ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ Journalist Temesgen Desalegnተመስገን ደሳለኝ
"በአፍሪካ ትልቁ አምባገነን" የሚል ተቀፅላ የተሰጣቸው የሊቢያው ኮሎኔል መሀመድ ጋዳፊ እና የግብፁ ሆስኒ ሙባረክ በህዝባዊው እምቢተኝነት ከሥልጣን መነሳታቸው በመሰል አገዛዞች ስር ያደሩ ሕዝቦችን ለለውጥ ማነቃቃቱ የሚጠበቅ ነው። በተለይም ከራሳቸው መንግሥት ተኳርፈው አስተማማኝ የዲሞክራሲ ተቋማትን በገነቡ የምዕራብ ሀገራት በብዛት የሚኖሩ ዜጎች ላሏት ኢትዮጵያ ንቅናቄው የፈጠረው ተመሳሳይ መነሳሳት ቀላል ባለመሆኑ ኢህአዴግን ሊወጣው ከማይችለው ቅርቃር ውስጥ ከቶታል። የዚህ ተጠየቅም ቀድሞ እንዲህ አይነት ችግሮች ሲፈጠሩ ድርጅቱ 'እሳት ማጥፊያ' ያደርጋቸው የነበሩ አጀንዳዎቹ ያለፈባቸው (Expired) መሆናቸውን ማሳየት ነው።

 

ሰባቱ "ቀኖና"ዎች

ሥርዓቱ ከሃያ ሁለት ዓመታት በላይ በሥልጣን የመቆየቱ ምስጢር ከሁለት ምንጭ የሚቀዳ ነው። አንዱ የታዘዘውን ሁሉ ያለ ምንም ማንገራገር የሚፈፅመው ጠመንጃ አንጋቹ (መከላከያ ሰራዊት፣ ፌደራል ፖሊስ እና የደህንነት መዋቅሩ) ሲሆን፤ ሌላኛው ደግሞ ከፖለቲካው ፍልስፍና የሚወረሱ አጀንዳዎቹ ናቸው፤ ይሁንና ለጊዜው የታጠቀውን ኃይል ወደ ጎን ብለን ሥርዓቱ "የፖለቲካዬ መገለጫዎች" ብሎ እንደ ቀኖና ይዟቸው የነበሩትን ሰባት ጉዳዮች በደምሳሳው ብንቃኝ የመቃብር አፋፍ ላይ የቆመ ሥርዓት ስለመሆኑ የማመላከት አቅም አላቸው ብዬ አስባለሁ።

 

፩. የገጠር ፖሊሲ

ኢህአዴግን የሦስት ፓርቲዎች ግንባር አድርጎ በመመስረቱ ሂደት የአንበሳውን ድርሻ የሚወስደው፣ በሀገሪቱ ከሚገኙ የገጠር ከተሞች ከሽሬ ጋር በሚዋሰነው "ደደቢት በርሃ" ላይ የተመሰረተው ህወሓት ሲሆን፣ መስራቾቹም ሆኑ አብዛኛው አባላቱ ከአርሶ አደሩና የገጠር አካባቢዎች የወጡ ናቸው። የህወሓት የታሪክ ንባብ እንደሚያረጋግጠው ትጥቅ ትግል ያስፈለገበት ዋነኛ ምክንያቶች ሁለት ነበሩ፤ የብሔር ጭቆናን እና የትግራይ አርሶ አደር ለአስከፊ መከራ ተዳርጓል የሚል።

ድርጅቱ ለትግል ካሰለፋቸው አባላቱ ሁለት ሶስተኛው ከእርሻ ሥራ በቀጥታ የተቀላቀሉ ስለመሆናቸው ድርሳናቱ ያወሳሉ። በወቅቱ በተድበሰበሰ መልኩ የቀረፁት የፖለቲካ ፕሮግራም በመሬትና በብሔር ጥያቄ ላይ የተንጠለጠለ እንደነበር ይታወቃል፤ ይሁንና ከትምህርት ገበታ ተሰውረው፣ በረሃ የገቡት ወጣቶች ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ ምናልባትም "'መሬት የመንግሥት ነው' የሚለው ፖሊሲያችን የሚቀየረው በመቃብራችን ላይ ነው" ወደሚል ኦሪታዊ የፖለቲካ አቋም (ቀኖና) የተመለሱት የኢትዮጵያ ተማሪዎች የ"መሬት ላራሹ"ን ትግል ጠልፎ ወደሥልጣን የመጣው ደርግ፣ ህወሓት በተመሰረተ ልክ በአስራ አራተኛው ቀን የካቲት 25 ቀን 1967 ዓ.ም መሬትን በተመለከተ መሬትን ያራሹ ባደረገው አዋጅ የሰጠው ምላሽና ያገኘው ድጋፍ ሌላ አማራጭ የነፈጋቸው ይመስለኛል (ህወሓት የተመሰረተው የካቲት 11 ቀን 1967 ዓ.ም መሆኑን ልብ ይሏል) በነገራችን ላይ ለኢትዮጵያውያን ፖለቲከኞች መሬት ከኢኮኖሚ ይልቅ ፖለቲካዊ ጠቀሜታው እንደሚበልጥ በርካታ ማሳያዎች አሉ።

