በወ/ት ብርቱካን የሚመራው ላዕላይ ምክር ቤት ነገ አርብ ይሰበሰባል
Ethiopia Zare (ሐሙስ የካቲት 20 ቀን 2000 ዓ.ም. February 28,2008)፦ የቅንጅት ለአንድነትና ለዲሞክራሲ ፓርቲ በተ/ም/ሊ ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ የሚመራው የላዕላይ ምክር ቤት ነገ አርብ ስብሰባ እንደሚያካሂድ ታማኝ ምንጮች ጠቆሙ።
ምክር ቤቱ ታህሳስ 20 ቀን 2000 ዓ.ም. ተሰብስቦ፤ ሥራ አስፈፃሚው የፓርቲውን ሕጋዊነት በሚመለከት አማራጭ ሃሳብ ይዞና በተጓደሉት አባላት ምትክ ምርጫ አካሂዶ እንዲመጣ ውሳኔ አስተላልፏል።
በዚህም መሠረት ምክር ቤቱ የሥራ አስፈፃሚውን ሪፖርት ለመስማት በነገው ዕለት የሚሰበሰብ ሲሆን፣ ሥራ አስፈፃሚው በተጓደሉት ምትክ ምርጫ አድርጎ 16 አባላትን መምረጡን መዘገባችን አይዘነጋም።
ፕሮፌሠር መስፍንን ጨምሮ የተመረጡት አስራ ስድስት የምክር ቤቱ አባላት ከነባር አባላት ጋር ትውውቅ የሚያደርጉ ሲሆን፣ የፓርቲውን ቀጣይ ሁናቴ የሚተልሙ መሆኑን ዛሬ የደረሰን ዘገባ ያስረዳል።
ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው የፓርቲውን ሕጋዊነት በሚመለከትና ፓርቲውን በአዲስ ስም የማስመዝገብ ውሳኔውን ለምክር ቤቱ እንሚያሳውቅ የሚጠበቅ ሲሆን፣ ምክር ቤቱ የመሰብሰቢያ ቦታና ቢሮ በማጣት በተለያዩ ጊዜያት አቅዶ የነበረውን ስብሰባ ለመሰረዝ የተገደደ መሆኑ የተዘገበ ከመሆኑም በላይ፤ የቤት አከራዮች ከተስማሙ በኋላ የደህንነት ሰዎች በሚያደርጉባቸው ዛቻና ማስፈራራት የውል ሰነድ ለመፈረም ፈቃደኛ ሊሆኑ እንዳልቻሉ ለመረዳት ችለናል።
ተያያዥ ዜናዎች



