“ጊዜ መስተዋቱ!” ተስፋዬ ገ/አብ ማነው?
(ከወልደሚካኤል መሸሻ)
ውድ አንባቢያን ይህን ጽሑፍ ጀምሬ ያጠናቀቅሁት ወደ እ . ኤ. አ በ2012 መጀመሪያ ነው። ለምን እስከአሁን አቆየኸው? የሚል ጥያቄ መነሳቱ አይቀሬ ነው ታዲያ። ተገቢ ጥያቄ ነው። የተለያዩ አቅጣጫዎችን የማየትና የማሰላሰል ሁኔታ በአንድ በኩል፣ በሌላ ደግሞ በአነሰኛ መጽሐፍ መልክ ባሳትመውስ የሚል አሳብ እየተደቀነብኝ መጥቶ ነው። ሁለቱም ተራ በተራ ተፈታተኑኝ። የትኛውን እንደምመርጥ ማውጣት ማውረዱን ቀጠልሁ። ጽሑፍን እንድያዩትና አሳባቸውን እንዲሰጡኝ ለጥቂት ወዳጆቼ ላክሁ። አንዳንዶቹ ቶሎ ጽሑፉ እንዲወጣ የሚገፋፋ አሳብ ሰጡኝ። አንዳንዶች ከማስጠበቅ ውጭ ላያልፉ ሆኑ። በዚህ ላይ እያለሁ ለጽሑፉ መሠረት የሆነው የእምዬ ጠላት በመርዘኛ ብዕሩ ብቅ ማለቱን ሰማሁ። ወዳጆቹ ከወዲህ ወዲያ እያሉ መሆኑንም አዳመጥሁ። እርሱም የእምዬ ልጆችን የማባላቱን ሥራ ማጠናቀቁን ከወብሳይቱ ተመለከትሁ።
ይህ ሰው በዚህ ሰሞን "ላይፍ" ለተባለ በኢትዮጵያ ለሚታተም መጽሔት በሰጠው ቃለ-ምልልስ ላይ በኢትዮጵያ ላይ ያለውን ጥላቻ ግልጽ አድርጎታል። አማሮች ኦሮሞችን መበደላቸውን በይፋ አምነው ይቅርታ መጠየቅ አለባቸው በሚልና በመሳሰሉት። አልፎ ተርፎም፣ በተለይ በዚያው ዕድሜ፣ የነበራቸውን ትልቅ የኑሮ ዕድል ትተው፣ ለበደልኩት ሕዝብ በአገልግሎቴ እክሳለሁ ብለው፣ አኩሪ ገድል እያከናወኑ ያሉትን ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ላይ ክፉኛ ታስልቆባቸዋል። "ነጋሶ ጭንቅላታቸውን ተናግረው አያቁም።" በማለት። አንዳንድ አንድነት ምን እንደሆነ ብዥብዥታ ያላቸውን ኦሮሞችን ያስደሰተ መስሎት ስብዕናቸውን በዚህ ዓይነት ለመንካት ሞክሮአል። አንጀት የሚያቆስል ነው።
እንዲህ ሰውዬው የሚቀበዘበዘው፣ ለሌላ አይደለም። የመጽሐፉ አሻሻጭ ለማመቻቸት ነው። እንዲያውም በዚህ ሰሞን እዚህ አምስተርዳም ያሉት የኦሮሞ ማህበረሰባችን አንድ ስብሰባ እንዲያዘጋጁለት አድርጎ በመገኘት አማሮች በኦሮሞ ሕዝብ ላይ የሰሩትን ግፍ አምነው መቀበል አለባቸው። ይህ ግድ የሚል ነው በሚል ደስኩሮ ተመልሶአል የሚል ወሬ ሰምቻለሁ። ተስፋዬ መቼም ኢትዮጵያ የምትባል አገር ደብዘዋ ሳይጠፋ ላይቀመጥ የማለ ይመስላል።
እናም፣ ግራ ቀኙን የማየቱን አስቆመኝ። በእምዬ ኢትዮጵያ ላይ በሥውር ጨበጣ መሰርሰሩን ከሚቀጥል ምናልባትም በኔ በልጇ ላይ ቢቀጠል ይሻላል ወደ ሚል ቁርጠኛ ውሳኔ ላይ ደረስሁ። በሽቷን ከማይ፣ ሞቷን ከማይ ሞቴን እመርጣለሁም አልኩ። እናም እንዲወጣም ወስንሁ።
መግቢያ፣
“ሰውን ውደደው እንጅ አትመነው” የሚል የጥንት የአበው አባባል አለ። ግራ የሚገባኝ አባባል ነው ለእኔ። ከወደድኩት እንዴት አላምነውም የሚል ጥያቄ በአእምሮዬ እያመላለሰብኝ። መቼም እየጠሉ ማመን የሚባል ነገር ከቶም ይኖራል ብሎ ማሰብ መኖሩን እጠራጠራለሁ። በዚያው መጠን ደግሞ በመካከላቸው አንዳች ነገር እስካልተከሰተ ድረስ፣ እየወደዱ ያለማመን ነገር እንዴት እንደሚኖር ማሰብም ያስቸግረኛል። ምናልባትም ያልጠረጠረ ተመነጠረ ዓይነት ለማለት ከሆነ ያስኬድ ይሆናል። አዲስ ሰው ስትቀርብ እየተጠራጠርህ ሊሆን ይችላል። አስቀድመህ አታውቀውምና። ትናንት ጠላትህ የነበረ ዛሬ ወዳጅህ ሊሆን ይችላል። ከወደድከው እስከሚመችህ ድረስ ታምነዋለህ። ለስሜት ሳትበገር ሰከን ካልክ በጉዞ ላይ ትፈትነዋለህ፣ ታየዋለህ። እውነቱ ላይ ደርሰህ ማንነቱን ትለየዋለህ። የብልህ ተግባር እንዲህ ነውና።
ዳኛ በተለይም በወንጀል ተከሶ የሚቀርበውን ተከሣሽ፣ ምንም ዓይነት የወንጀል ሪኮርድ ቢኖረውም፣ ምናልባትም ክስ ቀርቦበታልና በጥርጣሬ ከመመልከት ውጭ ወንጀለኛ አድርጎ አያየውም። ፊቱን አይቋጥርበትም። አያስፈራራውም።
አያስበረግገውም። ማንም በወንጀል ድርጊት የተከሰሰ ሰው በሕግ ወንጀለኛ ተብሎ እስከአልተፈረደበት ጊዜ ድረስ እንደ ንጹህ ሰው ሆኖ ይቆጠራል (Every one charged with criminal offence shall be presumed innocent until proved guilty according to law.)፣ ወይም (Presumption of Innocense) የምንለው ዓለም-አቀፍ ተቀባይነት ካገኘው የፍትህ ቃል አነጋገር በመነሳት። እኔ ዳኝነት ስጀምር፣ የችሎቱ ሰብሳቢ የነበሩ ሰው አንድ ተከሳሽ፣ በተለይም በሌብነት ወንጀል የቀረበን እችሎቱ ሲያነጋግሩ ትንሽ ሳት ካደረገ አልቀለት በቃ። “ፊትህ ራሱ ሌባ ይመስላል” ከሚል አነጋገር ጀምሮ ይወረዱበታል። አስቀድሞ የወንጀል ሪኮርድ ካለበትማ ማቆሚያ የላቸውም። ይዘህ ከወጣኸው ትምህርትና እውቀት ጋር ይጋጭብሃል ታዲያ። ከስብዕናም አመለካከት ውጭ ነውና ለእኔ እጅግ አስደንጋጭ ነበር በወቅቱ። የኋላ ኋላ ግን ይህንና የመሳሰሉ አነጋገራቸውና አመለካከታቸውን በትግል ከሌሎቹ ሁለት የችሎቱ ዳኞች ጋር ሆኜ አስቆምኳቸው። ለነገሩ ሰውዬው በንጉሡ ዘመን በፓርላማው አማካይነት ካላቸው የሕግ ሰርትፊኬት ጋር እንዲህ ዓይነቱን ገደብ የለሽ ልምድ ከነበረው ሥርዓት አዳብረውት ስለመጡና ሃይ የሚል ሰው በመጥፋቱ ነው ይዘው የቆዩት ለማለት ይቻላል።
ሦስት ዳኞች ወይም በሰበር ችሎት አምስት ዳኞች እንደተመደቡ በመጀመሪያዎቹ ውስን ጊዜያት ሥራዎችን የሚያከናውኑት እርስበርስ በጥርጣሬ እየተያዩ ነው። አንዱ አጥንቶ ያመጣውን የአንድ ጉዳይ መዝገብ ላይ ሲወያዩ አሰልችና አጓጉል ጥያቄዎች ይጎርፉለታል። መዝገቡን ሰርቶ ለፊርማ ሲያቀርብም እናነባለን በሚል ጊዜያት ይወሰዳሉ። ውሎ እያደር ሲሄድ ግን አጥኚው ዳኛ ነጥቦቹን አስረድቶ ሲጨርስ ምን ይመስለሃል? የሚል ጥያቄ ይቀርብና አስተያየት ተሰጥቶበት በዚህ መልክ ሥራው ተብሎ ይታለፋል። አጠናቅቆ ሲያቀርብም እንደመጀመሪያዎቹ እናምብበው በሚል የጊዜ መፍጀት ነገር አይኖርም። ወዲያውኑ ፊርማቸውን ማሳረፍ ነው።
