ሕዝብና ቤት ቆጠራ ለሦስተኛ ጊዜ እንዲራዘም ተወሰነ
ማዕከላዊ ስታትስቲክስ ኤጀንሲ
ምክንያቱ የኮሮና ወረርሽኝ ነው
ኢዛ (ሐሙስ ሰኔ ፬ ቀን ፳፻፲፪ ዓ.ም. June 11, 2020)፦ አራተኛው የኢትዮጵያ ሕዝብና ቤት ቆጠራ ለሦስተኛ ጊዜ እንዲራዘም ሁለቱም ምክር ቤቶች በጋራ ባካሔዱት ስብሰባ ወሰኑ።
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትና የፌዴሬሽን ምክር ቤት ዛሬ ሐሙስ ሰኔ 4 ቀን 2012 ዓ.ም. ባካሔዱት የጋራ ስብሰባቸው፤ ሕዝብና ቤት ቆጠራ ለሦስተኛ ጊዜ እንዲራዘም የቀረበውን የውሳኔ ሐሳብ ከተመለከቱ በኋላ፤ መራዘሙ ተገቢ መኾኑን በማመን ውሳኔያቸውን አሳልፈዋል።
ምክር ቤቶቹ ከዚህ ቀደም ለሁለት ጊዜ የተራዘመውንና አሁን ለሦስተኛ ጊዜ እንዲራዘም ውሳኔያቸውን ያሳረፉበት ዋንኛ ጉዳይ፤ ከኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ጋር በተያያዘ ቆጠራውን ለማካሔድ አመቺ ባለመኾኑ ነው።
ለሕዝብ ጤናና ደኅንነት ሲባል ቆጠራው እንዲራዘም የቀረበውን የውሳኔ ሐሳብም፤ በአምስት ተቃውሞ፣ በ13 ድምፀ ተአቅቦ እና በአብላጫ ድምፅ አጽድቀውታል። (ኢዛ)



