አቤ ቶኪቻው

የፈረንጆች ገና መጣ። እንንኳን መጣ! የእኛም በቅርቡ ይመጣል። እስከዛው ግን እንኳን ለፈረንጆቹ ገና አደረሰን እንባባል። ያው እንደሚታወቀው አነዚህ ፈረንጆች ገናቸውን ባከበሩ በሳምንቱ አዲስ አመታቸውን ደግሞ ያክብራሉ። ታድያ ይሄኔ እነርሱ አመት ባል ባመትባል ሲደራርቡ እና እረፍት በእረፍት ሲብነሸነሹ ፈረንጅ የያዘው ዶሴ ተሸፈፍኖ መተኛቱ ነውና፤ ከፈረንጅ ጉዳይ ያለው ሰው ቻል ማድረግ ይገባዋል ማለት ነው።

 

አነሳሴ እንኳ ስለ ዶሴ ለማውራት አልነበረም። ነገር ግን አሁን የፈረንጆች አዲስ አመት ሊገባ ሲል በኛ አዲስ አመት ዘወትር የሚነገር አንድ አባባል ትዝ ብሎኝ ነው። ምን መሰልዎ…?

 

ጉድ ሳይሰማ መስከረም አይጠባም!” እንግዲህ መስከረም አዲስ አመታችን ነው። ብዙ ተስፋ የምንሰንቅበት፣ ብዙ የምናቅድበት፣ ብዙ የምንፎክርበትአዲስ አመት። ታድያ ይህም ሆኖ መስከረም ከመጥባቱ በፊት የሚደመጡጉዶችአይጠፉም። ከዚህ ጋር ተያይዞ ነው ተረቱም መተረቱ! እናልዎ ሰሞኑን የሰማዋቸው አንዳንድ ነገሮች ለካስ የእኛ ብቻ ሳይሆን የፈረንጆችም አዲስ አመት ጉድ ሳይሰማ አይጠባምና! ብዬ እንዳስብ አደረጉኝ። ትዝ ሲለኝ ደግሞ ነገሩን የሰማሁት ከአዲሱ አመትም ከገናውም በፊት ነበርና ርዕሴንጉድ ሳይሰማ የፈረንጆች ገናም አይመጣም!” አልኩት። ጉዱ ምንድነው? ካሉኝ ልብ ለማንጠልጠል ያደረግሁት ሙከራ ተሳክቶልኛል ማለት ነው። ምን መሰለዎ…? አይቸኩሉዋእንደውም አዲስ መስመር ላይ እንገናኝ

 

የአቶ በረከት ስሞን መፅሀፍ መታተሙን ሰሙልኝ? ጉሽ! ከሰሙ ይበቃል ለማንበብ እንዳይጓጉ። እንኳንስ እርስዎ እና መፅሀፉን ያሳተሙላቸው ሼክ መሀመድ አላሙዲ እንኳአላነበብኩትም ነገር ግን ለወደፊቱ ትውልድ ዲሞክራሲ መማሪያ የሚሆን ነው!” ብለው ነው የተናገሩት ታድያ ጉደኛቸው ሼክ መሀመድ ካለነበቡት እርስዎ በምን እዳዎያነባሉ? ዝም ብለው አስተያየት መስጠት እና መስማት እየቻሉ።

 

ማሳሰቢያ፦ ከላይ ባለው አንቀፅ ሼኩን ጓደኛቸው ብዬ መፃፍ ሳያቅተኝጉደኛቸውሼክ መሀመድ ያልኩት ሆነ ብዬ መሆኑን ለማሳወቅ እወዳለሁ።

 

እናልዎ ወዳጄአንድ የተባረከ ወዳጄ ከመፅሐፉ የተወሰነ ቅምሻ ይሆንሃል ብሎስካንአደርጎ በኢሜል ልኮልኝ ነበር። ታድያ አንብቦ ሳይጨርሱ አስተያየት መስጠት በእኔ አልተጀመረምና፤ ለግዜው ጉድ ያሰኘኝን ነጥብ አነሳለሁ።

