መለስ ሆይ ፡- ባልተመቸው ሕዝብ ላይ የተመቸው መሪ መሆን እስከ መቼ?
ተመስገን ደሳለኝ
“ክልምኖም ይስምዑኒ!!!”
“(እስኪ ልለምንዎ አንዴ ይስሙኝ)”
…እያልኩ ያለሁት ‹‹አባታችን ሆይ›› አይደለም፤ ‹‹መለስ ሆይ!›› ነው። መለስ ሆይ…(በእርግጥ አንዳንድ የድረ ገጽ ተቺዎች (Sic!) ‹‹ሁልጊዜ መለስ፣ መለስ ትላለህ? መለስ ምን ያድርግህ? ወይስ ከመለስ ወንበር ያየኸው ነገር አለ ወይ?›› ሲሉ ይወቅሱኛል። ምንም እንኳ በባሕርዬ ወቀሳ ተቀባይ እና ጥፋቴን ፈጥኜ የማምን ብሆንም በዚህ በኩል የሚመጣውን ወቀሳ ግን አልቀበልም። አዎ፣ አልቀበልም የምለው እንደወትሮዬ በትሕትና አይደለም። በቁጣ እንጂ! ያውም በታላቅ ቁጣ!! ያውም ገና ተራሮችን ያንቀጠቅጣል ብዬ በማስበው ቁጣ። እናም እደግመዋለሁ፤ እንኳንም ከስንት አንዴ ‹‹መለስ ሆይ›› ማለት ብቻ ሳይሆን እንደ ሠርክ ጸሎት አዘውትሬ ‹‹መለስ ሆይ›› ስል እጮኻለሁ።
በእርግጥ ይህ ጩኸት የእኔ ብቻ አይደለም፤ የሚልዮኖችም እንጂ። ጩኸቱ ልዩነት አለው ከተባለ ተበታትነን መጮኻችን ብቻ ነው። በተቀረ ተሰባስበን የምንጮኽበት ጊዜ ሩቅ ላይሆን ይችላል። …ደግሞስ በኢትዮጵያ ሰማይ ሥር ላሉ ችግሮች ከቶስ ወደማን መጮኽ ይገባል? ከመለስ ውጭ? ስለዚህም በእንተ ሀገር መጮኼን እቀጥላለሁ።)
‹‹መለስ ሆይ!›› ‹‹ክልምኖም ይስምዑኒ!!!›› (ልለምንዎ፤ እስኪ አንዴ ይስሙኝ እንደ ማለት ነው ወደ ፌደራል መንግሥቱ ቋንቋ ስንመልሰው) አዎ! መለስ ይስሙን! ፍትሕ ተዛባብን፤ ኑሮም ተወደደብን፤ ግብርም በዛብን፤ ድህነትም ተንሰራፋብን፤ ሥራ አጥነትም ተትረፈረፈብን። በርግጥ ሥራ አልባ የሆነው ወገኔ ቁጥሩ ከ40 በመቶ እንደሚልቅ በተለያየ ጥናት የታወቀ ቢሆንም የሥራ አጡ ቁጥር ስምንት በመቶ ደረሰ በሚል የአሜሪካ ጎዳናዎችን በጩኸት እየናጡ እንዳሉት አሜሪካውያን ኢትዮጵያውያኑ አልገነፈሉም፤ እመኑኝ ይሄ ግን ዛሬ ነው እንጂ ነገም አይገነፍሉም እንደ ማለት አድርገው አያስቡት!
