PM Dr. Abiy Ahmed

ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ

ወለላዬ ከስዊድን

ስንቱን ጉድ ይኾን የምታልፈው? ስንቱ ጉድ ይኾን የሚያልፍህ?

ለተነሳህበት ዓላማ፣ ለአንድነት፣ ለመደመር፣ ለብልጽግና የሰላም ጉዞህ።

ስንት ውትብትብ ይኾን የምትፈታው

ተናግረህ ምታሳምን - ተሻግረህ ምታሻግረው

እየሠራህ ላለኸው ላንተ ይቅርና ለእኔ ደከመኝ ያንተ ጣር፣

እንዴት ይኾን? የአንድ ቀን ውሎህ? እንዴት ይኾን? የአንድ ቀንህ አዳር

ለዘመናት የተቆለለ የአገር ጉድ አንተ ላይ ወድቆ ተከምሮ

ውሎ ሲያድር ሸክምህን እየጨመረው ከሮ

አላሠራ ቢልህም አላረፍክ - ይኸው ሥራህ ጎልቶ ወጣ

አዳዲስ ነገር ይዞ ነፍሰ ሥጋ ጨብጦ መጣ

ግን ይብላኝልህ ወንድሜ አይችሉ መቻል ለወደቀብህ

ሐሜት፣ ጥርጣሬ፣ ተንኮል፣ ምቀኝነት፣ ክዳትና መሰሪነት ላከሰለህ

እኔማ ምን ልረዳህ ከመብሰልሰል ከማሰብ በላይ አቅም የለኝ

ስደት አርቆ ያሰረኝ

ሐሳብ አመንምኖ ያኖረኝ

አንድ ብኩን አልሞት ባይ ነኝ።

አሁንማ ተስፋ ቆረጥኩ

በጽሞና ልኖር አሰብኩ

ፖለቲካው ተምታታብኝ

አካሔዱ ጠጠረብኝ

የሰው ሥራው ራቀብኝ

አመስግኘው ጨርሼ፣ አድሬ ሳልመጣ

ቃሌ በክህደት ቀርሽቶ ምርቃቴ እፌቴ ሲገረጣ

ስንት ግዜ አየሁ ስንት ግዜ ትዝብት ዋጠኝ

ስንት ጊዜ አሳቀቀኝ ስንት ግዜ አሳፈረኝ

ወንድምዬ ይብላኝ ላንተ፣ ላንተ ይብላኝ

እንደው ግን ለነገሩ የሰው ልጅ እንዲህ ነው ወይ ለካ

ሥልጣን የማይበቃው በተደረገለት የማይረካ

በቀለለለት ቁጥር ተጨመረብኝ ብሎ የሚያማርር

መሪውን በቁልቢጥ የሚሰፍር

ወንድሙን ለዕለት ውሎ የሚገድል

እንዲህ ነው እንዴ የኢትዮጵያዊነት የማስተሳሰሪያው ውል

ይኼን ነው እንዴ ከዘር ግንዱ የወረሰው

ይኼን ነው እንዴ ዓይቶ ሰምቶ ያደገው

ይሄን ሳስብ ያንተ ብርታት ሁሉን አስንቆኝ

እንደገና ነፍስ ዘርቶ አስነስቶኝ

ተስፋ ሠጥቶ ያውለኛል

ያንተ ነገር ግን ያሳሳኛል

የጉድ አገር ገንፎ እያደር ይፋጃል እንዲሉ

የኛም ጣጣ በረደ ስንል መጋሉ

ያሳስበኛል ላንተና ለአገር

ውጥንህ ተበላሽቶ መና ሆኖ እንዳይቀር

ይኼው ኢትዮጵያን ከዳበስካት ከመጣህላት ጀምሮ

እውነትና ውሸት ተስፋና ፍርሃት - አንድ ላይ ተከምሮ

በአስመሳዩ አዋሻኪው አሾክሻኪው

በአውደልዳዩ አጎብዳጁ ወሬ ነፊው

በሥልጣን ጥም በናወዘው

የዘር ልክፍት ባሳበደው

አገር እየተናጠች እየተላጋች ብታድርም

ያንተ ሥራ አልነጠፈም