 

ቆይ ቆይ አቶ በረከት ስሞን መፅሐፋቸው ለምን ውጪ ሀገር ታተመ? ምንአልባት የኢትዮጵያ መንግስት እንደ እስክንድር ነጋ መፅሐፍ አታሚዎቻቸውንይህንን መፃፍ ታትሙ እና የእንጀራ ገመዳችሁ ይበጠሳል!” ብሎ አስፈራርቶባቸው ይሆን እንዴ? ይሄን ግዜ እርስዎፈቃጅ ከልካዩ እርሳቸው አይደሉ እንዴ!?” ብለው በአግራሞት ይጠይቁኝ ይሆናል፤ እኔ ያነበብኳትን ገፅ ቢያነቡ ግን ሌላም ነገር ይጠራጠራሉ።

 

የምር ወዳጄ፤ አቶ በረከትን ጠረጠርኳቸው! ብሎት ያምኑኛል? እንዴት ይበሉኛ…! እንዴት ማለት ጥሩ ጥያቄ ነው። ሰውየው ስለ አዲስ ነገር ጋዜጣ በመፅሐፋቸው ገፅ 250 ላይ እንዲህ ይላሉ፤አዘጋጆቹ በቴሌቪዥን መስኮት ቀርበው ሀገራችን ሀሳብን በነፃነት ለመግለፅ የሚያስችል መብት አለ!” ካሉ በኋላ ገበያቸው በአንዴ ቀዘቀዘ!” አሉ። ይህንን ሳነብ በእውነቱ አቶ በረከት ምን ነካቸው? ብዬ እጅግ ተደንቄያለሁ። ይህንን ንግግርየኢትዮጵያ ከረንት አፌርስወይምኢትዮ ሚዲያወይ ደግሞኢትዮጵያን ሪቪውአልያም ሌላ ገለልተኛ አስተያየት ሰጪ ወይም ተንታኝ ቢናገረው አይገርመኝም ነበር። ከአቶ በረከት ግን የምጠብቀውልጆቹ በኢቲቪ ቀርበው ዲሞክራሲ አለ ብለው ከተናገሩ በኋላ ገበያቸው ጨመረ።የሚል ንግግር ነበረ። ለካስ ሰው በኢቲቪ ሲቀርብ ህዝቡአይንህ ላፈር!” እንደሚለው አቶ በረከት ያውቃሉና? ጉድ አይሉልኝም?

 

እውነትም በተለይ አሁን አሁን የአገሬ ህዝብ አንድ ሰውን በኢቲቪ ሲመለከተው ጠንቋይ ቤት ያየው ያህል ነው የሚጠየፈው ብልዎ ያምኑኛል? አያምኑኝም። ምክንያቱም እርሱ ያጋንናል ብለው ስለሚጠረጥሩኝ አያምኑኝም። እውነቱ ግን ሰዉ ከኢቲቪ ደስ ብሎትእሰይ መጣልኝብሎ የሚመለከተውሰው ለሰውእናገመናድራማን ብቻ ነው። አኪልዳማንስ? ብለው ቢጠይቁኝ በሳቅ መሞቴ ነው!!!

 

በርግጥ አቶ በረከት ይህንን እንደሚያውቁ እኔም አውቃለሁ። ነገር ግን ደፍረው፤ ሊያውም ታሪክ ሆኖ በሚቀመጥ መፅሐፍ ላይ እንዲህ ይናገራሉ ብዬ አስቤም አላውቅም ነበር። እንዴ እኛን ሁሉ ስለ ኢቲቪ ቅድስና እንድንናገር አድረገውን ሲያበቁ ዛሬኢቲቪ ላይ ቀረቦ ዴሞክራሲ አለ፤ ያለን ሰው፣ ህዝቡ ይጠየፈዋልብለው ማለታቸው የንስሀ ዘመናቸው ደርሶ ይሆን? ያሰኛል ! አሁን አሁን ሳስበው በተለያየ ጊዜ የመንግስትን መግለጫዎች፣ ማብራሪያዎች፣ እና ማረሪያዎች ይዘው ምክትላቸው አቶሼም የለሽንየሚልኳቸው ለካስህዝቡ እስከ አሁን የደበርኩት ይበቃኛል። አሁን ደግሞ እስቲ አንተ ሂድእያሉ ነውና…! ጉድ ሳይሰማ የፈረንጆች ገናም አይመጣም ማለት ይሄኔ አይደለም?

