ ይሰጋል፡፡

 

6. በቅርቡ በቤንች ማጂ ዞን የተከሰተው ምስኪን አርሶ አደሮችን ከመኖሪያ ቀዬአቸው በማፈናቀል በገፍና በግፍ የማባረሩ እርምጃም በሀገሪቱ የሕግ የበላይነት ከሥም ሥርዓት አልበኝነት የበላይነቱን በመያዘ ሀገሪቱን ቀውሰ ውስጥ እንዳይከታት መድረክ አጥብቆ ይሰጋል፡፡

 

ስለሆነም፣ የተቃውሞ ፖለቲካን ለማጥፋት ሲባል የዜጎችን ግለሰብና ቡድን መብቶችን እየ ረገጠ ያለው በሀገሪቱ መልካም አስተዳደር በመጥፋት ሕግና ሕጋዉነት የማይከበርበት ደረጃ ላይ የተደረሰበትን ሁኔታ በሠላማዊ ደሞክራሲያዊ አግባብ ለመቀየር መድረክ የሚያደርገውን ትግል በመደገፍ መጠነ ሠፊ ሠላማዊ እንቅስቃሴ ውስጥ እንዲገባ ለመላው ሕዝባችን ጥሪ እናስተላልፋለን፡፡

የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ (መድረክ)
መጋቢት 23 ቀን 2ዐዐ4 ዓም
አዲስ አበባ

 

የካናዳን ሕዝብ የትግላችን አጋር ስለማድረግ

Star InactiveStar InactiveStar InactiveStar InactiveStar Inactive

ሀገራችንን የገጠማት ችግር ዘርፈ ብዙ የመሆኑን ያህል የሚጠይቀው መስዋዕትነትም ከፍተኛ ነው። የውጭ መንግስታት የመለስን መጥፎነት ጠንቅቀው እያወቁ ድጋፋቸውን ያለማቋረጥ ሲሰጡት ስንመለከት ደግሞ ምን ያህል ትግላችን አዳጋችና ውስብስብ እንደሆነ እንረዳለን። በዚህም ምክንያት “ድሮስ ከባዕድ መንግስት ምን እንጠብቃለን” የሚል ቁጭትም በውስጣችን እንዲያጭር ያደርጋል። ነገር ግን የብዙ ጥያቄዎች የመልስ ጽንሰ ሃሳቡም በራሱ በጥያቄው ውስጥ ሊኖር መቻሉን ካጤንን ለዚህ ችግር መፍትሄውንም ማግኘት እንችላለን። (ሙሉውን ጽሁፍ ለማንበብ ይህንን ይጫኑ)

የዜጎች የንብረት ባለቤትነት መብት ይከበር!! (መድረክ)

Star InactiveStar InactiveStar InactiveStar InactiveStar Inactive

ከኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ (መድረክ) የተሰጠ መግለጫ

 

በአንድ አገር ውስጥ የሚኖሩ ዜጎች የባለአገርነት ስሜት እንዲኖራቸው የሚወጡ አዋጆች መመሪያዎችና ድንጋጌዎች ሁሉ አብዛኛውን የሕብረተሰብ ክፍል ስምምነት ያገኘ መሆን ይኖርበታል። መንግሥት ሕዝቡ የሚተዳደርበትን የትኛውንም አይነት ሕግ ሲያወጣ ማዕከል ማድረግ ያለበት የዜግነት መብትን ለማስጠበቅ ለማጎናጸፍ እንጂ አንገት የሚያስደፋ የሚያሸማቅቅ የሚያስፈራራ አፋኝና ባጠቃላይ በመብት ገፈፋ ላይ የተመረኮዙ መሆን አይኖርበትም። የከተማ ቦታን በሊዝ ስለመያዝ የወጣው አዋጅ ቁጥር 721/2004 . በማን አለብኝነት የዜጎችን ንብረት የማፍራት የመሸጥ የመለወጥ እና የመጠቀም መሠረታዊ መብቱን በሕግ ሽፋን የገፈፈ አዋጅ ነው። በኢህአዴግ የሚመራው መንግሥት በሥልጣን በቆየባቸው 20 ዓመታት ሲያደርግ እንደነበረው ሁሉ ዛሬም የሚወጡ ህጎች ከፖለቲካና የሥልጣን ዕድሜ ከማራዘም አንፃር ብቻ ታይተው በሕዝብ ላይ የሚጫኑ ናቸው።

