አል-አሙዲ 4ቢሊየን ዶላር እንዲያገኙ ደሀው ህዝብ ሊፈናቀል ነው
ተፈናቃዮች ካሳ አይሰጣቸውም
የአካባቢ ብክለት ስጋት ፈጥሯል
(ልዩ ሪፖርታዥ-ኢትዮጵያ ዛሬ)
Ethiopia Zare (ቅዳሜ መጋቢት 16 ቀን 2004 ዓ.ም. March 24, 2012)፦ ንብረትነቱ የሼህ መሀመድ ሁሴን አሊ አል አሙዲ የሆነው ብሔራዊ የማዕድን ኮርፖሬሽን (NMC) በቅርቡ በደቡብ ኢትዮጵያ ያገኘውን መጠኑ 550 ሺህ ኪሎ ግራም የተገመተ የወርቅ ክምችት ለማውጣት በዝግጅት ላይ መሆኑ ሲታወቅ ከዚሁ ጋር በተገናኘ የአካባቢው ነዋሪዎች ያለ አንዳች የካሳ ክፍያ በግዳጅ ሊፈናቀሉ እንደሆነ ተገለጸ።ኮርፖሬሽኑ ቀድሞ የኢትዮ-ሊቢያ ማይኒንግ ኮርፖሬሽን በመባል የሚታወቀውን ድርጅት ከመንግስት ለመግዛት ሲባል እ.ኤ.አ 1993 ዓ.ም የተቋቋመ ሲሆን በቐታዩ አመት (1994ዓ.ም) የኢትዮጵያ ፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ የተመረጡ የመንግስት ድርጅቶችን ወደ ግል ይዞታነት ማዛወር ሲጀምርም የመጀመሪያውን ግዥ የፈጸመው ይሄው ዝግጁ ሆኖ ሲጠባበቅ የነበረው የሼሁ ኩባንያ ነበር።
ብሄራዊ የማዕድን ኮርፖሬሽን በደቡብ ኢትዮጵያ ከአዲስ አበባ በ660 ኪ.ሜትር ርቀት ላይ በሚገኘው ኦኮት በተባለው አካባቢ ከ550 ሺህ ኪሎ ግራም በላይ የተገመተ የወርቅ ክምችት ማግኘቱን የገለጸ ሲሆን በመጪዎቹ 20 ዓመታት ጊዜ ውስጥ 4ቢሊዮን ዶላር እንደሚያገኝበትም የድርጅቱ ዋና ሃላፊ የሆኑት አቶ መላኩ በዛ ለጋዜጠኞች በሰጡት ቃለ ምልልስ ላይ አሳውቀዋል።
በዚህ በኦሮሚያ ክልል ውስጥ ከሚገኘው ዳዋ ኦኮት ከተባለው አካባቢ የተገኘውን የወርቅ ክምችት ለማውጣት ኮርፖሬሽኑ ዝግጅቱን እያጧጧፈ ሲሆን በመጭዎቹ ሁለት አመታት 73 ሺህ ኪሎ ግራም ወርቅ ለማምረት መሰናዳቱም ተመልክቷል። ከዚያ በሗላ ባሉት ጊዜያት ግን ሀይሉን በማስፋፋት በአመት 10ሺህ ኪ.ግራም ወርቅ ለማውጣት ማቀዱንና ይህም ለሼሁ ኮርፖሬሽን ከአኮት ብቻ በዓመት 500ሚሊዮን ዶላር እንደሚያስገኝ ታምኖበታል።
ብሄራዊ የማይኒንግ ኮርፖሬሽን በተለያዩ የማእድን ፍለጋና ማውጣት ስራዎች ላይ ተጠምዶ የቆየ ሲሆን ከአኮት በስተሰሜን 100 ኪ.ሜትር ርቀት ላይ የሚገኘውን የላጋዳንቢን የወርቅ ማዕድን ለማምረት ሲባል በስሩ ያቋቋመው ሚድሮክ ጎልድ የተባለው ድርጅቱም ከላጋዳንቢ ብቻ በዓመት 4ሺህ ኪሎ ግራም ወርቅ እያወጣ መሆኑ ይታወቃል።
