የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ማዕከል ተመረቀ
የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ማዕከል
ማዕከሉ ከመመረቁ በፊት በጡት ካንሠርና የጭንቅላት ዕጢ ላይ ሲሠራ ነበር
ኢዛ (እሁድ መስከረም ፲ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም. September 20, 2020)፦ ሰው ሠራሽ የኾነ የማሰብ ክህሎትን በተለያዩ የሥራ መስኮች የሚያሰማራ ቴክኖሎጂን የሚያሰርጸው የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ማዕከል ዛሬ እሁድ መስከረም 10 ቀን 2013 ዓ.ም. ተመርቆ አገልግሎት ጀመረ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ ሐሳብ አመንጪነት የተገነባው ይህ ማዕከል፤ ሙሉ ለሙሉ ራሳቸውን ችለው ለሰው ልጅ አድካሚ የኾኑ ተግባራትን በፍጥነት ማከናወን የሚያስችሉ ማሽኖችን የያዘ ነው።
ማዕከሉ ለግብርና፣ ለትምህርት፣ ለጤና እንዲሁም ለሕብረተሰብ ጥበቃና ደኅንነት አገልግሎቶች ይውላል።
ማዕከሉ ዛሬ ከመመረቁ ቀደም ብሎ አንዳንድ ሥራዎች ሲሠራ እንደነበር የተጠቀሰ ሲሆን፤ በእስካሁኑ የአጭር ጊዜ የአገልግሎት ጅማሮው በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ የተደገፉ የጡት ካንሰርና የጭንቅላት ዕጢ መለየት በሚያስችሉ መተግበሪያዎች እየሠራ ይገኛል ተብሏል። ማዕከሉን ዛሬ መርቀው የከፈቱት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ናቸው። (ኢዛ)