 

ለአቶ በረከት አንድ ጥያቄ አለኝ። አዲስ ነገሮች አንድ ቀንኢቲቪ ላይ ሲቀርቡ ህዝብ አይናችሁ ላፈር ብሏቸዋልብለው በድፍረት ተናግረዋል። እንዲህ ከሆነ፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ እና አጠቃላይ ፓርቲው ላለፉት ሃያ አመታት የቴሌቪዥኑስክሪን ሴቨርሆነው ያያቸው ህዝብ ምን የሚላቸው ይስልዎታል? “ሳንፈልጋቸው ሃያ አመታቸውእያለ ይዘፍናል ካሉ በትክክል መልሰዋል።

 

እውነቱን ለመናገር ግን አቶ በረከት ኢቲቪን ለማዋረድ ፈልገው ካልሆነ በስተቀረ፤ የአዲስ ነገር ደንበኞች ብቻ ሳይሆኑደመኞችምጭምር አንድ የተስማሙበት ሀቅ አለ። የአዲስ ነገር ጋዜጣ ተወዳጅነት እና ጥልቀት ያለው ትንታኔ አሰጣጥ መንግስትንክውአድርጎታል። ጠላትዎ ክብ ይበል! (እዚች ይቅርታ አድርጉልኝና አንድ ግዜ ቅንፍ ውስጥ ይዣችሁ ልግባ (እኔ የምለው መንግስት በሀገሪቱ ውስጥ አንድ ነገርአሪፍሲሆን ለምንድነው አይኑ ደም የሚለብሰው? የፕሪስ ተቋማት፣ የሙያ ማህበራት፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ትንሽ ብቅ ብቅ ሲሉ እና በህዝቡ ዘንድ ተቀባይነት ማግኘት ሲጀምሩሰይጣን የሆነኩርኩም እየኮረኮመ በአጭር ያስቀራቸዋል። ምክንያቱ ምን ይሆን…? እኒያ የቦረና ሰውዬ ለካስ ወደው አይደለምአሁን አሁን ሳስበው እኛን የሚገዛን ጣልያን ነው እንዴ? እላለሁ!!!” ብለው የተናገሩት። ሰው ለሀገሩ ጥሩ ነገር ሲመጣለት በራሱ ህዝብ ላይ ምቀኛ ይሆናል? ብሎ ማሰብ ከባድ ነው!))

 

የሆነ ሆኖ አዲስ ነገር ጋዜጣም ህዝቡን ፍቅር እንዳስያዘው መንግስታችን ሲረዳ ተሸበረ። ያኔም አዘጋጆቹን በአሸባሪነት ሊከስ ማማሟቅ ሲጀምር ግዜነቄዎቹአዲስ ነገሮች ላጥ አሉበት። እነሆ በሌሉበትም ተከሰሱአሸባሪተባሉ። ዛሬም ጭምር የአዲስ ነገር አዘጋጆች መንግስትን እያሸበሩት ይገኛሉ። ህዝቡም እንዲህ ነው እንጂ እያላቸው ባገኘው አጋጣሚ ሁሉ ተሻምቶ ያነባቸዋል።

 

