በወልድያ ዩኒቨርሲቲ ሁለት ተማሪዎች ሞቱ
10 ቀላልና ከፍተኛ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል
ኢዛ (ሰኞ ኅዳር ፩ ቀን ፳፻፲፪ ዓ.ም. November 11, 2019)፦ እስካሁን መንሥኤው አልታወቀም በተባለ ግጭት ሁለት የወልድያ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች መሞታቸውንና አሥር ተማሪዎች ደግሞ ቀላልና ከፍተኛ የአካል ጉዳት እንደደረሰባቸው ተገለፀ።
ቅዳሜ ጥቅምት 29 ቀን 2012 ዓ.ም. ምሽት ላይ የደረሰውን የሞትና የመቁሰል አደጋ ተከትሎም የአማራ ክልል መንሥኤውን ለማወቅ ምርመራ የጀመረ መኾኑን ሲገልጽ፤ በድርጊቱ የተሣተፉ አካላትንም ለሕግ አቀርባለሁ ብሏል። ለዚህም አንድ የምርመራ ቡድን የተቋቋመ ሲሆን፣ ተጠርጣሪዎችም እየተያዙ ነው ተብሏል።
የኦሮሚያ ክልል ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ መግለጫ የሠጡ ሲሆን፣ በዩኒቨርሲቲው የደረሰውን ድርጊት ክልላቸው የሚያወግዝ መኾኑን ገልፀው ድርጊቱን የፈፀሙ አካላትን ከፌዴራልና ከአማራ ክልል ጋር በመኾን ለሕግ እንዲቀርቡ እንደሚሠሩ ገልጸዋል።
የድርጊቱ ፈጻሚዎች አብሮ የመኖር እሴትን በመጋፋት ሰላም እንዳይኖር በሚሹ ወገኖች የተፈፀመ ነው የሚል እምነት ያላቸው መኾኑን ጠቅሰዋል።
ከዩኒቨርሲቲው የተገኘው መረጃ፤ ጉዳዩ በፖሊስ መያዙን የሚጥቅስ ሲሆን፣ የፌዴራል ፖሊስና መከላከያ መግባቱንም የሚጠቅስ ነው። በዕለቱ የወልድያ የአገር ሽማገሌዎችና የተለያዩ የሕብረተሰቡ አባላት ውይይት ያደረጉ መኾኑም ተገልጿል። (ኢዛ)