እናም ይህ ሁሉ የሆነው የዙፋኑ ጌታ በሆኑት በእርስዎ ነው፡፡ ሆኖም እርስዎ የሐላፊነትዎን ያህል አልተረዱትም። ለዚህም ነው ‹‹በቃ›› ማለትን ሳይቀር በሰላማዊ ዜጎች ላይ ቦንብ እንደማፈንዳት ወይም የአጥፍቶ መጥፋት ድርጊት አድርገው የሚወስዱት። በጋዜጣ መተቸትንም እንደ ሽብር ጥቃት ያዩታል። አይተው ብቻም አይተዉት አጸፋውን ይሰጣሉ። ስለዚህም ይህን የፈላጭ ቆራጭነት ሥልጣን ከወዴት ያገኙት እንደሆነ ያስረዱን ዘንድ እንደ ዜጋ ወይም እንደ ግብር ከፋይነቴ የመጠየቅ መብት አለኝና ድምፄን ከፍ አድርጌ ወይም እንደቀድሞው ዐምባገነን ጓደኛዎ ታምራት ላይኔ ግጥም ‹‹ተራራውም ይናድ…›› በሚለው አስገምጋሚ ድምፅ ‹‹መለስ ሆይ…..›› እያልኩ እጠይቃለሁ። ስለገባሪነቴም ማረጋገጫ ካስፈለገ እነሆኝ፡-
ወርኀዊ ደሞዜ ሦስት ሺሕ ብር ነው። ነገር ግን ሦስት ሺሕ እኔ ኪስ የሚገባ አይደለም፡፡ በእርስዎ የግብር ዐዋጅ አስገዳጅነት ከሦስት ሺሕ ብር ደመወዝ አንድ ሺሕ ሰማንያ ብር በወር እገብራለሁ። ኧረ እነጠቃለሁ ብል ይቀላል (የፔሮል ታክስ እና ጡረታ ተብሎ)። በእውነቱ ይሄ ምን ያህል ብዙ እንደሆነ እርስው የተረዱት አይመስለኝም። ዳሩ ነግሠው እንጂ ሥራ ፈልገው ተቀጥረውና ሠርተው፣ ግብር ገብረው የሚያውቁ ስላልሆነ ግብር ሲበዛ የሚፈጥረውን የኑሮ ጫና ሊረዱት የቻሉ አይመስለኝም። …የሕይወት ታሪክዎ እንደሚነግርን፡-
...ሚያዝያ 30/1947ዓ.ም በታሪካዊቷ የዐድዋ ከተማ ተወለዱ። ዕድሜዎ ለትምህርት እንደደረሰም ትምህርት ጀመሩ። አንደኛ ደረጃ፣ ሁለተኛ ደረጃ እያሉም በጥሩ ውጤት አልፈው ዩኒቨርስቲ ገቡ፤ በሕክምና ትምህርት ክፍልም ተመደቡ። ሆኖም በወቅቱ የነበረው የገዥዎች ጭቆና የከፋ በመሆኑ ከጥቂት ጓደኞችዎ ጋራ አልቀበልም ብለው ዐመፁ፤ ትምህርትዎንም አቋርጠው በርሐ ገቡ።
ያው እንደሚታወቀው ደግሞ በበርሐ ግብር መገበርም ሆነ ሥራ መሥራት (በደመወዝ እና በቅጥር) የለም። ያለው ወይ እያነጣጠሩ መተኮስ ነው፤ አልያም አፈ-ጮማ በመሆን ተኳሽ የማብዛት ሥራ ላይ ተመድቦ ‹‹ግፋ በለው›› ማለት ነው። …የማታ ማታ (በርግጥ ይች እንደዋዛ የማታ ማታ የምትለው ቃል አስራ ሰባት ዓመት የፈጀች ከመሆኗም በላይ የምራቸውን አዲሲቷን ዴሞክራሲያዊ እና ጠንካራ ኢትዮጵያ እንፈጥራለን በሚል ብዙ ሺ ከትግራይና ከሌሎች የኢትዮጵያ ክፍላተ ሀገር ያመፁ ወጣቶች ከባድ መሥዕዋትነት ከፍለውበታል) የሆነ ሆኖ ጨቋኙ ደርግ እና ፈላጭ ቆራጩ መንግሥቱ ኃ/ማርያምም ተሸነፉ። ብሶተኛው ኢሕአዴግም ዙፋኑን ተረከበ።