እናልዎ ወዳጄ አቶ በረከት ኢቲቪን ሊሞልጩት ፈልገው ካልሆነ በስተቀረአዲስ ነገሮች በኢቲቪ ስለቀረቡ ህዝቡ ጠላቸውየሚል ገለፃ ከእርሳቸው አይጠበቅም። በስርአቱ ተፀፅተው ሊያሸሙሩ ፈልገው ነው ብለን እንዳናስብኢሂአዴግ ገና አርባ አመት ይገዛልብለዋል። እኔ የምለው እንዲህ ርስ በርሱ የሚጣረስ ነገር የሚያወሩት ሰውየው የራስ ህመማቸው አልተሻላቸውም እንዴ? ሼኩ መፅሐፉን ቢያነቡት ኖሮ አንጠልጥለው ወደ ህክምናቸው ያደርሱልን ነበር።

 

ይልቅ ወዳጄ የሼኩ ነገር አልገረምዎትምበረከት ህክምናውን አቋርጦ ሲመጣ አንጠልጥዬ እወስደው ነበር።ብለው ተናግረዋል። በነገራችን ላይ አቶ በረከት ስሞን የሚያማቸው ራሳቸውን ነው።ጨለፍየሚያደርገው ይሁን አይሁን እንጃ እንጂ ችግሩ ግን ጭንቅላታቸው ላይ እንደሆነ ሰምቻለሁ። የዚሁ አይነት ህመም ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትራችንም አለባቸው አሉ። (አረ በኔ እና በርሶ ብቻ ይቅር እንጂ እርሳቸውማ አንዳንዴ በሰላም ሀገርጠብያደርጋቸዋል ሲባል ሰምቻለሁ።) ይሄ ነገር የቤት ጣጣ ነው እንዴ? ብሎ መሳለቅ ነውር ነው። ሌሎችም የኢህአዴግ አባላት በተለይ የላይኞቹ የሚያደርጉትን ልብ ብለን አይተናል የሚሉ አንዳንድ ወገኖች፤እንዲህ አይነቱ ህመም ሁሉም ሳይኖርባቸው አይቀርምእያሉ እያወጉ ነው። ታድያ ይሄኔ እኒያ ሼክ ሁሉንም እያንጠለጠሉ ወደ ሀኪም ቤት አልያም ወደዱአቤት ቢወስዱልን ጥሩ ነበር ሲሉ ሰምቻለሁ።

 

ለማንኛውም ወዳጄ የአቶ በረከትን መፅሐፍ አንብቤ አልጨረስኩትም በቅርቡ ከተባረኩት ወዳጆቼ መካከል አንዱ ሙሉ መፃፉን ልኮልኛል እናም አንብቤ የሚወራ ካለው እናወራበት ይሆናል። ሌሎች ጨዋታዎቻችንን በመጨረሻም ላይ እናውጋቸው

በመጨረሻም

ፍትህ

 

ተወዳጇ እና አንድ ለናቱ የሆነችው ፍትህ ጋዜጣ ሰሞኑን መከራዋ በዝቶ ሰንብቷል። አዘጋጆቹ ሲገቡም ሲወጡ፣ ሲበሉ ሲጠጡ፣ ሲቆሙ ሲቀመጡ ያደረጉትን ሁሉ አብረዋቸው የሚያደርጉ ደህንነቶች ተመድበውላቸዋል። ጋዜጣዋም ባልታወቀ ምክንያት ቅዳሜ ትወጣ የነበረውን ዘላ እሁድ በሰንበቱ ወጥታለች።

 

እኔ የምለው ግን መንግስት እንዲህ ለእያንዳንዳችን ደህንነት መድቦ ይችለዋል? ብዬ ስጨነቅ የሰማኝ አንድ ወዳጄ ምን አለኝ መሰልዎ? “መንግስት በአምስት አመቱ ስትራቴጂ ውስጥ ከነደፋቸው ነገሮች አንዱ የሚቃወሙት ለመሰለውን በሙሉ በቂ የሆነ ደህንነት እና ድህነት መስጠት ነው አለኝ!” ጉድ እኮ ነው!