ሰዎች መዋደድ ላይ ደርሰውም፣ መተማመን ላይም ደርሰውም ውሉ የሚላላበት ሁኔታ የመፈጠሩ ዓይነት በፍ/ቤትም ይከሰታል። በዚህ በኩል አንድ ምሳሌ ጠቀስ ላድርግ። ወደ 1995 (2001) ላይ ይመስለኛል አንድ አስደንጋጭ ነገር በፌዴራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ላይ ተከሰተ። ሦስት ዳኞች ያሉበት ችሎት ነው። በወቅቱ እኔ የጠቅላይ ፍ/ቤት ዳኛ ነበርሁ። ጉዳዩ የቀይ ሽብር ጉዳይ ነው። ብዙ ተከሳሾች የሚገኙበት ነው። እንደተለመደው አንዱ ዳኛ የመዝገቡን ጉዳይ አጥንቶ ለሁለቱ ያቀርባል። ተወያዩበትና የተወሰኑት እንዲለቀቁ፣ የተወሰኑት እንዲከላከሉ ብይን ሰጥቶ እንዲያቀርብ ሁለቱ ይነግሩታል። እርሱም ተስማማበት። ዳኞች እርስበርስ መተማመን ላይ የደረሱበት ችሎት ስለነበር፣ በማግሥቱ እንደተነገረው ሰርቶ ማቅረቡን ዳኛው ሲነገራቸው፣ ሁለቱ ዳኞች በቀጠለው እምነት መሠረት ፈርማቸውን ያሳርፉበትና እችሎቱ ይሰየማሉ። እችሎቱ አዘጋጅው ዳኛ ብይኑን ሲያነብ ሁሉንም ከክሱ ነጻ አድርገን በዛሬ ቀን ለቀናል የሚል መደምደሚያ ያሰማል። ሁሉም ተከሳሾች በደስታ ይፈነድቃሉ። ሁለቱ ዳኞች ግን ሃዘን ውስጥ ይገባሉ። ከእምነታቸውና ከቃላቸው ውጭ የተሰራ ነገር በመስማታቸው።
ጉዳዮቹ ተስተናግደው ሳያልቁ፣ ሁለቱ ዳኞች ችሎቱ እንዲቋረጥ አድርገው ሁሉም ወደ ጽ/ቤት ይገባሉ። ጽ/ቤቱ ወደ አምባጓሮ ይለወጣል እንደሰማነው በወቅቱ። ከዚያም ለፍ/ቤቱ አስተዳደር ማለትም ለፕሬዚዳንቱ ይቀርብና ዳኛው ወዲያውኑ ከሥራው ይታገዳል። በወንጀል ጉዳይ ፕሬዚዳንቶች ውሳኔዎችን ማገድ ስለማይችሉ ውዲያውኑ ዐቃቤ ሕጉ ለፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት ይግባኝ ብሎ የእግድ ጥያቄ እንዲያቀርብ ይደረጋል። ቀውሱ በዚህ ዓይነት ተስተካከለ። ዳኛውም በዳኞች አስተዳደር ጉባኤና በተወካዮች ም/ቤት ውሳኔ ከሥራው ተባረረ። በኋላ ግን ይህ ዳኛ በቅንጅቶች ጉዳይ የሽመልስ ከማል ምክትል ዐቃቤ ሕግ ሆኖ በተሰጠ የምሽት ሹመት ብቅ አለና ጉድ አሰኘን። ሁሉ ነገር በወያኔ የተገላቢጦሽ አይደል?
እንደየሁናቴው ሰዎች በአብሮ መኖር ዙርያ ላይ እርስበርስ ይዋደዳሉ፣ ይተማመናሉ፣ ይጣላሉ፣ ይታረቃሉ። ሁሉንም ይሆናሉ። የሰው ልቦናው ተገልጦ አይታይም። ግን በሂደት እየተፈተነ ይጋለጣል፤ ይታያልም። ከርቀት ሰውን መገደብ፣ ስለትናንት እያነሱ ወደ ግድግዳ ማስጠጋት፣ ዛሬን መርሳት ይሆናል። ትናንት ዛሬ አይደለምና። ዛሬ ሌላ ነውና አጉል አካሄድ ነው። በስሜት ፈረስ ላይ መፈናጠጥ ስለሆነ። ታዲያም ጉዳት አለው። ከቶ ላያመልጠን ችኮላው ለምን? እናም ሰውን እንደአመጣጡ እንቀበለው። እንይው። እንፈትሸው። ጠላትን ከማብዛት ወዳጅን ማብዛት ሳይሻል አይቀርምና። እናም፣ ዛሬ ባናገኘው ነገ ለምናገኘው ምን ያስቸኩለናል?
እምዬ ኢትዮጵያን አምላክ እንደሚጠብቃት በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ተመልክቶ ይገኛል። እምዬ አገራችን በየወቅቱ ከውስጥም ከውጭም ፈታኝ ጠላቶች አልጠፏትም። የጡት ነካሾቿ ደግሞ ይብሳሉ። በርሳው ተወልደው፣ እትብታቸው ተቀብሮባት፣ አድገው ለቁም ነገር የበቁት ዛሬ ክዷት፣ ሊያጠፏት ጉድጓድ ሲቆፍሩ ማየትና መስማት የተለመደ ሆኖአል። ይህ ደግሞ ሕሊናን የሚያደማ፣ የሚያቆስል ቸነፈር ነው። ግና ምን ያደርጋል እንዲህ ዓይነት ሰዎችና ድርጊቶች ትናንት የነበሩ፣ ዛሬም ያሉ፣ ነገም የሚኖሩ ናቸው። ታዲያም ምንም ያህል ቢሯሯጡ፣ ምንም ያህል ቢሰባበሩ እምዬ የወላድ መካን አልሆነችም ፤ አትሆንምም፤ አላትና አንድዬ። እንዲህ እያልክ ወዴት ልትወስደን ነው? ምን ልትለን ነው? ሳትሉኝ እንደማትቀሩ ይሰማኛል። ጊዜው ደረሰና አንድ አፍጥጦ፣ አግጦ ስለወጣ ቁም ነገር ልተርክላችሁ ዕድል አግኝቼ ነው። ምንድነው እሱ? ልትሉኝ ነው ቀጥሎ። እሱንማ ከጽሑፉ ታገኙታላችሁ ይሆናል መልሴ። እናም፣ ተከታተሉት ውድ የኢትዮጵያ ልጆች።
ክፍል 1.
ጊዜ ደጉ!
ያ ቀን ሲደርስ፣ ጎሁ ሲቀድ፣ ሌቱም ሲነጋ ማንም፣ ምንም መጋለጡ አይቀርም። ክፉ ሥራው በክፋቱ፣ ደግ ሥራው በደግነቱ ይታያል። ጊዜ ማስጠንቀቂያ የለውም። ራሱን በራሱ ሁሉም እንዲፈትሽ ገደብ የለሽ መብት ግን ይሰጣል። ላወቀበት ጊዜ ኩራት ነው። ላለወቀበትና ለታወረው ጊዜ ማፈሪያው፣ መሸማቀቂያው ነው። ጊዜ ቀኑን ጠብቆ ብቅ ባለ ሰዓት ይቅርታ የለውም። አጋልጦ እንደጅብራ አቆሞ ማሳየት ነው። በክፋት ታውሮ የሰራው ተንኮል ከተፍ ሲልበት አይ ጊዜ ክፉ ሲል፣ ተሸሽጎበት የነበረው እውነት ብቅ ያለለት ደግሞ አይ ጊዜ ደጉ! ይልና ይጽናናል። ቀደም ብሎ ወደ እ.ኤ.አ በ2008 ላይ፣ “ለሁሉም ጊዜ አለው” በሚል ርዕስ የፌዴራል ፍ/ቤቶች ሲያምስ የነበረው የፍ/ቤቶቹ አስተዳዳሪ ተብሎ ተሹሞ የነበረው ሰው ቀኑ ደርሶ በይፋ መጋለጡን ምክንያት በማድረግ አንድ ጽሑፍ አቅርቤ እንደነበር ይታወሳል። እውነትን በጊዜ ስለአየሁ። ዛሬ ደግሞ “ጊዜ! መስተዋቱ!” በሚል ርዕስ አንድ አነስተኛ ጽሑፍ አዘግጅቼ ይዤ ቀርቤአለሁ።
