የጠቅላይ ሚኒስትሩ የቀድሞ ኢሜይል ሃክ ተደረገ?
ወንጀለኞች በቀድሞ ኢሜላቸው ሐሰተኛ መረጃ እያሰራጩ በመኾኑ ጥንቃቄ አድርጉ ተባለ
ኢዛ (ማክሰኞ ሚያዝያ ፳፮ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም. May 4, 2021)፦ በቀድሞ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የግል ኢሜይል አድራሻ የተላከ በማስመሰል እየተሰራጨ ያለ መረጃ እንዳለ በመግለጽ፤ ጥንቃቄ እንዲደረግ የጠቅላይ ሚኒስቴር ጽሕፈት ቤት አስታወቀ።
“የወንጀለኞች ቡድን ከቀድሞ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የግል ኢሜይል አድራሻ የተላከ በማስመሰል መረጃ በመጠየቅ እና ሐሰተኛ ምላሽ በመስጠት ላይ መኾናቸውን አውቀናል” የሚለው ከጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ ጽሕፈት ቤት ዛሬ የወጣው ማሳሰቢያ፤ በዚህ ኢሜይል ሐሰተኛ መረጃ እየተሰራጨ መኾኑን ገልጿል።
በመኾኑም ሁሉም ሰው ሐሰተኛ መረጃ በመሰራጨት ላይ መኾኑን አውቆ፤ ተገቢውን ጥንቃቄ እንዲያደርግ የሚያመለክተው ይኽ ማሳሰቢያ፤ “እንደዚህ ያሉ አጠራጣሪና ጥፋት የሚያስከትሉ እንቅስቃሴዎችን ለሕግ አስከባሪ አካላት እንዲያሳውቅ እናሳስባለን” በማለት አክሏል።
ይህ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት የተሰጠው ማሳሰቢያ፤ በወንጀለኞች ተሰራጨ የተባለው የሐሰት መረጃ ምን እንደኾነ ባይገለጽም፤ ከማሳሰቢያው ኢሜይሉ ሃክ ተደርጎ ሊኾን ይችላል የሚል አንደምታ ያለው ስለመኾኑ ጥርጣሬ ያሳደረ ኾኗል። (ኢዛ)