ከዚህ በኋላማ ምኑ ይነገራል? እርስዎ እና ጥቂት ‹‹አስተኳሾች›› በሰማኒያ ሚልዮን ሕዝብ እና በሰማኒያ ብሔር ብሔረሰብ ላይ አዛዥ እና ናዛዥ ሆናችሁ። እናም የተንደላቀቀ ኑሮዎት በደመወዝ ላይ የተመሠረተ ከመሆን ተገላገለ። ለዚም ነው ግብር ከፋይ ሆነው ስለማያውቁ፤ የግብር ጫናን ሊረዱት አልቻሉም ያልኩት፡፡ በዚህም የተነሳ የእርስዎ መንግሥት የግብር ጥያቄ በየዕለቱ ከመጨመሩ እና ከመስፋቱ አንጻር ከእጅ ወደ አፍ ልትባል ከማትችለው ከእኛ ገቢ ጋራ ይኸው ባላንጣ ከሆነ ከራርሟል፡፡ ነገሩም ሀበሻ ሲተርት ‹‹ፈረንጅ! ሲለቀስ የሚዘፈን ይመስለዋል›› እንደሚለው ነው የሆነው፡፡ ርስዎም ከዕለት ወደ ዕለት በግብር ላይ ግብር እየጣሉ ባልተመቸው ሕዝብ ላይ የተመቸው መሪ ሆነዋል።
በአጠቃላይ አስተዳደርዎ በቀድሞ መንግሥታት ጊዜ የነበረውን ችግር ከመፍታት ይልቅ በብዙ እጥፍ አሳድጓቸዋል። ኧረ ለመሆኑ አሁን ስላለው ትውልድ አስበው ያውቃሉ? መቼም በመስቀል አደባበባይ የተሰቀለው ግዙፍ ምስልዎን እና ‹‹ለመጪው ትውልድ ልመናን ሳይሆን ልማትን ነው የምናወርሰው›› የሚለውን መፈክር እንደማያሳዩኝ ርግጠኛ ነኝ፤ ያ መፈክር ነውና። መፈክር ደግሞ በቃ መፈክር ነው። በተጨባጭ ያለውን እውነታ ስናየው ግን የዚህ ትውልድ እጣ ፈንታ የጨለማ መሆኑን ነው። ህፃናት ሱሰኛ እየሆኑ ነው። ሕፃናት እሕቶቻችን ሴተኛ አዳሪ ሆነዋል፤ ገሚሶቹም ‹‹የሞት ሀገር›› እየተባለ ወደሚነገርለት ዐረብ አገር እየሄዱ ለከፋ ሥቃይ ተዳርገዋል። እግዜር ያሳይዎ! ሞት አለበት፣ የሞት አገር ነው እየተባሉም ከኢትዮጵያ ይሻላል በሚል ሲሰደዱ። በእርግጥ የርስዎ እና የድርጅትዎ የአመራር አባላት ልጆች በዐረብ አገሮች ግርድና ተቀጥረው ስለሚሞቱት ወገኖቻቸው የሚያውቁት ነገር የለም። ይሄ እነሱን አያሳስብም። ለምን ካሉ? መልሱ ግልጽ ነው። የአሸናፊዎች ልጆች ናቸውና ነው። ሞትንም ቢሆን የደኃ ገበሬ ልጅ ሲታገል ሞቶላቸዋልና አያሳስባቸውም። ስለዚህም ከዕድሜ አቻዎቻቸው ችግር ገና በጊዜ ነፃ ወጥተዋል። ረጅም ዕድሜ በስማቸው ለሚነገደው ሰማዕታት ይሁንና የትምህርት ቤት ክፍያም አያሳቅቃቸውም። ቤት፣ መሬት የለኝም የሚለው ጭንቀት ለእነሱ አርቲቡርቲ ነው።