ቀን በቀን እየተቃጠልክ እየከሰልክ

ስንቱን ፈውሰህ ስንቱን አዳንክ

ስንቱን ለምነህ እርቅ አወረድክ

ስንት ከቤቱ አግብተህ አሳደርክ

ያም ሆኖ ይብላኝልህ ላንተ፣ ነጋ ስትል ለሚጋርድህ ጭለማ

አለኝ ያልከው ለሚርቅህ ለሚጠነሰስብህ አድማ

ግን ማን ይመንህ በእጅህ ሰይፍ ሳትጨብጥ - ግዳይ ጥለህ ሳታቅራራ

አገር የለመደበትን አስጥተህ መች እሺ ይልሃል ስለ ፍቅር ብታወራ

ሰላም ፍቅርና ተስፋ፣ ለካ አያምርብንም ጃን

ይኼው ደም የለመደው እጃችን

እያጋደለ፣ እያጫረሰ ያውለናል

መተማመንና አንድነትን ነስቶናል

ያንተም እድልህ አልቀና አለ፣ መከራው ችግሩ እያደር ባሰ

ለሰላም ያልከው ለጥላቻ፣ ለፍቅር ያልከው ለጸብ ተነሳሳ፣

እርስ በእርስ ተጫረሰ

ከጎሬው ወጥቶ ስንቱ ደነፋ ስንቱ ዱላ ቀሰረ

ስንቱ በጠራራ ፀሐይ አበደ ስንቱ ቀን ለቀን ሰከረ

ስንቱ በተኛበት ተገደለ

ስንቱ ከኖረበት ተፈናቀለ

ይኼን ሁሉ መከራ እላይህ ላይ ተሸክመህ

ያላሰብከው ተፈጽሞ ሆኖ እያየህ

እንዴት ይኾን ውሎህ፣ እንዴት ይኾን እኮ አዳርህ

መቼ ይኾን ባፍህ ‘ሚዞር የለት ጉርስህ

ወንድምዬ! ይብላኝ ላንተ ይብላኝልህ

ሐውልት ብታቆም መርገምት፣

አንድነት ብትፈጥር ውግዘት፣

አገር ብታጸዳ ሹፈት፣

እርቅ ብታወርድ ቅጥፈት፣

ሆኖ ሲወራብህ መልኩን ለውጦ ሲቀርብልህ

ወንድምዬ ምን ተሰማህ?

የዘመናትን ግፍና በደል

በአንድ ግዜ ነቃቅለህ ለመጣል

አገር እንድታድግ ነፃነት ከአጥናፍ አጥናፍ እንድታበራ

ሕዝብ በአንድነት ተደምሮ እንዲሠራ

ያ’ረከውን ምንም እኛ ባንመሰክር ባናወራ

ከአገር አልፎ ዓለም ሰምቶት

ጥበብህን አውቆ አድንቆት

ስምህን ከአድማስ አድማስ እየጠራ አጉልቶ እያየህ

ከትልልቆቹ ተርታ አሰልፎ ሽልማት አሸከመህ

ያም ሆኖ ወንድምዬ ስንት ይኾን ገና የሚቀርህ

ለተነሳህበት ዓላማ የከፈልከው ገና ደግሞ ‘ሚያስከፍልህ

ብዬ እያሰብኩ የአገሬና ያንተ ነገር የሚጨንቀኝ

አንድ አንተኑ የምከተል ሥራህ ጉዞህ የሚገባኝ

ከሩቅ ኾኜ የምታዘብ ስደት ውጪ የጠፈረኝ

ለፍቶ ሠሪ ማስኖ አዳሪ የአገር ልጅ ነኝ

አንተ ግና የስንቱ ዐመል የጠበሰህ፣ ሸክሙ ከብዶ የተጫነህ

ትልቅ ሐሳብ እቅድ ያለህ የአገር ጉዳይ የሚያበርህ

ወጀብ ጎርፉ የሚንጥህ፣ ወዲያ ወዲህ የሚያላጋህ

ብዙ ገና ገና ብዙ የሚቀርህ፣

እረፍት የለሽ ውድ ወንድሜ፣ ይብላኝ ላንተ ይብላኝልህ!

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