ለነገሩ እኔ ከአገር ከወጣሁ በኋላ ተሸሽገው የነበሩ የፌዴራል ፍ/ቤቶች እውነቶችን እየሰማሁ ነው። መቆየት ደግ ነው። አንድ ለአብነት ያህል ባነሳ። ከካቻምና ወዲያ2010 አጋማሽ ላይ አንድ ዜና ከኢትዮጵያ ፍ/ቤቶች ወጥቶ በወብሳይት ላይ አነበብሁ። በተለይም በአራጣ አበዳሪዎች ላይ የተሰጠ ፍርድ። ውሳኔ የተሰጠባቸውን ዝርዝር እንደአየሁ አሁንም ለራሴ ወይ ጊዜ!! አልኩ። ይዘገያል እንጅ እውነት ተቀብሮ እንደማይቀር ዳግመኛ ሰማሁ። ነገሩ እንዲህ ነው ታዲያ። ከተወሰነባቸው መካከል አንዱ አቶ ሌንጫ ዘገየ የተበለው አራጣ አበዳሪ ነው። እኔ ነገረ-ፈጅ በነበርኩበት ወቅት ወደ ፍ/ቤት ብቅ ስል ይህን ሰው ተመልከተው። ምድረ ሀብታምን ያጠበ፣ ያሽመደመደ ሰው ነው። የዋዛ አይምሰልህ። እጅግ ሀብታም ነው በአራጣ አበዳሪነቱ። ጊዜ አዳልጧቸው በርሱ እጅ የወደቁ ያለቅሳሉ ሁሌ፣ ይከሱታልም ሁሌ። እርሱ ግን አልተቻለም። በርሱ ላይ የማይፎክር ዳኛ የለም። ግን ያገኘው የለም እያሉ ጓደኞቼ ይነግሩኛል። ለምን አያገኙትም? ለምን ይሆን? እያልሁ እነዚያን የነገሩኝን ስጠይቅ የተጨበጠ መልስ የላቸውም። ሰውዬው በዓይን ሲታይ ደሞ ያለው አይመስልም። ግራ የሚያጋባ ነበር።
በዚህ ላይ እንዳለ፣ በኢ . አ በ1986 ዓ.ም በዳኝነት ተሹሜ ወደ ፍ/ቤት ገባ አልኩ። በ1988 ግንቦት ላይ የፌዴራል ፍ/ቤቶች እንደ ተቋቋመ እየተገለባበጠ የመጣ አንድ ትልቅ ፋይል ገጠመኝ። ከሳሽ ዐቃቤ ሕግ፣ ተከሳሽ ሌንጫ ዘገየ የሚል። ያ ሰው ይሆን እንዴ? ብዬ አሰብሁ። መዝገቡን ከፈት አድርጌ ሳነበው ነገሩ ከአራጣ ጋር የተያያዘ የወንጀል ድርጊት የሚል በመሆኑ፣ እርሱ መሆኑን ተረዳሁ። የልቤ ምት ጨመር ማለቱ አሁን ትዝ ይለኛል። ምክንያት? ውጭ ሆኜ እንደሌሎቹ እንዴት? ለምን? በሚል እንደመፎከር ዓይነት ብዬ ስለነበር እኔም እዚያው ውስጥ እንዳልገባ ፍርሃት፣ ፍርሃት ብሎኝ ይመስለኛል። ግና አጋጠመኝ።
እናም የሌንጫን መዝገብ ስመለከተው፣ ማስረጃ ሳይሰማ ለዓመታት እየዘለቀ የመጣ ነው። ምክንያቱ አይታወቅም። የቀረበውን የማስረጃ ዝርዝር በመጀመሪያ ዳሰስሁ። ይዘቱን በአጭሩ ዘርዘር አድርጌ መዝገቡን እንደምሰራው ለሌሎቹ ሁለቱ ዳኞች ነገርኳቸው። እነርሱም ተስማሙ። እናም፣ ሰከን ብዬ ወደ እልህ ገባሁ። ቢሆን በዚህ ምታሃተኛ ሰው ላይ ፍርድ ለማሳረፍ፤ ባይሆን ያው እንደቀድሞቹ ፎከራዬ በአጭሩ እንዲጠናቀቅ ለማድረግ። አጭር ቀጠሮ ሰጥተን በመጀመሪያ ዐቃቤ ሕግን፣ ቀጥሎ የተከሳሹን የሌንጫን ማስረጃዎችን ሰማን። 43 ገጽ የወሰደ የውሳኔ ትችት ጽፌ ለመጀመሪያ ጊዜ ሌንጫ ላይ በአራጣ ወንጀል የጥፋተኛነት ውሳኔ ተሰጠበት። በማግሥቱ በአምስት ዓመት ጽኑ እሥራት ፍርድ ተሰጥቶበት ወደ ከርቸሌ ማረሚያ ቤት እንዲገባ የተዛዘበት ትዝ ይለኛል። ጉድ ተባለ። በችሎቱ የነበሩና ጉዳዩን ይከታተሉ የነበሩ የሌንጫ ተጠቂዎች በወቅቱ ስሜታቸውን መቆጣጠር አቅቷቸው ዛሬስ ላንተ ዳኛ ተገኘ? እያሉ ቀና ብለው ለአምላክ ምስጋና እያቀረቡ መውጣታቸውም ትዝ ይለኛል።
ሌንጫ ዘገየ ለፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት ይግባኝ ይጠይቃል። ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቤትም ይግባኙን ተቀብሎ ካከራከረ በኋላ የኛን ውሳኔ ሽሮ ሌንጫን በነጻ ለቀቀው። እናም ውሳኔው የሦስት ዳኞች ቢሆንም፣ የሰራሁት እኔ ስለነበርሁ ቂም ሌናጫ በእኔ ላይ እንደያዘና እንደሚፎክርብኝ ሰማሁ። መቼም ከፍተኛ ፍ/ቤት ውስጥ አይጠፋምና ዓይን ለዓይን ስንተያይ ኮምጨጭ እንደሚልብኝ አስተውል ነበር። በመሰረቱ በወንጀልም ሆነ በፍትሐብሔር አንድ ውሳኔ በተሰጠ ቁጥር፣ ውሳኔውን የሰጠው፣ ወይም የጻፈው ዳኛ አንድ ቂመኛ አያጣም። ዳኝነት ስይዙት ከስሙ በላይ ከባድና አስፈሪ ነው። እንደየግለሰቡ ሕሊና መለያየቱ እንደተጠበቀ ሆኖ፣ በዳኝነት ሁሌ መጨነቅ፣ ሁሌ መጠበብ፣ ሁሌ በጉቦና በአድልዎ መጠርጠር የተለመደ መሆኑ የታወቀ ነው። እውነተኛና በራሱ የሚተማመን ዳኛ ግን ለእንዲህ ዓይነቶች አይበገርም።
በወቅቱ አስገራሚው የሌንጫ እኔን እንደባላንጣው አድርጎ መከታተሉ አልነበረም። ጠቅላይ ፍ/ቤቱ ውሳኔውን የሻረበት ምክንያት ወይም ትችት እንጅ። “አሁን መንግሥት በሚከተለው ነጻ ኤኮኖሚ መሠረት ሰዎች በማንኛውም የንግድ ዘርፍ መሰማራት ይችላሉ። ስለዚህ ሌንጫ በአራጣ አበዳሪ ዘርፍ ተሰልፎ እያበደረ ቢሰራ ወንጀል ሊባል አይችልም።” በሚል” የሰጠው መንደርደሪያ።
አገራችን የምትከተለው የኮንትኔንታል (ሲቪል) ሕግ ዘርፍ ነው። በዚህ መሠረት ዳኞች አስቀድሞ በሕግ አውጭው የወጣን ሕግ ነው የሚተረጉሙት እንጅ ራሳቸው ሕግ ሽረው፣ ሕግ አውጭ መሆን አይችሉም። ሥልጣን የላቸውም። የወቅቱ የጠቅላይ ፍ/ቤት ዳኞች ሌንጫን ከወንጀሉ ነጻ አድርገው የለቀቁት ትርጉምም የማያስፈልገውን በግልጽ የሚናገረውን የወንጀልና ተያያዥነት ያለውን የፍትሐብሔር ድንጋጌ የሻረ ነው። በወቅቱ ለካስ ሌንጫ ያልተቻለው በጤናው አይደለም አልንና አዘንን። በጊዜው የዳኞችን ውሳኔ የሚመረምር አካል አልነበረም። አሁንም ያለ አይመስለኝም። ጠቅላይ ፍ/ቤት የሚሰጠው ውሳኔ የመጨረሻ በመሆኑ ሌንጫም በድል ፈረስ ላይ እንደገና ተፈናጠጠ። ለማዳን ከሕግ ውጭ ተፈልጎ በተገኘ ምክንያት። ውሳኔውን የሻሩት የጠ/ፍ/ ዳኞች መስፍን ገ/ሕይወት የሕግ ትምህርት ቤት መምህሬ የነበረና ወደ 92 ዓ.ም አከባቢ ከዚህ ዓለም በሞት የተለየ፣ ፈጠነ ወንድሙ እስከወጣሁ ድረስ ጠበቃ የነበረ፣ አንድ ስሟን የዘነገኋት የሴት ዳኛ ነበሩ። ግና አሁን መንግሥት ለፖለቲካ ፍጆታ ሳይሆን አይቀርም ብዬ እገምታለሁ፣ ጊዜው ደረሰና በእርጅና እድሜው ሌንጫ አምና በዚሁ በአራጣ ወንጀል ተፈርዶበት ወደ እስር ቤት ገባ። “ሁሉም ነገር ጊዜውን ይጠብቅለታል” ዘፋኙ ብሎ የለ። እናም ገረመኝ።
