የትግራይ ክልል ምክር ቤት ከፌዴሬሽን ምክር ቤት ውሳኔ በተፃራሪ በክልሉ ምርጫ ለማድረግ ወሰነ
ውሳኔውን ያጸደቀው በሙሉ ድምፅ ነው
ኢዛ (ዓርብ ሰኔ ፭ ቀን ፳፻፲፪ ዓ.ም. June 12, 2020)፦ የትግራይ ክልል ምክር ቤት ስድስተኛውን ክልላዊ ምርጫ፤ በክልል ደረጃ ለማካሔድ በሙሉ ድምፅ ማጽደቁ ተሰማ።
በአገር አቀፍ ደረጃ መካሔድ የነበረበት ምርጫ አልተካሔደም፤ እኔ በክልሉ ውስጥ ክልላዊ ምርጫ አደርጋለሁ ሲል የነበረው ሕወሓት፤ ዛሬ ዓርብ ሰኔ 5 ቀን 2012 ዓ.ም. የትግራይ ክልል ምክር ቤት አስቸኳይ ስብሰባ ላይ፤ ስድስተኛውን ክልላዊ ምርጫ እንዲካሔድ አስወስኗል።
የትግራይ ክልል ኮምዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ እንዳመለከተው፤ የክልሉ ምክር ቤት የ2012 ክልላዊ ምርጫ ሕግን ተከትሎ በወቅቱ እንዲካሔድ የምክር ቤቱ አባላት ሙሉ ድምፅ ሰጥተዋል።
ይህ የክልል ምክር ቤቱ ውሳኔ በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ረቡዕ ሰኔ 3 ቀን 2012 ዓ.ም. በፌዴራል መንግሥቱ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ስድስተኛው አገራዊና ክልላዊ ምርጫው እንዲራዘም የወሰነውን ውሳኔ የሚፃረር ነው። (ኢዛ)