 

የሊዝ አዋጅ አወጣጥ እና የአፀዳደቁን ሂደት ብንመለከት ፈፅሞ የተለመደውን አሰራር የተከተለ አይደለም። የዚህ አዋጅ አፀዳደቅ እና አቀራረብ ሁለት መሠረታዊ ግድፈቶች ይታይበታል፡-

 

1. በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 8 ንኡስ አንቀፅ 3 “የኢትዮጵያ ብሄሮች ብሄረሰቦች እና ሕዝቦች ሉአላዊነታቸው የሚገለፀው በዚህ ሕገ-መንግሥት መሠረት በሚመርጣቸው ተወካዮቻቸው እና በቀጥታ በሚያደርጉት ዴሞክራሲያዊ ተሳትፎ ይሆናል።ይላል ይሁን እንጂ በአዲሱ የሊዝ አዋጅ መሬትን በመሰለ መሠረታዊ ጉዳይ ላይ የሉአላዊ ሥልጣን ባለቤት የሆነውና በቀጥታ ጉዳዩ የሚመለከተው ሕዝብ ጉዳዩ ቀርቦለት በነፃነት እና በግልፅነት እንዲወያይበት አልተደረገም

 

2. ኢህአዴግ በፓርላማው የወጣው የሕዝብ ተወካዮች /ቤት ስነ-ምግባር ደምብና አሰራር እንኳን እንደሚገልፀው ከስብሰባው 48 ሰዓት በፊት የአንድ አዋጅ ረቂቅ ለም/ቤቱ አባል መድረስ እንዳለበት ይደነግጋል። የፓርላማ አባሉ በዚህ 48 ሰዓት ውስጥ ረቂቅ አዋጁን መርምሮ ባለሞያዎችን አማክሮ ይቀርባል። ረቂቅ አዋጁም ወደሚመለከተው ቋሚ ኮሚቴ ይመራል። ኮሚቴውም ባለሞያ ጋብዞና አማክሮ ለሕዝብና ለሚዲያው ክፍት አድርጎ ያወያያል ሃሳቡን አዳብሮ በድጋሚ ለፓርላማ ያቀርባል። ፓርላማው ሲፈልግ ያፀድቃል። ሳይፈልግ ውድቅ ደርገዋል። ግልፅ የሆነው አሰራር ይህ ሆኖ ሳለ ለራሱ ከመሰለውና ለፖለቲካ ፍጃታ ይጠቅመኛል ካለ እንኳን የሥነ ምግባር ደምብና አሰራር ቀርቶ ሕገ-መንግሥት የሚጥሰው የኢህአዴግ መንግሥት ትልቁን የዜጎች መብት ለፓርላማ አባላት ማታ 1200 ታድሎ ጧት 3 ሰዓት አዋጅ ሆኖ እንዲፀድቅ አድርጓል

 

እዚህ ላይ አንዳንድ ጉዳዮችን ወደ ኋላ መለስ ብሎ መዳሰስ ያስፈልጋል ብለን እናምናለን፡፡ በብዙ ጉዳዮች በኢህአዴግ መንግሥት በወንጀለኝነት የሚጠቀሰው ጊዜያዊ ወታደራዊ አስተዳደር ደርግ እንኳን የከተማ ቦታና ትርፍ ቤትን የመንግሥት ንብረት ለማድረግ ባወጣው አዋጅ ቁጥር 47/67 መዕራፍ ሁለት አንቀፅ 1 “አንድ ቤተሰብ ወይም ግለሰብ ለመኖሪያ ቤት መስሪያ የሚያውለው እስከ 500 ካሬ ሜትር የሚደርስ የከተማ ቦታ ሚኒስትሩ በሚወጣው መመሪያ መሠረት በይዞታ ሊሰጠው ይችላል። ባለይዞታ የሟች ሚስት ወይም ባል ወይም ልጆች በቦታው ተተክተው የመጠቀም መብት ይኖራቸዋል፡፡ይላል። ለም/ቤት ወይም ድርጅት በሚቀርበው አቤቱታ መሠረት ሚኒስቴር /ቤት እንደሚሰጥ በዚሁ መዕራፍ አንቀፅ 2 እና 3 ይገልፃል። በዚሁ አዋጅ ምዕራፍ 3 እና 12 የከተማ ቤት ስለማስተላለፍ በሚለው ሥርአንድ ቤተሰብ ግለሰብ ወይም ድርጅት በከተማ ቤቱ የመጠቀም ወይም ይህንኑ ቤት የማውረስ የመሸጥ ወይም የመለወጥ መብት አለው።ይላል።