በዚሁ ወደ ተነሳሁበት ርዕስ እንግዲህ ልግባ። ሌላ አስገራሚ እዚሁ ሳይበሩ ከዳኝነት ቋት ውጭ አጋጠመኝ። የወያኔ አባላት የነበሩም ሆኑ፣ ከወያኔ ጋር ይሰሩ የነበሩ፣ በብዛት የሥርዓቱን እኩይ ተግባር በማውገዝ ወደ ሕዝባችን በአገር ቤት የተቀላቀሉ፣ ወይም ወደ ውጭ የወጡና የውጭውን ማህበረሰብ የተቀላቀሉ፣ አለዚያም አፋቸውን ዘግተው የተቀመጡ አሉ። በአንጻሩ ደግሞ በተቃዋሚነት ጎራ ተደራጅተውም ሆነ በተናጠል ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ግለስቦችም በነጻና በሰላማዊ መንገድ መንቀሳቀስ ባለመቻላቸው ወደ ውጭ ተሰደው ይገኛሉ። ከነዚህም ውስጥ በብዛት የነጻው ፕሬስ አባላት ይጠቀሳሉ። እንደዚህም የመንግሥት ጋዜጠኞችም ይገኙባቸዋል።
በአገር ቤት ውስጥ የነጻው ፕሬስ ጋዜጠኞች የወያኔ መንግሥትን እኩይ ተግባር በየጊዜው በማጋለጥ እጅግ አኩሪ ታሪክ ሰርተዋል። ብዙዎችም ዋጋ ከፍለዋል። ለስደትም ተዳርገዋል። አብዘኛዎች የቀድሞውን ተግባራቸውን ያለመታከት ቀጥለዋል። አንዳንዶች በአገር ቤት ያሉት ዓይናቸውን ወደኋላ ላያዞሩ ሆነው ለመከራ ስቃይ እየተዳረጉ ይገኛሉ። የሽብርተኝነት ታርጋ የተለጠፋባቸው እንደነ እስክንድር ነጋ የመሳሰሉትን መጥቀስ ይበቃል።
በሌላ በኩልም፣ ከመንግሥት ሚዲያዎች ለቀው ከተሰደዱት አብዘኛዎቹ እንደዚሁ ሥራ ላይ በነበሩበት ወቅት ባይችሉም፣ አሁን ካሉበት ነጻ ቦታ ለሕዝባችን የተቻላቸውን አገልግሎት እያበረከቱ ይገኛሉ። በዚህ በኩል በቪ.ኦ.ኤ እና በጀርመን ሬዲዮ በአማርኛው ክፍል፣ እና በኢሳት ውስጥ የሚሰሩትን ኢትዮጵያዊያን ጋዜጠኞችን ልንጠቅስ እንችላለን።
አንድ ሰው በነበረበት መንግሥት ሥራ ውስጥ ባለበት ወቅት አውቆም ሆነ ሳያውቅ ጥፋቶችን ሊፈጽም ይችላል። ዋናው ቁም ነገር ግን በነበረበት ቦታ የሰራውን፣ እየተሰራ የነበረውን መጥፎ ወይም እኩይ ተግባራትን ተረድቶ በመላቀቅ የበደለውን ሕዝብ ለመካስ ወደ ማገልገሉ ከመጣ እሰዮ ብሎ መቀበል ተገቢ ይመስለኛል። እናም በሥራው ይፈተናል። ይመዘናል። ካለው ባሕርይ፣ ወይም ይዞት ከመጣው ዓላማ የተነሳ ፈተናውን ሊያልፍ አይችል ይሆናል። ክትትል ማድረጋችን ስለማይቀር ስንደርስበት ማጋለጥ ደግሞ ተገቢ ነው። ይህ አካሄድ ያለና ወደፊትም የሚኖር ክስተት ነው።
እናም ወዴት ነው ነገርህ? ትሉኝ ይሆናል። እንዲያው ለተነሳሁበት ጽሑፍ የመንገድ ጥርጊያ ዓይነት ነው እንጅ ጉዳዬ ከወያኔ ጉያ ወጥቶ ስለተቀላቀለን አንድ ደራሲ ነኝ ባይ ነው። በአገር ቤት የወያኔ መንግሥት በሚያዘው ሚዲያዎች ውስጥ በሃላፊነት፣ ከዚያም የወያኔ መንግሥት አታሚ ድርጅትም ሥራአስኪያጅም ሆኖ ሰርቶ ስለነበር ደራሲ ነው። መቼም ጊዜ ደግ ነው። ደረሰና ስለደራሲው የቀድሞ ሥራውን ከአሁኑ ጋር እንዳሳይ ዕድል ሰጥቶኝ ብቅ ልል ቻልሁ።
ትንሽ ቆሎ ይዞ ወደ አሻሮ።
ትንሽ ቆሎ ይዞ ወደ አሻሮ. . . ይሉታል አበው ሲተርቱ። በግርድፉ ትንሽ ዕቃ ወይም ነገር ይዞ ወደ ብዙ መጠጋት ለማለት ተፈልጎ ሲሆን፣ ግን ውስጠ-ምስጢሩ ብዙ ለማግኘት ትንሽ ግን ስሜት የሚነካ፣ አንጀት የሚበላ ነገር ይዞ ወደ ብዙ ሚገኝበት ጠጋ የሚለውን ለመነካከት ያህል የሚነገር ዘይቤ ይመስለኛል። ደግሞም “ትግላችን አስቸጋሪ፣ መንገዳችን ጠመዝማዛ ነው” የሚል አነጋገር እሰማ የነበረው በዘመነ-ደርግ ነው። ኮሙኒዝምን ለመገንባት ደርግ በተነሳሳበት ወቅት ካጋጠመው ውስብስብ ሁኔታ ተነስቶ ይመስለኛል ይህን አባባል ያወርደው የነበረው። ወደ ግቡ ለመድረስ እልህ አስጨራሽ እንቅስቃሴና ትዕግሥት ያስፈልጋል ለማለት። ደርግን የተካው የአሁኑ የወያኔ መንግሥት፣ “ነፍጠኛ”፣ “የብሔረሰቦች እኩልነት”፣ “በመፈቀቃድ አንድነት”፣ የራስን ዕድል በራስ እስከመገንጠል” በሚሉ እኩይ ቅመራና
አነጋገሮች ሕዝባችን እርስበርሱ ተማምኖና ተከባብሮ እንዳይኖር ያመጣብን ጣጣ እንዲህ በቀላሉ የሚነገር አልሆነም። ስለሆነም፣ ይህ መንግሥት የያዘውን መንገድ ለማስለወጥ ወይም ራሱን ለማስወገድ የሚደረገው ትግል አስቸጋሪና ጠመዝማዛ ሆኖ እየታየ ነው። ለዚህም ምክንያቶቹ ብዙዎች ይሆናሉ። ወያኔ በቀጥታና በሾሪኒ የሚሰራቸው እንደተጠበቀ ሆኖ፣ አስመሳዮችና አድርባዮች፣ አይሰሩ ወይም አያሰሩ ሰዎች፣ ግለሰቦች የሚፈጥሩት፣ የሚያወርዱት ናዳ እና ያልታሰቡ ውስብስብ ሁኔታ የመሳሰሉ።
በተለይ ከወያኔ ጉያ ወጣ ሲሉ አንዳንዶቹ የበግ ለምድ ለብሰው ይገቡብናል። እነርሱ የሚፈጥሩት፣ የሚቀምሩትና የሚቀብሩብን ፈንጅ ከሁሉም በላይ አደገኛ ነው። ግን ውሎ አድሮ ካልሆነ በስተቀር፣ ወዲያውኑ አይገባንም፣ አንደርስባቸውም። እንደዚህ ዓይነት ሰዎች ዓላማቸውን ለማሳካት በተቀናጀ መልኩ ይዘው የሚገቡብን በሬት የተለወሰ ማር ቀላል አይደለም። መጀመሪያዉኑ በከፍተኛ ጥናት፣ ስትራተጅክ የሆነ ፕላን ነድፈው ስለሆነ። የሕዝብ ስሜትን ኰርኰር በማድረግ ጠጋ ይሉና የከፍተኛ ፖለቲካ ቀማሪዎችና አዋቂዎችን ልብ ጭምር ይሰርቃሉ። በቀላሉም የሚደረስባቸው ስለማይሆኑ በማህበረሰቡ ውስጥ የሚረጩት መርዝ እንደዚሁ ቀላል አይደለም። እንዲህ መሰል ሰዎች ገባ ሲሉብን፣ ስሜትን ተቆጣጥሮ፣ በሰከነ አእምሮ ሁኔታዎችን ማየትና መገምገም ብልህነት ነው። ሁሉን እንደወረደ ከመቀበል ጎን ለጎን መጠርጠር ያስፈልጋል። ከዚያ ጉያ ወጥተው እስከመጡ ድረስ ልንጠረጥራቸው የሚያስችለን መነሻ ይኖረናልና። ክትትል ማድረግ ክፋት የለውም። ቢያንስ እንዴት? ለምን? የተሰኙትን ጥያቄዎችን እያነሳን ወደ ጫፍ ሊያደርሱን የሚችሉ መልሶችን ከእይታችን ጋር አዛምደን ልናገኝ እንችላለን። እናም ጥንቃቄ ማድረግ ለጥሩ ውጤት መዳረሻ ይሆናል።
ወጣቱ የቅንጅት ትንታግ፣
እቤትህ ልመጣ እችላለሁ?