የሆነ ሆኖ ከኢህዴንና ኦህዴድ ጋር ተጣምሮ ኢህአዴግን የመሰረተው ህወሓት በ1983 ዓ.ም ለመንግሥታዊ ሥልጣን መብቃቱን ተከትሎ ራሱን 'የኢትዮጵያ አርሶ አደር ነፃ አውጪ' አድርጎ አስተዋውቋል። በተጨማሪም "በቅዱስ መፅሀፌ 'አብዮታዊ ዲሞክራሲ' መርህ መሰረት የቀመርኩት" የሚለውን "ገጠርን እና ግብርናን ማዕከል ያደረገ የልማት እስትራቴጂ" በፖሊሲ ደረጃ ከማውጣቱም በተጨማሪ በተለያየ ጊዜ ባሳተማቸው መጻህፍት እና ጥናቶች የአርሶ አደሩን ህይወት በከፍተኛ ደረጃ እየቀየረው እንደሆነ ለማስረዳት ሞክሯል። በአናቱም ሀገሪቱ ያላት ሀብት የሰው ኃይልና መሬት መሆኑ ለሚከራከርበት ንድፈ-ሃሳብ ቅቡልነት አስተዋፅኦ ያደረገ ይመስለኛል።

በቀዳሚዎቹ ሦስት ሀገር አቀፍ ምርጫም አፅንኦት ሰጥቶ የተሟገተው "ለአርሶ አደሩ የምታገል ፓርቲ ነኝ" እና "አርሶ አደሩ ይደግፈኛል" የሚል እንደነበረ ይታወሳል። ይሁንና በምርጫ 97 በከተሞች በደረሰበት ያልተጠበቀ ሽንፈት እንዲያ ከበሮ የደለቀለትን "ገጠርና ግብርናን ማዕከል ያደረገ የልማት ስትራቴጂ" ለድንገቴ (አልቦ ቅድመ-ዝግጅት) ለውጥ ይዳርገ ዘንድ መገደዱን የሚጠቁሙ ምልክቶች እየታዩ ነው (የትራንስፎርሜሽን እቅዱ፣ የአባይ ግድብ፣ የመከላከያ ኢንዱስትሪ እና የኮንዶምኒየም ቤቶች ግንባታ የተበጀተላቸው ባጀት ሥርዓቱ በአዋጅ የነገረንን የገጠር ልማት ፖሊሲ፣ ያለኮሽታ መቀየሩን ያመላክታል) የአብዮቱን የምፅአት ቀን ካቃረቡት ዋነኛ ምክንያቶች አንዱ ነው።

 

፪. የብሔር ጥያቄ

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ የህወሓት መስራቾች በርሃ ለመግባት ሌላኛው ዋና ምክንያት "ነፃ የትግራይ ሪፕብሊክ"ን ለመመስረት ቢሆንም በጊዜው በአቅራቢያቸው የሚንቀሳቀሰው ኢህአፓ ይህንን ሴራ ኢትዮጵያዊ ብሔርተኝነትን ለሚያስቀድመው የአካባቢው ህዝብ በማጋለጥ ትልቅ የፖለቲካ ኪሳራ ስላደረሰባቸው የ"ነፃነት" ጥያቄያቸውን ወደ "የብሔር ጭቆና" እንዲቀይሩ መገደዳቸውን በጉዳዩ ዙሪያ የተዘጋጁ በርካታ ድርሳናት አጋልጠውታል። ከድርጅቱ በተለያዩ ምክንያቶች የወጡ የአመራር አባላትም በፃፏቸው 'ገድሎች' እንደአተቱት ከዚህ በኋላ ነው "በሀገሪቱ የአንድ ብሔር የበላይነት ነግሷል" የሚለው ተረታ ተረት በማርክሲዝምና ሌኒንዝም አስተምህሮ ተተንትኖ በማጎን የድጋፍ መቀስቀሻ የተደረገው። የሆነ ሆኖ ለህወሓት መደርጀት ዋናው ምክንያት ተጋኖ የተቀነቀነው የጎጠኝነት ፕሮፓጋንዳ ሳይሆን፣ የወታደራዊው ደርግ ጭካኔ የተሞላበት ጭፍጨፋና አፈና ያስመረረው በሙሉ በቅርብ ያገኘውን የፋኖዎች ድርጅት መቀላቀል መምረጡ እንደነበር ከጊዜው ንባብ መረዳት ይቻላል።