በተመሳሳይ መልኩ ብሄራዊ የማዕድን ኮርፖሬሽን ሳካሮ በሚባለው አካባቢ 20ሺህ 483 ኪሎ ግራም ወርቅ ለማውጣት የ10 ዓመታት ውል ተፈራርሞ እየሰራ ሲሆን በትግራይ ክልልም 18ሺህ ኪሎ ግራም ወርቅ እንዲሁም ከፍተኛ መጠን ያላቸው የብር-ሊድና ዚንክ ማዕድናትን በማውጣት ላይ ይገኛል።
ባለ ሀብቱ ሼህ ከፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ በ140 ሚሊዮን ዶላር እንደገዙት ከተነገረው ከላጋዳንቢው የወርቅ ማዕድን ብቻ እስከ 2009 ዓ.ም መጨረሻ ድረስ በነበረው ጊዜ 466 ሚሊዮን ዶላር ሲያገኙ ከሰሜን ትግራይ የሚያወጡት ወርቅ ደግሞ 792 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያስገኝላቸው ተገልጿል።
ባለፉት አመታት ከሀገሪቱ የሚወጣው የወርቅ መጠን በከፍተኛ ደረጃ ሲጨምር እስካለፈው ጁላይ ወር ድረስ በነበረው ዓመት የወርቅ ኤክስፖርት 75% ማደጉን ጥናቶች አመልክተዋል።
በያዝነው በኢትዮጵያዊያን አቆጣጠር 2004 ዓ.ም የመጀመሪያዎቹ 6 ወራት ከወርቅ የተገኘው ገቢ ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር 80 ሚሊዮን ዶላር ያህል የላቀ ገቢ ማስገኘቱን የንግድ ሚኒስትር ይፋ ያደረጋቸው አሀዞች ያሳያሉ።
ሼህ መሀመድ ሁሴን አሊ አል አሙዲ ከገዥው ህወሃት/ኢህአዴግ መንግስት ባለስልጣናት ጋር ባላቸው የጠበቀ ግንኙነት ሳቢያ ባለፉት 20 ዓመታት ውስጥ ፍትሐዊ ባልሆነ መንገድ ከሀገሪቱ ከፍተኛ ሀብት እያጋበሱ ስለመሆኑ በስፋት ሲወነጀሉ መቆየታቸው ይታወቃል።
በዘመነ ኢህአዴግ ከዓለም የሀብታሞች መዝገብ ላይ ከ400 በላይ ደረጃዎችን እንደተወጣጡ የሚናገሩ አሉ። ባለፉት 4ዓመታት ብቻ በፎርበስ መጽሔት የዓለም የሀብታሞች ሊስት ላይ ከ80ኛ ደረጃ ወደ 61ኛነት ሲመነጠቁ ሀብታቸውም ከ8ቢሊዮን ዶላር ወደ 12.5 ቢሊዮን ዶላር ማደጉ ተመልክቷል።
ባለሀብቱ የኢትዮጵያ ፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ ወደ ግል ባለሀብቶች ካዛወራቸው የመንግስት ይዞታዎች መሀል ዋና ዋና የተባሉትን በሙሉ የተቆጣጠሩት መሆኑ ቢታወቅም በመጀመሪያዎቹ አመታት ግን የካፒታል ችግር እንደነበረባቸው የሚናገሩ አሉ። ለምሳሌ የቀንቲቻ ታንታለም ማይኒንግን በ23.45 ሚሊዮን ዶላር እንዲገዙ በተፈቀደላቸው ወቅት ገንዘቡን በተባለው የጊዜ ገደብ ውስጥ መክፈል ባለመቻላቸው ውሉ ተሰርዞባቸው እንደነበር ይታወሳል።