ወደ የካቲት 2003 ዓ.ም አካባቢ ነው እ . ኢ . አ አንድ የማውቀው ወጣት ደውሎ እቤትህ ለአንድ ነገር ልመጣ እችላለሁ? የሚል ጥያቄ አቀረበልኝ።
እንዴታ! ማን ከልክሎህ? አልኩት።
እንዲያ መጠየቁ ወጣቱ ያው በፈረንጁ ባህል ውስጥ ራሱን ማስተካከሉንም እግረመንገዱን እየነገረኝ እንደነበረ ተስምቶኛል። ቀጠሮ መያዝ መሆኑ ነው። እናም በተቀጣጠርነው ቀንና ሰዓት ወጣቱ ከተፍ አለ። ኢትዮጵያዊ ሰላምታ ተለዋወጥን። ሻይ ቀርቦም እየጠጣን ዛሬ የመጣሁበት ምክንያት ከማለቱ እኔም እህ! አልኩት።
አንተ ተስፋዬን የምታውቀው በደራሲነቱ ነው አይደል? ብሎ ጠየቀኝ። የቱ ተስፋዬ? ቀጠለ የኔ ጥያቄ። ተስፋዬን አጣኸው እንዴ? ያ የጋዜጠኛው ማስታወሻ፣ የደራ. . . ከማለቱ እ! በቃህ! በቃህ! በማለት አቋርጨው እንዲህ ስል መለስኩለት።
“አይ! እኔኮ ብዙ ተስፋዬዎች ስላሉ የትኛውን ለማለት እንደፈለግህ ለመለየት ነው የጠየቅሁ። የምትለውን ተስፋዬንማ እንዴት አላውቀውም? በመልክ ሳይሆን፣ በተግባሩ አሳምሬ አውቀዋለሁ። ግን ከደራሲነቱ ውጭ በሌላም ይታወቃል እንዴ? የሚል ጥያቄ አቀርብሁለት ከራሱ ጥያቄ ተነስቼ።
ቀጠለም ወጣቱ፣
“ተስፋዬ ለኢትዮጵያ እና ለኢትዮጵያዊያን ያዘነ መስሎ ስዬን እየኮነነ፣ ስሜት ኮርኩሮ መርዛማውን የአዞ እምባውን በተለይም በሳይበሩ ላይ ረጨ። ወደ አገርም ዘልቆ በተለይ በአንድነት ፓርቲ ውስጥ የለኮሰው እሳት ፓርቲውን ክፉኛ አናውጦታል። እጅጉን አዝኜ ነበር። ለዚህም ነው እምነቴ አንተ ጋ ሆኖ ወደ አንተ ዛሬ የመጣሁት” አለኝ።
ትንሽ ደንገጥ አልሁ። ትንፋሼን ሰብሰብ አድርጌ፣ እንዴት? ምን አገኘህ ደግሞ? አልኩት ምናልባትም ስለተስፋዬ የወጣ፣ ያነበበው አንድ ጽሑፍ ይኖራል ብዬ በመገመት።
“ቀደም ብዬ አንተ የምትላቸውን የተስፋዬን መጽሐፍት እኔም አንብቤአለሁ። በተለይ የጋዜጠኛ ማስታወሻ የተባለውን መጽሐፉን ካነበብሁ በኋላ ተስፋዬ ማነው? አላማው ምንድነው? የተሰኙትን ጥያቄዎች ማውጣት ማውረድ ጀመርሁ። እንዳጋጣሚ ሆኖ እግዚአብሔር ከእኔ ጋር አዳረገው። እናም ተስፋዬን ለመከታተል ምቹ ሁኔታ ተፈጠረልኝ ማለት ነው። የተስፋዬን ማንነት እንደሚነገረን ሳይሆን፣ ይዞ ወደ ሳይበሩ የገባበትን አላማ የሚያሳዩ አንዳንድ መረጃዎችን ማግኘት ጀመርሁ። በመጨረሻም፣ ተስፋዬ ኢትዮጵያዊ ያለመሆኑን፣ የሻቢያ ሰላይ መሆኑን የሚያረጋግጥ መረጃዎች ላይ ደረስኩ። ክትትሌም ጠነከረ። ብዙ አስረጂዎችን በጄ ለማድረግ ቻልሁ። እናም፣ የተስፋዬን ማንነትና ምንነት ሊያሳዩ ይችላሉ ብዬ የገምትኋቸውን ሰነዶች ይዤ መጥቼልሃለሁ” ብሎ እርፍ አለ።
ኧረ እንዴት! እንዴት!? አልኩት የሰማሁትን ማመን አቅቶኝ።
እንዲህ ነዋ! ብሎ ጀመረ ወጣቱ። ይዞ የመጣውን ቦርሳ ከፈት አድርጎ። አንዳንድ ያመጣቸውን ማስረጃዎችን እያሳየኝ ይዘረዝርልኝ ገባ። እንጨትም ይሸብታል ይሉታል የዕድሜ ባለፀጋውን አስተሳሰብ ለማጣጣል ሲከጅሉ። ገና በአፍላ ዕድሜ ውስጥ ያለው፣ ገና ወደ አስተውሎቱ ያልደረሰው እንደ አዋቂ ሲናገር፣ ሲያስብና ሲያስተውል የልጅ አዋቂ ይሉታል ደግሞ። እናም እኔም ወጣቱን የልጅ አዋቂ አልሁት በሆዴ። አልተያዝክለትም እንጅ ብይዝህ ኖሮ፣ ወያኔ አንተን በደህንነት በደምብ ይጠቀምህ ነበር የሚልም ጨመርሁለት ለቀልድ ያህል። ዳሩ ምን ያደርጋል አመለጥከው ስለው ከትከት ብሎ ሳቀና እየቀለድህብኝ ነው አይደል ጋሽ ወልዴ? ብሎ የማስረገጫ ጥያቄ አቀረበልኝ። ምን እቀልዳለሁ ከአንጀቴ ነው የምለው። ማንም ያደርጋል ብዬ የማልገምተውን ነው ያደረከው። እናም፣ ቢኖር ከዚህም በላይ ልልህ ይገባኝ ነበር አልኩት።
ቀደም ብሎ “የቡርቃ ዝምታ” መጽሐፉን በአገር ቤት አንብቤ እግዚአብሔር ደግሞ እንዲህ ያለ አሪዮስ ጸሐፊ ከየት አመጣብን? ብዬ ጀመርሁ። አሁን በሳይበሩ ደግሞ “የጋዜጠኛው ማስታወሻ” መጽሐፉን ካነበብሁለት በኋላ የፈረጅሁት በጋዜጠኛነቱ ሳይሆን፣ በበታኝ ሰላይነቱ ነው።” አየህ! ተስፋዬ ይህንኑ መጽሐፍ ጽፎ እንዳጠናቀቀ ወደ ውስጣችን የገባው፣ መጽሐፉ ብዙ ያልሰማናቸውና ያላየናቸውን የወያኔን ምስጢር እንደያዘ አድርጎ አስቀድሞ ፕሮፓጋንዳ ነዝቶብን፣ በመጀመሪያ ረድፍ የተወሰኑ ጋዜጠኞችን፣ ከዚያም ወደ ሚዲያዎች ጠጋ ብሎ ነው።
አላነበብኸውም “እየተስተዋለ” በሚል ርዕስ አውጥቼው የነበረውን ጽሑፌን? ብዬ ጠየቅሁት። ያንን ጽሑፍ ለማውጣት የተገደድሁት፣ ከላይ ባልኩህ መሠረት ተስፋዬ ገብቶ እዚህ ያለውን ማህበረሰብ ሁለት ቦታ መከፋፈል መጀመሩን ደርሼበት ነው። እናም ሙከራዬ የነበረው፣ እየሸተተ የነበረውን ክፍፍል ለማክሸፍ፣ እየሰፋም ሂዶ ወደ አገር እንዳይደርስ ነበር። አንዳንዶቹ ተስፋዬ ስሜታቸውን እየኮረኮረ በመቀጠሉ የጽሁፌን መነሻና ይዘት ሊረዱ አልቻሉም። ይባስ ብለው በዚያ ጽሑፌ ወደ ወያኔነት የፈረጁኝም አልጠፉም። የትጥቅ ትግል ተቋሚ አድርገው የቆጠሩኝም አልጠፉም። እንደምታየው ተስፋዬ የአጻጻፍ ክህሎቱ ወደ በዓሉ ግርማ ይጠጋል። ለተወሰነ ጊዜ የማንንም ሕሊና የመግዛት ሃይል ያለው ነው። በዚህ መሠረትም፣ በትምህርት የላቁ፣ በልምድና በእድሜ የበሰሉ፣ በፖለቲካ ሥራቸው አንቱ የተባሉም ኢትዮጵያዊያንም ከወጥመዱ አላመለጡም። እናም ውሎ አድሮ የፈራሁት አልቀረ፣ የማይከፋፈል ማህበረሰብ ተከፋፈለ በተጻረረ መንገድ። እዚህ ውጭ ያለው የአንድነት ኃይሉ እንደዚያ ዓይነት አደጋ ውስጥ ሲገባ፣ ለአገር ቤቱም ተረፈ። መቼም ምንም ያህል ትምህርት ቢኖርህ፣ ምንም ያህል እድሜ ቢኖርህ ሰው ነህና አንዳንድ ጊዜ አስተውሎትህ የስሜትህ ተገዥ ይሆናል። እናም ሚዛንህ ትክክል አይመጣም።
አዎን አውቃለሁ። በወቅቱ እንዳልከው ጥቂቶቹ እንደዚህ ብሉህም ብዙዎች፣ በተለይም ተስፋዬን የሚያውቁ፣ መጽሐፉን ያነበቡና የመረመሩ ካንተው ጋር ነበሩ። እኔም አንዱ ነበርሁ። ጽሑፍህንም በደንብ አድርጌ አምብቤዋለሁ። ትክክልም ነበር። አንዳንድ ሰው ስለሚቸኩል፣ ነገርን አዙሮ ወዲያውኑ ማየት ይሳነዋል። አሁን ግን ይረዱታል አለኝ።
እኔም ቀጠልሁ። በሕግ ትምህርት ቤት ውስጥ መምህራኑም ሆነ የሕግ መጽሐፍት የሚያስጠንቅቁት፣ በተለይም በዳኝነትም ሆነ፣ በሕሊና ፍርድ ጊዜ በተቻለ መጠን ስሜትህን ልትቆጣጠር ይገባሃል። አለዚያ ፍርድህ ፍርደ-ገምድል ይሆናል። ይህ ደግሞ ስዎችን፣ ሕዝቦችን በጣም አድርጎ ይጎዳል በሚል። እንደዚያም ተምረህ ወጥተህ፣ እንደዚያም አውቀህ ወጥተህ መቼም ሰው ነህና ስሜት ውስጥ ትገባለህ። የራሴን አንድ ምሳሌ ልጥቅስልህ አልኩት ወጣቱን። ወጣቱ ምንም ሳይለኝ ብቻ አትኩሮ እያየኝ ማዳመጡን ቀጠለ።
ፍየል ከመድረሷ. . . .
