ምነው ዲያስፖራ! (ዳግማዊ ዳዊት)
ምነው ዲያስፖራ!
ዳግማዊ ዳዊት This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.
ትናንት ለኢህአዴግ - ሲሠራ የነበረውን - “ያን ባለጌ ወራዳ
አላዋቂ ማይም - አጎብዳጅ - ለጠላት ያደረ ክፉ ባንዳ
ትምህርት ቤት ያልረገጠ - ደፋር ማይም - የማያውቀን ዘላባጅ
ህሊናውን የሸጠ - የወራዶች ሁሉ ውራጅ”
ተማረ እንዲባል ለስሙ - በመለስ ቀጭን ትዕዛዝ
እንዲመች ሆኖ - እንዲሠራ - ለወያኔው አገዛዝ

ሲቭል ሰርቪስ ገብቶ
በሕግ ተመርቆ ወጥቶ
ለአግአዚ ጦር አለቃ - ሆኖ - በኅዳር ሰማይ የጥይት መብረቅ ያጮኸ
እናቶችን በለቅሶ - በደረታቸው ያስዳኸ
ታዬ አሉ ዘንድሮ - እዚህ ዲሲ - አሜሪካ ምድር ገብቶ
“ሀገር ከድቶ - ከመለስ ተጣልቶ።”
ውሎ ሳያድር - ከተቃዋሚዎች ጎራ
ሲቀላቀል ሲያወራ
“ያንን ጠብደል ማይም - ያ ደደብ ያልነውን” ሰው
ይጀመራል ክፍከፋው - ይቀጥላል ምስጋናው
እናም በቆዩት ቦታ - እሱን ከፍ እናደርግና
ሊቅ ያለ እሱ ማን አለ - ብለን እንለውና
ትግሉ በወያኔ - ተመልሶ ሲጠለፍ - እናያለን እንደገና።
ወያኔ በስልቱ - በሚያውቀው ጎዳና
ጠላት አስመስሎ ወዳጁን - ማከላችን ያስገባና
ትግላችንን ሲያኮላሸው - መመዘን አቃተንና
ትግል ትግል እንላለን - ይህም ትግል ተባለና!
ምነው ዲያስፖራ - ምነው ሚናችን ቅጡን አጣ
የወያኔ ደጋፊ ነን - ወይስ ተቃዋሚ ባለአንጣ?
ዳግማዊ ዳዊት
This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.
ጥቅምት 2003 ዓ.ም.