ከዚህ ውጭ ያለው አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ግን ‹‹ምን በልቼ? ምን ጠጥቼ?›› ከሚለው ጭንቀቱ ባሻገር ትምህርቱን ከፍሎ የሚማርበት አቅም እንዳይኖረው ተደርጎ ተበጅቷል። ካልተማረ ደግሞ የወደፊቱ ዕጣ ፈንታ ግልጽ ነው። የእርስዎን እና የጓደኞችዎን ተተኪዎቹ እንዲህ እንደዛሬው በጫንቃው ተሸክሞ መጓዝ ነው።… እናም እርስዎ ራስዎት የትምህርት ቤት ዋጋ መወደድን እስከ አሁን አላወቁትም። በርግጥ ልክ እንደ ግብሩ ሁሉ የልጆች ትምህርት ቤትም ስለማያሳስብዎት ነው ችግራችንን የማይረዱት።
እንደሚሰሙት እና እንደሚያዩት ይህ ትውልድ የሚኖረው በቤተሰቦቹ ቤት ነው። የራሱ የሆነ ቤት እና ንብረት የለውም። ስለዚህም ቤተሰብ ሊመሠርት አይችልም። ይህን ደግሞ አርቀን ካሰብነው ተተኪ ትውልድ እስከማጣት ሊያደርሰን ይችላል፡፡ …የዚህ ሁሉ ተጠያቂው እርስዎ ነዎት።
በእርስዎ እና በጓደኞችዎ አሸናፊነት የእኛ ትውልድ ምን ተጠቀመ? ሊነግሩን ይችሉ ይሆን? በግልጽ እንደሚታየው ትውልዱ ‹‹ታገልንልህ›› ከሚሉት ያተረፈው ነገር ቢኖር ሱሰኝነትን እና የምዕራባውያን ጸያፍ ባህል ተከታይነትን ነው። ለዚህም ነው ተጠያቂው በዋናነት እርስዎ ራስዎ ነዎት እያልኩ ያለሁት።
‹‹መለስ ሆይ›› ይመኑኝ በየዶክመንተሪው ፊልም እየቀረቡ ስለኤርትራ የግብር ብዛት መተንተኑ መልሶ የሚጎዳው እርስዎኑ ነው። እስኪ አሁን ‹‹የሽብር አባት›› ፊልም ላይ ያቀረቡት በኤርትራውያን ላይ ግብር ስለመብዛቱ ምን ይባላል? ይህ ብቻ ቢያንስ የእርስዎ ነገር የማይዋጥላቸውን ለብርቱ ጥርጣሬ አይዳርግም ይላሉ? እውነቴን ነው የምልዎት፣ ይህ ያስጠረጥራል። ቆይ…ቆይ…ቃል በቃል በፊልሙ ላይ ያሉትን ላስታውስዎትማ፡-
‹‹የኤርትራ መንግሥት አርሶ አደሩ ካመረተው ምርት እኩል ድርሻ አለኝ ብሎ በዐዋጅ ካወጀ በኋላ አርሶ አደሩ ምርቱን ይዞ ወደ ከተማ እንዳይገባ ማዕቀብ በመጣል፤ የሥርዓቱ ሹሞች አውድማው ድረስ ሄደው ከአርሶ አደሩ እኩል በግብር ስም ይካፈላሉ። አርሶ አደሩም የራሱን ጥበብ ተጠቅሞ እህሉን እያስፈጨ ዱቄቱን ወደ ከተማ ይዞ መግባት ጀመረ። ይህን ጊዜም የኤርትራ መንግሥት ዱቄት ወደ ከተማ እንዳይገባ ማዕቀብ ጣለ። አሁንም አርሶ አደሩ በጥበቡ ዱቄቱን እያቦካ በሊጥ መልክ ማስገባት ጀመረ። አሁንም የኤርትራ መንግሥት በሊጥ ላይ ማዕቀብ ጣለ። …በውጭ የሚኖሩ ኤርትራውያን ላይም ግብር ጥሏል፤ የኤርትራ መንግሥት…›› በኢቴቪ የሰማሁት እንዲህ ነው። ደግሞም የተሳሳትኩ አይመስለኝም!
