ዲባቶ አረጋዊ በርሄ ከኦታዋ ኢትዮጵያዊያን ጋር መከረ
ስብሰባው በካሜራ እንዲቀረጽ ተፈቅዷል
“ለተቃዋሚ ሀይሎች ኅብረት ምስረታ ከግንቦት ሰባትና ሌሎች ተቃዋሚ ሀይሎች ጋር እየሰራን ነው”
ቅዳሜ፡ ኦገስት 20፡ ከሰዓት በኋላ በብሮንሰን ማእከል በተደረገው ስብሰባ ላይ፡ የህብረት ምስረታ ጉዳይን፡ የጠላትን ሀይል አሰላለፍ፡ የተቃዋሚዎችን አለመተባበር ችግርና የመተባበርን አስፈላጊነት፡ እንዲሁም የብሄርንና የራስን እድል በራስ መወሰን ጉዳይን አስመልክቶ ሰፊ ምሁራዊና ፖለቲካዊ ትንተና ሰጥቷል። የራስን እድል በራስ ከመወሰን ጋር በተያያዘ፡ ግለሰብም ይሁን ቡድኖች የራሳቸውን እድል በራሳቸው መወሰኑ የተፈጥሮ መብት መሆኑን፡ ነገር ግን “ዴሞክራሲ እንጂ መገንጠል የችግሩ መፍትሄ” እንደማይሆን፡ አበክሮ ተናግሯል።
አረጋዊ በመቀጠልም፡ የጠላት አሰላለፍ እኛ እንደምንንቀው ሳይሆን፡ ትናንት ሀይለሴላሴና ደርግ በወረዳና በቀበሌ ወስነውት የነበረውን የስለላና የአስተዳደር መዋቅር፡ ህወሀት/ኢህአዴግ በጎጥ፡ በቡድንና በአካባቢ አውርዶት እስከታች ድረስ በስለላ መዋቅሩ እንደሚቆጣጠርና፡ ይሄንን ለመቋቋምና በጣጥሶ ለመግባት የሚያስችል የትግል ስልት መንደፍ እንዳለብን አሳስቧል። ዲባቶ አረጋዊ በርሄ፡ ከህዝቡ የተነሱትን ጥያቄዎች መልስ ሰጥቶባቸው፡ ንግግሩን በሚከተለው መልኩ http://www.youtube.com/watch?v=SRwRybNMObE አጠናቋል። ዲባቶ አረጋዊ በመጨረሻም፡ ከግንቦት ሰባትና ሌሎች ድርጅቶች ጋርየሚመክር እነ አንዳርጋቸው ጽጌ፡ ነገደ ጎበዜና መሰል ፖለቲከኞች ያሉበት ኮሚቴ ተቋቁሟል ሲል ተሰብሳቢውን አጽናንቷል።
ቀደም ሲል በተደረገው የኦታዋ ስብሰባ ካሜራ እንዳይገባ የተከለከ ቢሆንም፡ በዚህኛው ስብሰባ ግን፡ ወደኢትዮጵያ ለሚመላለሱና በኢትዮጵያ ንብረት ላላቸው ሰዎች ሲባል የእንግዳው ንግግር እንዳይቀረጽ መደረጉ፡ የምንታገልለትን አላማ ይጻረራል በሚል፡ የስብሰባው አዘጋጆችና ራሳቸው ዲባቶ አረጋዊ ንግግራቸው በካሜራ እንዲቀረጽ ፈቅደዋል። በስብሰባው ላይ፡ የዲባቶ አረጋዊ በርሄ የህወሀትን ምስረታና የነመለስን ጠለፋ የሚያትት፡ A Political History of the Tigray People’s Liberation Front የተሰኘ መጽሀፍ ለግዢ ቀርቦ፡ ተሰብሳቢው በሙሉ ተቀራምቶታል።
ማስታወሻ፡ የዚህ ዜና ዘጋቢ፡ በገዛበት ሌሊት ብቻ ባደረገው ከፊል የመጽሀፉ ቅኝት፡ ማንበብ ሊያቆም እንዳልቻለና፡ ብዙ ስለሕወሀት የማያውቃቸውን ታሪኮች ለማወቅ እንደቻለ ይገልጻል። ኢትዮጵያዊያን ሁሉ ቢያነቡት፡ አሁን ያለውን የጠላት አሰላለፍ በቅጡ ለመረዳት ይረዳቸዋል የሚል እምነት አለው።
ተክለሚካኤል አበበ፡ እሁድ፡ ኦገስት 21፡ 2011