ወደ 1984 ዓ.ም ይመስለኛል ኦነግ ከጊዜያዊ መንግሥቱ እንደወጣ፣ በአባላቱ ላይ ያልተፈጸመ ግፍ ይኖራል ብዬ አሁን ማሰብ ይከብደኛል። አንድ ቀን የቴሌቪዥን ዜና ሳዳምጥ፣ የጎተራን ዲፖ ነዳጅ ሊያቃጥሉ ሲሉ የተደረሰባቸው የኦነግ አባላት ተያዙ በማለት የተወሰኑ ሰዎችን አሳዩን። ታውቃለህ በወቅቱ በልቤ ያልኩትን፣ እነዚህን የምን ፍርድ ቤት እንዳሉ ከነነፍሳቸው ማቃጠል እንጅ ነው ያልኩት። ነዳጁ እንደተባለው በፈንጂ ቢመታ አዲስ አበባችን የምትሆነው እየታየኝ። የሚያልቀው ሰው ብዛት እየታየኝ። ደግሞም በየወቅቱ ከሚነዛው የወያኔ ፕሮፓጋንዳ ጋር ተዳምሮ። ጊዜውም ገና ልጅ ስለነበረ የወያኔም አካሄድና መንገዱ በቅጡ ባልተለየን ወቅት ነው። ፍርዴም ታዲያ ሙሉ ለሙሉ ስሜታዊ ፍርድ ነበር። በወቅቱ የኢትዮጵያ ምግብ ኮርፖሬሽን የሚባል ድርጅት ውስጥ የሕግ አማካሪና ነገረፈጅ ነበርኩና ፍ/ቤት አልገባሁም። ባልገባም የሕግ ሰው ሆኜ እንደዚያ ማለት አይገባኝም ነበር። እንደዚያ ዓይነት ስሜታዊ ውሳኔ መስጠት የአስተውሎት ማጣት ነበር።
ግና በ1986 ጥር 1 የክልል 14 ይባል የነበረው በጊዜው አጠራር የዞን ወይም በኋላና በቀድሞው አጠራር ከፍተኛ ፍ/ቤት ዳኛ ሆኜ ተሾምሁ። ያጋጣሚ ሆኖ ከፍተኛ የሆኑ የወንጀል ጉዳዮች የሚታዩበት ችሎት ተሰየምሁ። የችሎት አሰራርን እስክለምድ ድረስ፣ አንዳንድ የቆዩ መዝገቦች ይሰጠኝና ዝም ብዬ ለማሟያ ያህል የግራ ዳኛ ሆኜ እያነበብሁ እችሎቱ እቀመጣለሁ። በሁለተኛው ሳምንት ግን ያገኘሁት መዝገብ የሚያስደነግጠኝ መዝገብ ሆኖ ተገኘ። እሽፋኑ ላይ እነ ባየራ ይላል። የጎተራውን ዲፖ ነዳጅ ሊያቃጥሉ ሲሉ የተያዙ የኦነግ አባላት ይላል የወንጀሉ ርዕስ። ያ እውጭ ሆኜ የፈረድኩት ጉዳይ በፍርደ-መንበር ተቀምጬ ልፈርድ እፊቴ አፍጦ መጣ። ያጋጣሚ ነገር ያስደንቃል። ተከሳሾችን አሁን በትክክል አላስታውሳቸውም ወደ 7 ተከሳሾች ይመስሉኛል። መዝገቡ ሲታይ ለሁለት ዓመት ሙሉ ምስክሮች ባለመቅረባቸው በሚል ብቻ እየተቀጠረ የመጣ መዝገብ። ከሰብሳቢው ዳኛ ተከሳሾችን ጥራና ለሁለት ወር ያህል ቅጠራቸው ይሉኛል።
ለምን ሁለት ወር? የኔ ጥያቄ። እባክህን ምስክር አሁንም አላመጡም ዐቃቤ ሕጉን እንደጠየቅሁት አሉኝ። ብዙም እችሎት ውስጥ መነጋገር አስቸጋሪ በመሆኑ ክርክሩን አልቀጠልኩበትም። እኔ ለሁለት ወር አልቀጥርም አቶ አሰፋ ብቻ አልኳቸውና የመዝገቡን ተከሳሾች ጠራሁ። እዱኳ ገቡ። ማንነታቸውን ጠይቄ ከማብቃቴ አቶ ባየራ የተባሉ አንደኛው ተከሳሽ፣ ኧረ ጌቶቼ ፍረዱብን ወይም ልቀቁን እያሉ ጀርባቸውን ዞር በማድረግ እዩት የተፈጸመብኝን ግፍ በማለት ልብሳቸውን ወደ ማጅራታቸው ከፍ አደረጉ። ለዓይን የሚዘገንን፣ የሰው ልጅ ጭካኔን የሚናገር፤ የመንግሥትን ፍጹም የሆነ ጭካኔ የሚያሳይ ነገር አየሁ። ጀርባቸው ተግተልትሎ ቁስሉ ገና በመዳን ላይ ያለ ነው። የአምላክ ያለህ! ያሰኛል። ታዲያ የሃዘኔን መግለጫዎችን በወቅቱ እንደምንም ተቆጣጠርሁ። የዐቃቤ ሕግ ምስክር ሲጠራ የደህንነት አባሎች ስለሆኑ እና በየቦታው ስለሚዘዋወሩ ሊገኙ አልቻሉምና ተለዋጭ ቀጠሮ ይሰጠን የሚል መልስ የችሎቱ ዕቃቤ ሕግ ሰጠ። በዚህን ጊዜ ሰብሳቢው እባክህን ወደዚያ ራቅ አድርገህ ቅጠረው አቶ ወልደሚካኤል አሉኝ ዳግም።
መልስ አልሰጧቸውም። ብቻ ለሳምንት ቀጠርሁ። ተከሳሾቹ ደስ ብሏቸው ወጡ። ትዝ ይለኛል ሰብሳቢው አቶ አሰፋ (ከፌዴራል ፍ/ቤቶች መቋቋም በኋላ ጠበቃ ሆነው ሲሰሩ ቆይተው እኔ ከአገር ከወጣሁ በኋላ አርፈዋል እንደሰማሁት) ንዴታቸው በርትቶባቸው እያጉረመረሙ ቀጥሎ ያለውን ሥራ በቅጡ መሥራት አቃታቸው። እኔ ደግሞ በሆዴ ከመሾሜ መባረሬ እየታየኝ፣ እንዲህስ ከምሰራ የፈጠረኝ አምላክ ያውቃል ለምን አልወጣም፣ ለምን አልባረርም እያልሁ ራሴን በራሴ ማጽናናቱን ተያያዝሁ። በዚሁም መዝግቦች አለቁና ወደ ጽ/ቤታችን ገባን። አቶ አሰፋ ገና ካባቸውን ሳያወልቁ፣
“ፍየል ከመድረሷ፣
ቅጠል መበጠሷ።” በሚል ተረት ጀምረውኝ፣ አቶ ወልደሚካኤል ይህ
ፍ/ቤት ነው። ሰብሳቢው በችሎት ያዘዘውን መፈጸም ግዴታ ነው አሉኝ። ሕጋዊ ያልሆነውንም? ብዬ ጠየቅኋቸው። በዚህን ጊዜ አራት ነበርና በተለይ እችሎቱ የነበረው ቀኝ ዳኛው፣ ሮመዳን ጣልቃ ገብቶ ምንድነው የሚሉት አቶ አሰፋ? ምን አድርግ ነው የሚሉት። ደግ አደረገ ብሎ ሲያፈጥባቸው በአንድ በኩል፣ በሌላው ደግሞ እጽ/ቤት የነበረውም ዳኛ፣ ይሁንም ተጨመረ። ወልዴ አድርጎት ከሆነ ትክክል ነው የሰራው። እኛ ተሸንፈን ነው መዝገቡ የቆየው። አሁንስ እርሶ አበዙት በማለት ተንጣጣባቸው። ሁለቱም የሆዳቸውን ቁስል ባጋጣሚው አከኩት። የእንግዳነቴን አጋጣሚ ተጠቅመው ከጧቱ ይህች ባቄላ ያደረች እንደሆነ . . . ሊሉኝ የነበረው በዚህ አከኋን ቀዘቀዘ። እናም በኋላ በቀነ-ቀጠሮው ዳግም ምስክሮቹ ስላልመጡ፣ በተለዋጩ ቀጠሮ ምስክሮቹ ካልቀረቡ ተከሳሾቹን የምንለቅ መሆኑ አስጠንቅቀን ትዕዛዝ ሰጠን። በዚህ ርምጃ የተሸበረው ዕቃቤ ሕግ የደህንነት አባል የተባሉትን በቀጠሮ ዕለት አቀረባቸው። የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽነር በወቅቱ የነበረው አራንሽን የተባለ ይመስለኛል ከሌሎች ሁለት የወያኔ አባላት ጋር ቀረቡ።