እስኪ አስቡት! ኢትዮጵያውያን በመኪና ከሚጫን ሊጥ በብዙ ያነሰ ንግድ ላይ ተሰማርተው እንኳ ‹‹ገብሩ›› የሚለው ጥያቄ በዝቶባቸዋል። መንገድ ላይ የጀበና ቡና የምትቸረችር አንዲት ሴት 80 ሺሕ ብር ገብሪ ተብላ ራሷን መሳቷን በአንድ ወቅት ‹‹ወቸው ጉድ!›› የተባባልንበት የኀዘን ወግ እንደነበረ የሚረሳ አይደለም፡፡ ጠላ እና ካቲካላ ቸርቻሪዎች ሳይቀሩ ‹‹የካሽ ማሽን ካልገዛችሁ፤ ውርድ ከራሴ›› የሚል መንግስት መሪ ስለጎረቤት ሀገር የግብር ሕግ አወጣጥ ተቃውሞ ሲያሰማ ግራ አጋቢ ነው፡፡ እንዲያው ስለ አሰብ ወደብስ ምን ይሆን የሚያስቡት? መቼም ዛሬም ‹‹ግመሎቻቸውን ውኃ ያጠጡበት›› የሚለው አቋምዎት ላይ ነዎት ብዬ አላስብም። …የወደብ ግብርን ኢትዮጵያውያን ደሃ ገበሬዎችን አስገድደው እያስከፈሉ ስለኤርትራውያን ገበሬዎች የዱቄት እና የሊጥ ሽያጭ ይመለከተኛል በሚል ሲከራከሩ እያየን ‹‹መለስ ሆይ!›› ብለን ብንጮኽ አያስደንቅም።
ለኤርትራውያን ተቃዋሚዎች እያደረጉ ያለው ድጋፍ ራሱ የሚያስተች ነው፤ ምክንያቱም የኢትዮጵያ ዋነኛ ችግር የጎረቤት አገሮች ጣልቃ ገብነት ሳይሆን የእርስዎ ዐምባገነናዊ አስተዳደር ነው። ለዚህ መፍትሔው ደግሞ በብድር እና ዕርዳታ ከሚሟላ በጀት እየቀነሱ፣ የጎረቤት አገሮችን ተቃዋሚዎች በየክልሉ እየሰበሰቡ፣ አበል እየከፈሉ፣ ቀለብ እየሰፈሩ እያንደላቀቁ ማኖሩ ሳይሆን የሀገር ውስጥን ድምፅ ማድመጥ ነው። ለምሳሌ የእርስዎ ተቃዋሚዎች ‹‹ምኀዳሩ ጠበበብን›› የሚሉትን ተቃውሞ ከብልጣ ብልጥነት በጸዳ ሁኔታ አጣርቶ መፍትሔ መስጠቱ አንድ ነገር ነው። በምርጫ ቦርድ እና በብዙኀን መገናኛ ላይ ያሎትንም አዛዥ ናዛዥነት በሕግ ክበብ ውስጥ ማድረጉ ሌላ መፍትሔ ነው። ለ20 ዓመት ከኖሩበት ሥልጣን መልቀቅም እንዲሁ ጠቃሚ መፍትሔ ነው።
ከዚህም ባሻገር በየዕለቱ በድህነት ወደ ጎዳና የሚወጣው ሕዝብ ቁጥር እየጨመረ ነው። የእርስዎ መንግሥት የሚነግረን ግን የተገላቢጦሹን ነው። ‹‹በደቡብ ረኀብ ተከሥቷል›› የሚል ዜና በውጭ ሚዲያ ሲዘገብ እርስዎ እና መንግሥትዎ ደግሞ ለተራበው ዜጋ ከመድረስ ይልቅ እንዳሻዎት በሚቆጣጠሩት የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ዶክመንተሪ ፊልም አሠርተው ‹‹ደቡብ ጥጋብ ነው›› የሚል ምላሽ ይሰጣሉ። …ጌታዬ! ይስሙኝ ዶክመንተሪ ፊልም ዳቦ አይደለም። ኢትዮጵያውያን እየጠየቁ ያሉት ዳቦ ነው። ዳቦ፣ ዳቦ፣ ዳቦ…
