ፈረሰኛ ሻምበል ማሩ መልካ Maru Melkaየቀብር ስነ ስርአታቸው ዛሬ በየካ ሚካኤል ይፈጸማል

Ethiopia Zare (ረቡዕ ታህሣስ 30 ቀን 2006 ዓ.ም. Jan 8, 2014)፦ በፈረስ ግልቢያ ስፖርት ታሪክ ውስጥ በአስተማሪነት፣ በስፖርተኝነትና በርካታ ሽልማቶችን በመቀዳጀት ግምባር ቀደም ተጠቃሽ የሆኑት ፈረሰኛ ሻምበል ማሩ መልካ በ87 ዓመታቸው ታህሣስ 29 ቀን 2006 ዓ.ም ከዚህ አለም በሞት የተለዩ ሲሆን ዛሬ የቀብር ስነ ስርአታቸው በአዲስ አበባ የካ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን እንደሚፈጸም ተገለጸ።


ፈረሰኛ ሻምበል ማሩ መልካ Maru Melka
ሻምበል ማሩ መልካ በኢትዮጵያ የፈረስ ግልቢያ ታሪክ ውስጥ ትልቅ አሻራ ያኖሩ ከመሆናቸውም በላይ በአገር አቀፍና አለማቀፍ ውድድሮች ላይ በመሳተፍ በአጠቃላይ 300 የሚደርሱ ከፍተኛ ሽልማቶችን በአሸናፊነት የተቀዳጁ ሲሆን ከ114 ጊዜ በላይ አንደኛ በመውጣት የከፍተኛ ሜዳሊያ ተሸላሚ እንደነበሩና በ42 የተለያዩ ውድድሮች ደግሞ ሁለተኛ ደረጃን በማግኘት እንደዚሁም ከ15 ጊዜ በላይ ሶስትኛ ደረጃ በመውጣት ሽልማቶችን አግኝተው እንደነበር ለመረዳት ችለናል።

ፈረሰኛ ሻምበል ማሩ መልካ ከአጼ ኃይለሥላሴ እጅ ሽልማት ሲቀበሉ ሻምበል ማሩ ህይወታቸውን በተለይ ከሚወዷቸው የውድድር ፈረሶች ጋር ያሳለፉ ሲሆን ቀድሞ ይሰሩበት ከነበረውና በርካታ ውድድሮችን በማድረግ ከሚታወቁበት ባልደራስ በጡረታ ከወጡ በኋላ በጣሊያን ኤምባሲ ፈረሰኞችን በማሰልጠንና ፈረሶችን ለውድድር በማዘጋጀት ህይወታቸው እስካለፈበት ጊዜ ድረስ በስራ ላይ እንደነበሩ ታውቋል።

የ9 ልጆች አባት እንደነበሩ በተለይ ለኢትዮጵያ ዛሬ የገለጹት ቤተሰቦቻቸው ሻምበል ማሩ መልካ 32 የልጅ ልጆችን እና 18 የልጅ ልጅ ልጆችን ለማየት የታደሉ የእድሜ ባለጸጋ እንደነበሩ ለማወቅ ተችሏል።


ፈረሰኛ ሻምበል ማሩ መልካ Maru Melka
ህይወታቸውን ለኢትዮጵያ የፈረስ ስፖርት እድገት ሲጥሩና እስከ 87 ዓመት የህይወት ፍጻሜያቸው ጊዜ ድረስ በስራ ገበታቸው ላይ ያሳለፉት የፈረስ ስፖርት አባት ሻምበል ማሩ መልካ ህይወት ማለፍ የተሰማንን ሀዘን እየገለጽን ለመላ ቤተሰቦቻቸውና አድናቂዎቻቸው ሁሉ መጽናናትን ታገኙ ዘንድ እንመኛለን።
ኢትዮጵያ ዛሬ

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