 

ይህንን አዋጅ ስንመለከት የአገሪቱን የከተማ ነዋሪዎች ከግለሰብ ጭሰኝነት ነፃ ያወጣ የከተማ ቦታን የመሸጭ የመለወጥ እና የባለቤትነት ክብር እንዲጎናፀፉ ያስቻለ ነው ማለት ይቻላል። አንድ አዋጅ ትክክለኛ አዋጅ ነው። ሕዝባዊ ነው። ሊባል የሚችለው ብዙሃን ሕዝብ ሲያስደስት ነው። ኢህአዴግ በየጊዜው የሚያወጣቸው አዋጆች ግን ገዢዎችን የሚጠቅም ሕዝብና ሀገርን የሚጎዳ ዜጎችን አንገት የሚያስደፋ መብትና ጥቅምን የሚጋፋ ሆኖ እናገኘዋለን።

 

ሰሞኑን የወጣው አዋጅ 721/2004 . የከተማ ቦታን በሊዝ ስለመያዝ የወጣ አዋጅን ብንመለከት የሚያሳየን ይህንኑ ነው። የዚሁ አዋጅ ክፍል ሁለት አንፅ 6 ነባር ይዞታዎች ወደ ሊዝ ስሪት ስለሚቀየሩበት ሁኔታ ከተራ ቁጥር 1-7 ተዘርዝሮ ተቀምጧል። የኢህአዴግ ሹመኞች የነባር ይዞታዎችን አይመለከትም። ዝርዝር መመሪያ አልወጣም። ተረጋጉ እያሉ በሕዝብ ላይ ውዥንብር ይፈጥራሉ። ነባር ይዞታዎችን አይመለከትም ቢሉም ሲሸጥ ሲለወጥ ሊዝ እንደሚገባ በግልፅ ደንግጓል። አንድ ነባር ይዞታን ሲገዛ ከባለንብረቱ ከሚከፍለው ክፍያ በተጨማሪ ለመንግሥት ያንኑ ቦታ የሊዝ ዋጋ ይከፍልበታል። ይህ አሰራር ብዙ ምርምር ማይጠይቅ ንብረት በማስተላለፍ ላይ ተፅዕኖ እንደሚያሳድር ለማንም ግልፅ ነው። የነባር ይዞታው ባለቤት ቦታውን ሸጦ ሌላ አነስተኛ ቦታ ገዝቼ በተረፈችኝ ገንዘብ ሕይወቴን ልምራ ቢል የሚገዛው በሊዝ ነው። ነባር ይዞታዎች ከሊዝ የሚያመልጡት እንዴት ነው ይዞታው ሳይሸጥ ሳይለወጥ የንብረት ዋጋ ሳኖረው እንደ ጉልቻ በመቀመጡ ብቻ ከሊዝ አመለጠ ማለት ነውን?