ለዚህም ነው መለስ ሆይ! ‹‹ክልምኖም ይስምዑኒ!!›› አዎ! ይስሙን፤ ፍትሕም እየተዛባብን ነው እያልን ያለነው። ለምሳሌ በቅርቡ ጋዜጠኞቹ ላይ የተፈረደውን ፍርድ አይተውታል፤ አይደለም እንዴ? እናሳ! እስኪ የስዊዲናውያን ጋዜጠኞች እና ኢትዮጵያውያን ጋዜጠኞች ላይ የተፈረደውን ፍርድ አሰላስሉት፤ ደግመው ደጋግመውም አሰላስሉት። የፍትህ ባልደረባ ርዕዮት አለሙ እና ውብሸት ታዬ የሽብር ድርጊት ሊፈጽሙ እና መረጃ ሲሰጡ (ሊሰጡ ሲሉ) ነው በሚል ነው ከየቤታቸው የተያዙት።
ስዊድናውያኑ ደግሞ በቀጥታ ኦብነግ ከተባለው አሸባሪ ድርጅት ጋራ መሣሪያ አንግበው ከኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ጋራ ሲፋለሙ በመከላከያ ኀይል ብርታት ያውም ‹‹በጥይት ቆስለው ተማረኩ›› ነው የተባለው፤ እንደመንግሥትዎ መግለጫ። እንግዲህ በዐውደ ግንባር ውጊያ የተማረከ እና በመንግሥት ት/ቤት በሰላም ተማሪዎችን እያስተማረች ሳለ የተያዘችው ጋዜጠኛ ርእዮት አለሙ ፍርድ ሲነጻጸር የሰማይና የምድር ያህል ነው-ልዩነቱ። ባለክላሾቹ 11 ዓመት ሲፈረድባቸው፣ ባለጠመኔዋ ርእዮት ደግሞ 14 ዓመት እና 33ሺሕ ብር። ይህ እንዴት ሆኖ ነው ፍትሐዊ የሆነው? ምናልባት የተለየ የሕግ ማብራሪያ ካለ ይንገሩን ወይም ጠመኔ ከክላሽ ከበለጠ ያስረዱን?
በተቀረ መለስ ሆይ፡- ‹‹ይስምዑኒ›› ለዚህ ሁሉ ተጠያቂ እርስዎ ነዎት፤ የመሠረቱት መንግሥት ነው፤ የሚከተሉት ጭራ እና ቀንድ የሌለው አብዮታዊ ዴሞክራሲ የሚባለው ፍልስፍናዎ ነው። እናም ሥልጣንዎን ለድርጅትዎ ሳይሆን፣ ለሕዝብ አስረክበው ዴሞክራሲያዊ እና ተአማኒነት ያለው ምርጫ እንዲካሄድ ያድርጉ። ያን ጊዜ ነው ኢትዮጵያ ትንሣኤዋ እውን የሚሆነው፤ አልያ እንጮኻለን። …ማን ነበረች በጩኸት የፈረሰችው ከተማ? ኢያሪኮ ነቻ! እሺ አንድ፤ ሌላስ? ………
ምንጭ፦ ፍትህ ጋዜጣ