በሂደት ግን ከባለስልጣናቱ ጋር ያላቸውን ቁርኝት በከፍተኛ ሁኔታ በማጥበቃቸው ልዩ ከለላ የሚደረግላቸው ሰው ሆነው ከመገኘታቸውም በላይ እሳቸውም የኢህአዴግ ድርጅቶችን ለመርዳትና ተቃዋሚዎችን ለማዳከም በከፍተኛ ወጭ ሲንቀሳቀሱ ቆይተዋል።
በተያያዘ ዜና ሼህ መሀመድ የሀገሪቱን የወርቅ ምርት በእጥፍ ያሳድጋል የተባለው አሁን በቅርቡ ያገኙትን የኦኮት የወርቅ ማዕድን ማምረት እንዲችሉ መንገዱን ለመጥረግ መሆኑ በታመነበት ሁኔታ በኦኮትና በአካባቢዋ የሚኖሩ ነዋሪዎች መኖሪያቸውንና ማሳዎቻቸውን ለቀው በአስቸኳይ እንዲወጡ ማስጠንቀቂያ የደረሳቸው መሆኑን በቅርቡ ከሀገር ቤት የወጣ አንድ ሪፖርት አመልክቷል።
ፍኖተ ነጻነት በዚህ ሳምንት እትሙ የአካባቢውን ነዋሪዎች ጠቅሶ እንደዘገበው ከሆነ በደቡብ ኢትዮጵያ በኦሮምያ ክልል ቦረና ዞን ውስጥ ባሉ ሁለት ወረዳዎች ኦኮትን ጨምሮ የተለያዩ አካባቢ ነዋሪዎች የማዕድን ማውጣቱን ስራ ለማመቻቸት በሚል ቀያቸውን ለቀው እንዲወጡ ታዟል።
በተመሳሳይ መልኩ የለጋዳንቢው የወርቅ ማዕድን በሚመረትበት በጉጂ ዞን በሻኪሶ ወረዳ ባሉ በተለያዩ ቀበሌዎች ውስጥ ነዋሪ የነበሩ ዜጎች ያለ ካሳ ተነስተው መፈናቀላቸውን ሪፖርቱ አያይዞ ገልጿል። ፍኖተ ነጻነት ማዕድን ማውጫዎቹ ባሉባቸው አካባቢዎች ነዋሪዎች በውሃ ወለድ በሽታዎች እየተጠቁ ስለመሆኑም ዘግቧል።
ይህንን የሼሁ የማእድን ማውጫዎች በአካባቢ ላይ የሚያደርሱትን ብክለት በተመለከተ ከሁለት አመት በፊት የሻኪሶ ወረዳ ነዋሪዎች ከለገደንቢ የማዕድን ማውጫ የሚደፋው መርዛማ ዝቃጭ የአካባቢውን ወንዝ በመበከሉ በርካታ ነዋሪዎችና እንስሳዎች እየታመሙ ነው በሚል ተቃውሞ ባሰሙ ወቅት የፌደራልና የክልሉ ፖሊሶች ድብደባ እንደፈጸሙባቸውና ከመቶ በላይ ሰዎችንም እንዳሰሩ ከአሜሪካ ኤምባሲ ሾልከው በወጡ ሪፖርቶች ላይ መመስከሩ ይታወሳል። አሁንም በደቡብ ኢትዮጵያ በተያዘው የማፈናቀል ድርጊት ላይ የክልሉ ባለስልጣናት ነዋሪውን በማስፈራራትና በማስገደድ ሚና እየተጫወቱ መሆኑ ተነግሯል።
በተመሳሳይ መልኩ ከጋምቤላ ክልል ከ70 ሺህ በላይ ነዋሪዎች በግዳጅ እንዲፈናቀሉ ምክንያት ከሆኑት ካምፓኒዎች መሀል ሳውዲ ስታር የተባለው የሼሁ ድርጅት አንዱ ሲሆን የድርጅቱ ሰራተኞችን በተቆጣው ህዝብ የበቀል እርምጃ እንዳይወሰድባቸው ሲባል መንግስት ከፍተኛ ጥበቃ እያደረገላቸው መሆኑ ሲዘገብ ሰንብቷል።



