ንግድን በማስተጓጐል እርምጃ የተወሰደባቸው ከ25 ሺሕ በላይ ደረሱ
የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ አቶ መላኩ አለበል
420 ታስረዋል፤ 890 የንግድ ፍቃዳቸው ተሰርዟል፤ 13,500 የንግድ ድርጅቶች ታሽገዋል
ኢዛ (ረቡዕ ሚያዝያ ፲፬ ቀን ፳፻፲፪ ዓ.ም. April 22, 2020)፦ ከኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ጋር በተያያዘ የንግድ እንቅስቃሴውን አስተጓጉለዋል በሚል የተለያዩ እርምጃዎች የተወሰዱባቸው የንግድ ድርጅቶች ቁጥር ከ25 ሺሕ በላይ መድረሱ ተገለጸ።
ዛሬ ከወቅታዊ ጉዳዮች ጋር በተያያዘ የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ አቶ መላኩ አለበል በሠጡት መግለጫ፤ የንግድ ተግባሩን አስተጓጉለዋል ተብለው እርምጃ የተወሰደባቸው 25,068 ሲሆኑ፤ ከዚህ ውስጥ 13 ሺሕ 350 የንግድ ድርጅቶች እንዲታሸጉ መደረጉን ጠቅሰዋል።
404 የንግድ ድርጅቶች ደግሞ ፍቃዳቸው መታገዱን ይኸው የሚኒስትሩ መግለጫ ያመለክታል። የተወሰደው እርምጃ የንግድ ፍቃድን እስከመሰረዝ የደረሰ ሲሆን፤ እስካሁን 890 የንግድ ፍቃድ መሰረዙን ለማወቅ ተችሏል።
በ10 ሺሕዎች ለሚኾኑት ደግሞ ማስጠንቀቂያ ስለመሠጠቱም መግለጫው ያትታል። እርምጃ ከማስጠንቀቂያ ጀምሮ እስከ እስርና ንግድ ፍቃድ መሰረዝን ያጠቃለለ በመኾኑ፤ በሰሞኑ እርምጃ 420 የሚኾኑ ግለሰቦችም በዚህ ንግድን በማስተጓጐል ክስ መታሠራቸው ተገልጿል። (ኢዛ)