 

በመጨረሻም

ጎንደር

 

በጎንደር ዩኒቨርስቲ ባለፈው ግዜ ተማሪዎች በተበላሸ ምግብ እና ውሃ ሳቢያ ታመው በትምህርታቸው ምትክ ሆስፒታል ተኝተው አሳልፈዋል።እንዲህ አይነት ነገር ነውር ነው!” ያሉ ተማሪዎችም በትምህርት ቤቱ ላይ ቁጣቸውን ሲያሰሙ ቆይተዋል። ታድያ ሰሞኑን ከጎንደር ዩኒቨርስቲ አካባቢ አንድ ዜና ተሰምቷል።

 

ምግብ እና ውሃ ብክለት ማጋጠሙ አዎ ትክክል ነው! ያሉት የትምህርት ቤቱ ተወካይ ነገር ግንየተበላሸም ቢሆን፤ ተበላሸ ብሎ መቆጣት አግባብ ባለመሆኑ ቁጣ ሲያሰሙ ከነበሩት መካከልቀንደኞቹለአንድ አመት ከትምህርት ገበታቸው እንዲገለሉ ተደርጓልየሚል መግለጫ ሰጥተዋል። ይሄኔ አንድ ነገር አስታወሱኝ

 

ነገሩን ዳኛ ብርቱካን ሚዴቅሳ ስታወራው ነበር የሰማሁት።የመንግስታችን ትልቁ ችግር መበደሉ ብቻ አይደለም ተበደልኩ ብለህ ስትጮህ መከልከሉ ነው!” ስትል ሰምቻት አውቃለሁ። እውነቷን ነው። የዚህ አይነት ጨዋታ ከዚህ በፊትም ተጫውተናል። እየደበደቡ አታልቅስ ብሎ መቆጣት የጤና ነው? ጉድ እኮ ነው!

 

በመጨረሻም

ርዕዮት አለሙ

 

መምህርት እና ጋዜጠኛ የነበረችው ርዮት አለሙአሸባሪተብላ ከታሰረች ቆየች። ሰሞኑን ታድያ ፍርድ ቤት ቀርባ ነበር። ፍርድ ቤት ስትቀርብ ጠበቆቿ ካሰቡት የመከላከያ ምስክሮች ውስጥኤክስፐርትየሚባሉ ምስክሮችን ማቅረብ ነበር። አንዲት እሳት የላሰች የህግ ባለሞያ ወዳጄ እንደነገረችኝ ከሆነ፤ (መሆኑም አይቀርም) ኤክስፐርት የሚባሉት ምስክሮች ሙያዊ ምስክርነት የመስጠት ብቃት ያላቸው ናቸው። በሌላው ሀገር እንዲህ አይነቱ ምስክርነት የተለመደ ነው ባይ ናት። ምስክሮቹ ረዳት ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና እና ዶክተር ያዕቆብ ሃይለማርያም ነበሩ። ፐሮፌሰሩ ከፖለቲካ አንፃር የርዮት ክስ የማያስኬድ መሆኑን የሚያስረዱ ሲሆኑ፣ ዶክተሩ ደግሞ ከህግ አንፃር ክሱ ውድቅ መሆኑን ለአቃቤ ህግ ሊያስረዱ ነበርምን ዋጋ አለው! ፍርድ ቤቱአረ ባካችሁልታሳምኑኝ ነው? ወይስ ልታሳምሙኝ?” ብሎ እንቢ አለ (አሁን አሉ በሉልኝ)

 

ይህንን የሰማ አንድ ወዳጄ ታድያ ምን አለኝ መሰልዎ፤ኢህአዴግ እኮ ሀገሪቷን ከቆጣጠረ ቀን ጀምሮ (ከተቆጣጠረ ማለቱ ነው!) ኤክስፐርቶች ሲደውሉለት ስልኩ ጥሪ አይቀበልምአለኝ። ለምን ይሆን ስለው… “ስልኩ የቻይና ነው!” አለኟ! የተቀበራቸሁ የኢህአዴግ አመራሮች ሆይ ይህ ነገር እውነት ነውን? ጉድ እኮ ነው!

 

ይበሉ ወዳጄ ለዛሬ ይበቃናል! ያወጋነውን ለፍሬ ይበለው! እስከ ሳምንት

 

አማን ያሰንብተን!

 

This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