በወቅቱ የከፍተኛ ፍ/ቤት ጠባቂ ፖሊሶች የቀድሞዎቹ ስለነበሩ መሣሪያ ተቀምተው ባዶ እጃቸውን ነው የሚጠብቁት። አንድ ምስክር መስክሮ ሲሄድ ለሌላኛው ጥያቄዎችን ለማስተላለፍ ቢሞክር ከልካይ የለም። በዚህ ላይ አሁን የቀረቡት ምስክሮች የወያኔ ባለሥልጣናትም ስለሆኑ የፈለጉትን ቢያደርጉ የሚቆጣጠራቸው የለም፡፡ እናም ዘዴ ፈጠርን። የችሎቱ ዳኞች አራት ነን። ሦስታችን ወደ ችሎቱ ስንወጣ አንዱ እጽ/ቤት ምስክሮቹን ይዞ ተቀምጦ፣ ምስክሮቹን አንድባንድ በጠራን ቁጥር እንዲልክ አደረግን። በዚህም የተዋጣ ውጤት አገኘን። አመሰካከራቸው ከመሣሪያ መያዝ ውጭ ወዲህና ወዲያ ሆኖ ተገኘ። እናም፣ በውጭ የሰጠሁት ፍርድ ተሻረ። በነጻ ከዋና ወንጀሉ ለቀን፣ መሳሪያ መያዛቸው ብቻ ስለተመሰከረባቸውና ሊያስተባብሉም ስላልቻሉ የታሰሩበትን በቂ አድረገን ለቀቅናቸው። ግና ውሳኔያችን ተግባራዊ ከመሆኑ በፊት ታገደ። በዚህም የተወሰንን ዋጋ ከመክፈል አልዳንንም በወቅቱ። ይህ ወደፊት ይገልጻል። ብቻ ይገበሃል? ለማለት የፈለግሁት፣ ማንም ሰው ቢሆን በተወሰነ ጉዳይ፣ በተወሰነ ወቅት እስሜት ውስጥ ይገባል።
እናም፣ እኔ እነዚያ በእኔ ላይ አንዳንድ ነገሮችን ባሉት ላይ አይደለም በወቅቱ ያዘንሁትና የፈረድሁት፣ ይኸ እርኩስ ከፋፋይ ሰው ላይ ነው። እነርሱ ሳይሆኑ ደመኛዬ አድርጌ የያዝሁት እርሱን ተስፋዬን ነው። እነርሱ ከልባቸው ኢትዮጵያዊነት አይፋቅም፣ እንዲያውም ይኮሩበታል እንጅ። እነርሱ እውነትን ሲያውቁ ይረዱታል። እናም ይመለሳሉ። እርሱ ዘንድ ኢትዮጵያዊነት ስለሌለ፣ እውነት ስለሌለ ይብሱን ወደማጥፋት ይሄዳል እንጂ አይመለስም። እርሱ ገዳያዋ ነውና። ስለሆነም፣ ነገሬ እርሱን መከታተሉና ማሳደዱ ላይ ነበር የተሰማራሁት ብዬ አበቃሁ።
ከዚያም አለማየሁ የነገረከን ምሳሌ ሳይሆን፣ የሆነ ድራማ ይመስለኛል። እንዴት ደስ የሚል ነው? ካለ በኋላ፣ በዚህ ሰው ላይ በመጽሐፍ መልክ ሊጻፍ የሚችል መሰለኝ አለኝ። ሰነዶቹን ካየሁ በኋላ ብንነጋገር ይሻላል አልኩት። ለሁሉም ትምህርት ስለሚሆን መጻፍ አለበት አለኝ ከረረ አድርጎ። በመጠኑም ቢሆን የሕግ ሰው ብሎም ዳኛም ስለነበርሁ ሁሌም ለስሜት ቶሎ ብሎ ያለመገዛትን ስንቄ ስላደረግሁ፣ አሁንም ለወጣቱ መልሴ ያመጠሃቸውን ልያቸውና ላመዛዝናቸው
አልኩት። ወጣቱ ግን ይዞ የመጣቸውን ማስረጃዎችን ከተስፋዬ እጅ መንጥቆ ለማውጣት ካደረገው ተጋድሎ ጋር እያዛመደ አዎን ጋሽ ወልዴ በርግጠኛነት እለሃለሁ አንድ መጽሐፍ ይወጠዋል። ያለአንተ የማምነውና ይጽፈዋል የምለውም ሰው የለኝምና ቶሎ እባክህን ጀምር። አሁን በያዘው የስደተኛው ማስታወሻ ላይ ቀሪውን መርዝ ረጭቶ ከማውጣቱ በፊት ጣደፍ፣ ጣደፍ አድርገህ ቶሎ አውጣው የሚል ወታደራዊ ትዕዛዝ ዓይነት ሰጠኝ።
ወጣቱ ልጅ ያልኩት ከመያድ ጀምሮ እስከ ቅንጅት የወጣት አባልና ሃላፊ ሆኖ የሰራ፣ ምርጫ 97 ባመጣው መዘዝ ከቅንጅት መሪዎች ጋር ለሁለት ዓመታት ያህል በቃሊቲ ዘብጥያ ተንገላቶ የወጣ፣ ከዚያም በአገር በሰላም መኖር ባለመቻሉ ወደ ስደት ወጥቶ የሚገኝ ነው። አለማየሁ ይባላል። እዚህ ኔዘርላንድ ለእኔ ጎረቤት በሆነች ህልቨርሱም በተባለች ወረዳ ውስጥ ይኖራል። ያ የትግል መንፈሱ አሁንም ከአለማየሁ ጋር አለ። ተስፋዬ በየማስታወሻዎቹ አልፎ.አልፎ አለማየሁን “ትንታግ” ይለዋል። እኔም ቃሉን የተጠቀምሁት ለዚህ ነው።
እናም፣ አለማየሁ ያመጣቸውን የማስታወሻ ሰነዶችን ለያይቼ ለማየትና ለማስተዋል እንደሞከርሁት፣ ከቡርቃ ዝምታ ጀምሮ ተስፋዬ ከሚያገለግላቸው ጌቶቹ ጋር የተለዋወጠበትን ጭምር አመላካቾች ናቸው። በመሆኑም፣ ሰንዶቹን እርሱ ከጻፋቸው መጽሐፍት ጋር እያመሳከሩና እያመዛዘኑ ቢጻፍ ለትውልድ በማስተማሪያነቱ የሚበቃ አንድ አነስተኛ መጽሔት፣ አለያም መጽሐፍ ለማውጣት ወደ ሚቻል መደምደሚያ ላይ ደረስሁ። እናም፣ በተቻለኝ መጠን በፈርጅ ፈርጁ ነድፌ አስቀመጥሁ። በዚህም ከአለማየሁ እየተረዳዳን መጽሐፍ እንደምንችል ነግሬው ተስማማማን። በዚህ መልክ ተጀመረ።
ተስፋዬም ገብረአብ በኤውሮፓ ኔዘላንድስ ለስደት የሚያበቃውን ወረቀት ካገኘ በኋላ በደባልነት የተቀመጠው አለማየሁ ቤት ነው። የተባሉትን ማስረጃዎችን አለማየሁ በነደፈው ጥበቡ ያገኘው ይህንኑ አጋጣሚ ተጠቅሞ ነው። ብቻ ነገሩ በሬ ከአራጁ ጋር ይውላል ዓይነት ሆነና ታየ። ቀደም ብሎ በፌዴራል ፍ/ቤቶች አስተዳዳሪ የነበረው ሰው በኮራፕሽን መጋለጡን እንደሰማሁ፣ “ለሁሉም ጊዜ አለው” በሚል ርዕስ በመጠኑም ቢሆን፣ ከፍ/ቤቶቹ ዋና ተዋንያን ጀምሮ ያለውን ኮራፕሽን ለመነካካት መሞከሬ ይታወሳል። ያ አገር ውስጥ ከነበረ፣ ከፍ/ቤት ጋር በተያያዘ ነበር። የዛሬው ግን በመግቢያው ላይ እንደተመለከተው ከአገር ውስጥ ሳይሆን፣ ከፍ/ቤት ጋር በተያያዘ ሳይሆን፣ እዚሁ እስከ ሳይበሩ የዘለቀ ነው ከላይ ለመጠቃቀስ እንደሞከርሁት። ተስፋዬ ገብረአብ በኢትዮጵያዊነትና በኢትዮጵያዊያን ላይ በደራሲነት ስም ዘው ብሎ ገብቶ ስለፈጸመው ደባና የስለላ መረብ።
ክፍል 2.
ተስፋዬ ገብረአብ ማነው?
ዜግነቱ፣
ወያኔ-ኢህአዴግ ሥልጣን ከያዘ ጀምሮ በዘር በጎሳ፣ በዘር ከፋፍሎን እያናቆረን ዓመታትን አስቆጥሮአል። ያልተጻፉ መርዘኛ መጽሐፎችን እያነባነቡና እየተረኩ ጨዋውን ሕዝብ ለበቀል ማዘጋጀቱን ቀጥሎአል። ሕዝብ እንዳይተማመን፣ ርስበርሱ እየተጨፋጨፈ እንዲለያይ፣ ኢትዮጵያ የምትባል አገር ተበታትና እንዳትኖር ጉድጓድ መማሱን ቀጥሎአል። የበደኖ፣ የአርባጉጉ ክስተት እንዲሁ ከመሬት ተነስቶ የተፈጸመ ድርጊት እንዳልሆነ ቁልጭ ብሎ የታየው ግን ከተስፋዬ “የቡርቃ ዝምታ” መርዛም መጽሐፍ በኋላ ነው። “ነፍጠኛ” በሚል ተቀጽላ በታጀበ ስልታዊ የወያኔ ደህንነቶችና ካድሬዎች ርምጃ ያለቁት የአማራ፣ የጉራጌ እና የሌሎች ዘሮች ቤት ይቁጠረው ብሎ ብቻ ማለፉ ለጊዜው በቂ ነው። ታዲያም ተስፋዬ ደራሲ ነኝ ይላል። በተከታታይም መጻፎችን አውጥቶአል። ደጋፊዎችንም አትርፎአል። ለመሆኑ ተስፋዬ ማነው? እውነት ጋዜጠኛ ወይስ ደራሲ ወይስ ሰላይ? የሚሉ ጥያቄዎች በተወሰኑ ማህበረሰባችን አእምሮ መግባታቸው አይቀሬ ነው። ኢትዮጵያዊ መሆን ያለመሆኑ ላይ ግን ከጥቂቶቹ በስተቀር፣ አብዘኞቻችን አልተጠራጠርንም። ግና ጊዜው ደረሰና የብዙዎች ጥርጣሬ በተለይም የነዚያ የነጻው ፕሬስ አባላት ጩኸት እውን ሆኖ ሊታይ ብቅ አለ። እንዴት?
