"ኢትዮጵያዊያን በፍርዱ ረክተዋል" ወ/ሮ ሙሉመቤት ረታ (በሲያትል የኢትዮጵያ ኮሚኒቲ ሊቀመንበር)

"በእኔ አስተያየት ፍትህ ተበይኗል፤ ዳኛዋም ሆኑ ፍርድ ሰጭዎቹ (ጁሪዎቹ) በትክክል ጉዳዩን አይተው ወስነዋል ብየ አምናለሁ" ዶ/ር ሸክስፒር ፈይሳ

Ethiopia Zare (ረቡዕ ጥቅምት 20 ቀን 2006 ዓ.ም. October 30, 2013)፦ ከሁለት ዓመት በፊት ሃና ዊሊያምስ የተባለችውን ታዳጊ በቅዝቃዜ ደጅ ላይ በማዋልና በማሳደር አሰቃይተው ገድለዋል የተባሉት አሳዳጊዎቿ ኬሪ ዊሊያምስና ባለቤቷ ላሪ ዊሊያምስ የ37 ዓመትና የ29 አመት ጽኑ እስራት የተወሰነባቸው ሲሆን በሲያትል አካባቢ የሚኖሩ ትዮጵያዊያን በፍርዱ መደሰታቸውን በተለይ ለኢትዮጵያ ዛሬ ገለጹ።

 

በሲያትል የኢትዮጵያ ኮሚኒቲ ሊቀመንበር ወ/ሮ ሙሉመቤት ረታ እንደገለጹት የፍርዱን ሂደቱ ለሁለት አመታት ኢትዮጵያዊው ማህበረሰብ ከከተማዋ ራቅ ብሎ በሚገኘው ቦታ ድረስ በኮሚኒቱው መለስተኛ ማመላለሻና በግል መኪኖች በመመላለስ ሲከታተል መቆየቱን ገልጸዋል።

"የጥፋተኝነት ውሳኔ ሰጭዎቹ (ጁሪዎቹ) በርካቶቹ የዊሊያምስ ቤተሰቦች ከሚኖሩበት አካባቢ በመሆኑና በተጓዳኝ ጉዳዮች ምክንያት የፍርድ ሂደቱ ይዛባ ይሆናል የሚል ፍራቻ ነበር' ያሉት ወ/ሮ ሙሉመቤት ውሳኔ ሰጭዎቹ ግን በሙሉ ድምጽ የኬሪንና የላሪ ዊሊያምስን ጥፋተኝነት መወሰናቸው በርካቶችን አስደስቷል" ብለዋል።

በተለይ ዳኛዋ እንደገለጹት ከሆነ ሁኔታው አልተፈጸመም የሚል ጥርጣሬ እንደነበራቸው ገልጸው በተለይ በጉዲፈቻ ለማሳደግ ከሃና ጋር ያመጡትን ህጻን አማኑኤልን ጨምሮ የኬሪና የላሪ ዊሊያምስ ከ13 እስከ 16 የሚደርሱ ህጻናት ልጆቻቸው ሲመሰክሩ ድርጊቱ በቤተሰቡ ውስጥ የተለመደ መሆኑንና ምንም ሳይሰማቸው "ቀዝቃዛ ውሃ እንደፋባቸዋለን፣ ውጭም በቅዝቃዜ እንቀጣቸዋለን ሲሉ መስማታቸው ሃሳባቸውን እንዳስለወጣቸው ገልጸው ውሳኔውን ግራና ቀኝ በመመልከት ክሱ ከሚጠይቀው በላይ የመጨረሻውን ፍርድ የ37 ዓመት ፍርድ ለኬሪ ዊልያምስ ሰጥተዋል። ባለቤቷ ሌሪ ዊሊያምስ በጥቅሉ 29 ዓመት ሲወሰንበት ሁለት አመት በእስር ላይ በመቆቱ ቀሪው 27 አመት እንደጸናበት ለማወቅ ተችሏል።

"በእኔ አስተያየት ፍትህ ተበይኗል። ዳኛዋም ሆኑ ፍርድ ሰጭዎቹ (ጁሪዎቹ) በትክክል ጉዳዩን አይተው ወስነዋል ብየ አምናለሁ።' ያለው በሲያትል ነዋሪ የሆነው የህግ ጠበቃ ዶ/ር ሸክስፒር ፈይሳ "እንደ ጠበቃ በአሜሪካ የፍርድ ሂደት ላይ ብዙ ጥያቄ ያለኝና ጥርጣሬውም ቢኖረኝም በሃና ጉዳይ ላይ ግን ፍትህ ቦታውን አግኝቷል። ዳኛዋ ያቀረቡት የፍርድ ማጠቃለያም እጅግ የሚያሳዝንና ጉዳዩን በጥልቀት የመረመሩ መሆናቸውንና ማስረጃው የሚደግፈው መሆኑን ያመላክታል።" ሲል አስተያቱን ገልጿል።

ከፍርዱ በኋላ ኢትዮጵያዊያኑና የደረሰባት ጥቃት አግባብ አይደለም ያሉ ወገኖች በጉዩዲፈቻ በአሳዳጊዎቿ ከኢትዮጵያ ወጥታ፤ በአሳዳጊዎቿ የደረሰባትን ጥቃትና እንግልት መቋቋም ባለመቻሏ ህይወቷ ያለፈው ሃና ዊሊያምስ የመቃብር ቦታ በመሄድ ሻማ ማብራት ስነስርአት እንደተደረገና በተለያዩ ምክንያቶች በመጨረሻ ውሳኔ ላይ ላልተገኙ ወገኖችም የሻማ ማብራትና የውሳኔውን ሂደት ለማሰብ በሲያትል የኢትዮጵያ ኮሚኒቲ አዳራሽ ተገኝተው ሃና ስትታሰብ ማምሸቷን ወ/ሮ ሙሉመቤት ለኢትዮጵያ ዛሬ ገልጸዋል።

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