ሕገወጥ የጦር መሣሪያ ዝውውር ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከክልሎች ጋር መክረዋል

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ
አዘዋዋሪዎችን ለመቆጣጠር ሁሉን አቀፍ ስምሪት ያስፈልጋል ብለዋል
ኢዛ (ሐሙስ ግንቦት ፮ ቀን ፳፻፲፪ ዓ.ም. May 14, 2020)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ከክልል አመራሮች ጋር ባደረጉት ውይይት በሕገወጥ መንገድ የጦር መሣሪያን ማስገባትና መዘዋወርን ለመግታት፤ እንዲሁም አዘዋዋሪዎችን በቁጥጥር ስር ለማዋል የሁሉንም ስምሪት እንደሚጠይቅ አስታወቁ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ትናንት በዚሁ ጉዳይ ላይ ከክልል አመራሮች ጋር ያደረጉትን ውይይት አስመልክተው ዛሬ ሐሙስ ግንቦት 6 ቀን 2012 ዓ.ም. በፌስቡክ ገጻቸው ላይ እንዳመለከቱት፤ ሕገወጥ የጦር መሣሪያ ዝውውርን ለመከታተልና አዘዋዋሪዎችን በቁጥጥር ስር ለማዋል የሁሉንም ስምሪት እንደሚጠይቅ እና ለዚህም ትብብር ማጠናከር እንደሚገባ መነጋገራቸውን ገልጸዋል።
ባለፉት ጥቂት ወራት ሕገጥ የጦር መሣሪያ አዘዋዋሪዎችን ተከታትሎ በመያዝ አኩሪ ሥራ መሥራቱንም የሚያመለክተው ይኸው መረጃ፤ ከእያንዳንዱ ምንጭ ወደ አገር የሚገባውን የመሣሪያ ዝውውር በአግባቡ ለመከታተል እና ሕገወጥ መሣሪያ አዘዋዋሪዎችን በቁጥጥር ሥር ለማዋል ተቀናጅቶ መሥራት አስፈላጊነት ላይ መምከራቸው ታውቋል። (ኢዛ)