ተስፋዬ ገብረአብ በ1960 ዓ.ም በኢትዮጵያ ኦሮሚያ ምድር፣ በደብረዘይት ከተማ ተወለድሁ ባይ ነው። እስከ አሥራ ሁለተኛ ድረስ ከተማረ በኋላ ወደ ሐረር ፖለቲካ አካዳሚ ሂዶ በ1980 ዓ.ም የጦር ሜዳ ጋዜጠኛነት ኮርስ ውስዶ ተመርቆአል። ከዚያም እንደሚለው ወደ ሰሜን ጦር ግንባር ሂዶ በመሥራት ላይ እንዳለ በኢህአዴግ ጦር ይማረካል። ወያኔ-ኢህአዴግ ኢትዮጵያን በ1983 ዓ.ም ሲቆጣጠር ከሠራዊቱ ጋር ወደ አዲስ አበባ ገባ። በ1988 ዓ.ም ወደ አሜሪካ፣ ሲያትል ተልኮ የራዲዮ ጋዜጠኛነት ትምህርት ተከታትዬ ተመልሻለሁ እጁን ለሰጠበት አገር ሲል፣ በደራሲ ማስታወሻ ላይ ግን ወደ አሜሪካ ሲያትል የሄድኩት ለረፍት ነበር ይላል። የትኛው እውነት እንደሆነ መገመት የሚቻለው ግን የተስፋዬን ማንነት መገንዘብ ከቻልን በኋላ ነው። ተስፋዬ በኢትዮጵያ ራዲዮና ቴሌቪዥን ውስጥ በሃላፊነት ሰርቶአል። እፎይታ የተባለ አሳታሚ ድርጅት፣ እና መጽሔት ሥ/አስኪያጅ እንደነበረም ይታወቃል። ከዚህ አልፎ ተርፎም ተስፋዬ ቀንደኛ የወያኔ ደህንነት አባልም የነበረ ለመሆኑ ወደ ፊት የምናይ መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ ግን ተስፋየ በሥራ ላይ በቆየባቸው ጊዜያት ውስጥ ተስፋዬ ከላይ የገልጽሁትን መጽሐፍ፣ “ተራሮችን ያንቀጠቀጠ ትውልድ”፣ ጨምሮ ወደ ሰባት የሚሆኑ መጽሐፍትን አሳትሞ ለንባብ አብቅቶአል። በአጻጻፍ ዘይቤውና አጣጣሉ ተስፋዬ የፈጠራ መጽሐፎችንና ተውኔቶችን አዘጋጅቶ ለማውጣት እና የአንባቢያን ቀልብ በግርድፉ ለመሳብ መቻሉን ማሳየት የሚችል ሰው ነው።
ተስፋዬ በተለይ እዚህ ውጭ በወጣበት ጊዜ እኛን ኢትዮጵያዊያንን ሊቀርበን የቻለው ኢትዮጵያዊ ለመሆኑ አጽንዖት በመስጠት ነው። ጠርጥረው ሲጠይቁት፣ እኔ ተወልጄ፣ ያደግሁባት፣ እና እትብቴ በተቀበረባት ቢሾፍቱ ወይም ደብረዘይት ኢትዮጵያ ነው። ማንም ኢትዮጵያዊነቴን ሊቀማኝ አይችልም ይለናል አስረግጦ። እናም በዚህ ጠንካራ አነጋገሩ ኢትዮጵያዊውን መንፈስ ጸጥ ያስደርጋል። ያው የሚባለውን የቢሾፍቱን ቆሪጥ ተስፋዬ ተጋርቶ ይሆን? የቢሾፍቱ ቆሪጥ ለመኖሩ፣ ወይም ተስፋዬ ለመገራቱ እግዚአብሔር ይወቀው ከምል ውጭ አልዘልም። አንዳንዴ ችግር ሲለን፣ የማናምነውን ነገር እያንሳን ወደ እውነትነት መለወጡ የሰው ባሕርይ ሆኖ ነው እኔም ጠቀስ ማድረጌ። የክርክሩ መሠረት ኢትዮጵያዊነት፣ ወይም የኢትዮጵያ ዜግነትን ላይ ነው። እናም ኢትዮጵያዊነቴን ማንም ሊነጥቀኝ አይችልም እያለ ተስፋዬ ፎክሮአል፣ ተሳልቆብናልም።
ለነገሩ ብዙዎቻችን ቀደም ብሎ አዎን! ማንም ይህን በመወለድ ያገኘውን የኢትጵያዊነት ዜግነቱን በሕግ ካልሆነ በስተቀር፣ ሊከለክለው፣ ወይም ሊነጥቀው አይችልም ብለናል። በኢትዮጵያ የዜግነት ሕግ መሠረት አንድ ሰው በኢትዮጵያ ውስጥ በመወለዱ ብቻ የሚያገኘው ስለሆነ። ታዲያም፣ ቁም ነገሩ በኢትዮጵያ ውስጥ ስለመወለዱ ላይ አልነበረም። ወይም ኢትዮያዊነቴን ማንም አይነጥቀኝም በማለቱ ላይ አልነበረም። ቁም ነገሩ ተስፋዬ እውነተኛ ኢትዮጵያዊ መሆን ያለመሆኑ ላይ እና ተግባሩ ላይ ነው። እንደሚለው ከልብ ኢትዮጵያን አገሬ ናት ብሎ አምኖ እየኖረባት ነበር? በሚለው ጥያቄ ላይ ነው። የሚጽፋቸው ነገሮች ኢትዮጵያን የሚገነቡ መሆን ያለመሆኑ ላይ ነው። ጽሑፎቹ እውነት ላይ መመሥረት ያለመመሥረት ላይ ነው።
ከቡርቃ ዝምታ መጽሐፉ በኋላ የነቁ ኢትዮጵያዊያን፣ በተለይም የነጻው ፕሬስ ጋዜጠኞች ሰሚ ባያገኙም በወቅቱ፣ ተስፋዬን አንተ ኢትዮጵያዊ አይደለህም፣ ኤርትራዊ ነህ፣ የሻቢያ ቅጥረኛ ነህ፣ አገር ማፈራረስ ላይ፣ ደም ማፋሰስ ላይ የተሰለፍህ ነህ እያሉ ጩኸውበታል፤ ሽንጣቸውን ገትረው ተሟግተውታል። በዚህም ዋጋ የከፈሉም አይታጡም። ሙግታቸው የኢትዮጵያ ዜግነቱን ለማሳጣት አይመስለኝም። ከድርጊቱ በመነሳት፣ ድርጊቱን እየኮነኑ እንጅ። ግን ተስፋዬ የዋዛ ሆኖ አልተገኘም። በወያኔ የኋላ ደጀንነትና አይዞህ ባይነት እንዲሁም የካድሬነቱ እኩይ ጥበቡ ተጨምሮበት መልሶ መላልሶ ኢትዮጵያዊነቱ ላይ አጽንዖት በመስጠት ምሎ ሲገዘት ከርሞአል። የተወሰኑትንም ለማሳመን ችሎአል።
ግና “እውነት ትዘገያለች እንጅ አትቀበርም”፣ “እውነትና ንጋት እያደር ይጠራል” የተሰኙ አባባሎች በእንዲህ ያለ ወቅት ወደ ወዘናችን ገባ ይላሉ። እናም፣ የተስፋዬ የዜግነቱ ጭምብል ጊዜውን ጠብቆ ላይደበቅ እንደ ጅብራ በፊታችን ቀጥ ብሎ ሊታይ የግድ ሆነ። እናም፣ ሁሉም ነገር ጊዜውን ጠብቆ እመር ብሎ መውጣቱ አይቀሬነቱ በተስፋዬም ታየ። በእንዴት? ትንታጉ አለማየሁ ካመጣቸው ሰንዶች ውስጥ ነዋ።
ከምን ዓይነት ሰነድ? መቼ?
ሰንዱ የተስፋዬ መታወቂያ ሰንድ። ተስፋዬ ወደ ኬንያ እንደገባ ምንም ያህል ሳይቆይ፣ ከኤርትራ ኤምባሲ የኤርትራ መታወቂያ ደብተር ካገኘበት የኤርትራ ዜግነቱን ከሚያረጋግጠው ሰነድ። መታወቂያውና የሰፈሩት መለያዎች የሚከተለውን ይመስላሉ።
1. መታወቂያው፣
የተስፋዬ እንዲህ ይላልም፣
እ.ኤ.አ በ14-06-2001፣ በቁጥር 1665582 የተመለከተና ከአሥመራ በትግሪኛ እና በዐረብኛ ተጽፎ የተላከለት፣
“ግዝያዊ መንግስቲ ኤርትራ (ህ.ግ.ሓ.ኤ)፣
ኤርትራዊ ወረቅዋት መንነት”
ብሎ የሚጀምረው መታወቂያ የሚከተለውን የተስፋዬን እንፎርሜሽን ይዞአል።
ስም፦ ተስፋየ ገብረኣብ ሃብተዴን
ጾታ፦ ተባ
ዕ/ልደት፦ 28.08.1968
(ሙሉውን ጽሁፍ በፒ.ዲ.ኤፍ ለማንበብ ይህንን ይጫኑ)