 

አዋጁ ሕዝብ የአገሩን ባለቤትነት የሚነካ ነው። የሊዙ ጥሩነት ነባር ይዞታዎችን ይነካል አይነካም በሚለው አይለካም። የዜጋን ሁሉ ተስፋ ያጨለመ ነው። አዋጁ የአገሪቱን ሕዝብ ከይዞታ ባለቤትነት አሽቀንጥሮ ጥሎ መንግሥትን የመሬት ባለቤት የሚያደርግ ነው። አዋጁ አምባገነኖች በማን አለብኝነት የሚያወጡት አዋጅ ነው። ሕገ-መንግሥቱ መሬት የሕዝብና የመንግሥት ነው ቢልም ኢህአደግ ግን በራሱ ጠቅልሎ ሕዝብን ጭሰኛ አድርጐታል። ንብረት የማፍራት ሕገ-መንግሥታዊ መብቱን ነጠቆታል። በዚህም ሕዝብ አቋሙን በግልፅ አሳውቋል። ሕዝብ ከአዋጁ መውጣት በኃላ ለይስሙላ በተካሄዱ ስብሰባዎች ላይ በአዋጁ መውጣት ቁጣውን ገልጿል። ሕዝብ ትክክለኛ አቋም ወስዷል። ሕዝብ ሊደመጥ ይገባል። ሕዝብ መከበር አለበት የሕዝብን እምነትና ፍላጎት በጡንቻ እየጨፈለቁ የሕዝብን ጮኸት እንደ ቁራ ጮኸት እየቆጠሩ መጓዝ ለማንም አይጠቅምም። ሕዝብ የማስጠንቀቂያ ደውሉን አሰምቷል። ሕዝብ የመደመጥ መብት አለው፡፡ በኢህአዴግ የሚመራው መንግሥት በተቆጣጠራቸው የሚዲያ ተቋማት የመሰለውን የሚያስፈልገውን በሕዝብ ስም እያስተላለፈ የሚያካሂደው ፕሮፖጋንዳ ለራሱም ለሕዝቡም ለአገርም እንደማይጠቅም አውቆ ሊያስብበት ይገባል።

 

በአዋጁ ዙሪያ በመንግሥት ባለሥልጣናትና ካድሬዎች የሚሰጠው መግለጫና ከሕዝብ ለሚቀርበው ጥያቄ የሚሰጡት መልሶች የፌዝ መሆናቸው የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክን (መድረክ) ያስገረመው ጉዳይ ነው። ይህም ነባር ይዞታህ እስክትሸጠውና እስክትለውጠው ድረስ ሊዝ አይገባም ማለትዶሮን ሲያታልሏት በመጫኛ ጣሏትአይነት መሆኑ ነው። እነዚህ አካላት አንዳብራሩትነባር የዞታዎች ወደ ሊዝ ስርዓት የሚቀየሩበት ሁኔታ ዝርዝር ጥናት ተደርጎ 4 ዓመት ጊዜ ውስጥ እርምጃ ሊወሰድ እንደሚችል ነው።” (አዲስ ዘመን ጥቅምት 22/2004 .) ከባለሥልጣናነቱ ማብራሪያዎች ለመረዳት እንደተቻለው አዋጁ ከጥናት በፊት ቀድሞ የመጣ እንደመሆኑ የኢህአዴግ ሥርዓት የሕዝብን መብት ቤተ ሙከራ ማድረጉ የአገዛዙን ሥርዓት የዜጎችን ጥቅምና ክብር ማዕከል ያላደረገ መሆኑን ሕዝባችን ይገነዘበዋል። በመድረክ ዕምነት ደግሞ ይህ አዋጅ ከመውጣቱ በፊት ተገቢው ጥናት መካሄድ ነበረበት እንላለን።

 

ስለሆነም በገጠር ነዋሪው አርሶ አደር የይዞታው ባለቤት መሆን እንዳለበትና የከተማ ነዋሪውም የመኖሪያ ቤት የሰራበት መሬት ባለቤትነት እንዲያረጋግጥ መድረክ በፖለቲካ ፕሮግራሙ ያሰፈረውን አውን ለማድረግ በተያያዘው ትግሉ እንደሚቀጥል እየገለፅን መላው ሕዝባችንም መብቱን የሚጋፉ አዋጆችንና ድርጊቶችን ለመቃወም በምናደርገው እንቅስቃሴ ውስጥ ከጎናችን እንዲቆም ሀገራዊ ጥሪችንን እናቀርባለን።

 

የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ (መድረክ)

 

ጥር 17 ቀን 2004 .

 

አዲስ አበባ

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