ከድል በኋላ ኢህአዴግ የቀድሞውን "አሀዳዊ መንግሥት" በብሔር ላይ ወደ ተመሰረተ የ"ፌደራል መንግሥት" ያስቀየረኝ መግፍኤ "በኢትዮጵያ አስከፊ የብሔር ጭቆና መንበሩ ነው" የሚለው መከራከሪያውን ዛሬም ድረስ እንደ በቀቀን ሲደጋግመው ይደመጣል። የግንቦት ሃያ ድልን ተከትሎ ሀገሪቱን የአፍ መፍቻ ቋንቋን መስፈርት ባደረገ ቀመር በዘጠኝ ክልላዊ መንግሥት እና በሁለት ራስ ገዝ ከፍሎ ማስተዳደሩ ለብሔር ጭቆና የማያዳግም መፍትሄ ቢያስመስለው፣ ዛሬም ድረስ በምርጫ ቦርድ ተመዝግበው በሰላማዊ መንገድ ከሚታገሉ ተቃዋሚ ፓርቲዎች መካከል አርባ አራቱ "የብሄራችን ጥያቄ ገና አልተመለሰም" በሚል ሀቲት በብሔር የተደራጁ መሆናቸው፤ በኦሮሚያ፣ በሶማሊያ እና ጋምቤላን መሰል አካባቢዎች ደግሞ ጠመንጃ ያነሱ የብሔር ድርጅቶች መኖራቸው ሥርዓቱ በብሔር ጥያቄ ረገድ የታሪክ ፈተናን ማለፍ እንደተሳነው መረዳት ይቻላል።

በኢትዮጵያ ሰማይ ስር የብሔር ጥያቄ 'ዳግም ላይነሳ መልስ አግኝቷል' ትርክት ምፀት የሚሆነው በሀገሪቱ ከሚገኙ ክልሎች በብዙ እጥፍ ያነሰ የህዝብ ቁጥር ያለው ሐረሪ፣ የኢህአዴግ አጋር የሆነው "የሐረሪ ዲሞክራሲያዊ ድርጅት-ሐዲድ"ን ጨምሮ "የሐረሪ ህዝብ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ-ሐሕዴፓ" እና "የሐረሪ ብሔራዊ ሊግ-ሐብሊ" የተሰኙ የፖለቲካ ድርጅቶች መኖራቸው ነው (በአፋርም አራት ህጋዊ የፖለቲካ ድርጅቶች አሉ) እነዚህ እውነታዎች ለሥርዓቱ ክሽፈትና የአብዮቱ የምፅአት ቀን በጣም የተቃረበ ለመሆኑ በቂ ምልክቶች ናቸው።

 

፫. የኢኮኖሚ ዕድገት

ኢህአዴግ ሥልጣን ላይ በወጣበት የመጀመሪያዎቹ ዓመታት የቀድሞ ሊቀ-መንበሩ "ህዝባችን በቀን ሶስቴ እንዲበላ እናደርጋለን" ብሎ በአደባባይ ቃል መግባቱም ሆነ "በአጭር ጊዜ ውስጥ መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገራት ተርታ ያቆመኛል" በሚል ሽፋን ሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶችን የደፈጠጠበት የ"ልማታዊ መንግሥት" ጩኸቱ አለመሳካት ሌላኛው የአደባባይ ተቃውሞን የሚጋብዝ ነው። የስራ አጥ ቁጥር አለቅጥ መጨመር እና የዋጋ ንረትን መቆጣጠር አለመቻሉም የምፅአት ቀኑን መቃረብ አብሳሪ 'ሰይጣን' ከአንዳች ሸለቆ መቀሰቀሱ አይቀሬ ነው፤ የዶ/ር መረራ ጉዲና "የሚበላውን ያጣ ህዝብ መሪዎቹን ይበላል" ትንቢትም የሚያመላክተው ይህንኑ ነው።

በሀገሪቱ ከፍተኛ ተከታይ ካላቸው ዋነኛ ኃይማኖቶች መካከል እስልምና አንዱ ነው። እንደኃይማኖቱ ልሂቃኖች ምስክርነት ኢህአዴግ የእምነቱን ተከታዮች መብት ለማክበር ከቀድሞ አገዛዞች የተሻለ ውጤት አለው። ይሁንና በምትኩ ከምዕመኖቹ ያገኘው ጠንካራ የፖለቲካ ድጋፍ ብቻውን ያረካው አይመስልም። ምክንያቱም ከተባባሪዎቹ የመጅሊስ መሪዎች ጋር በመመሳጠር ኃይማኖቱን 'አጋር ፓርቲ' አድርጎ እስከ መቁጠር ደርሷልና።

በርግጥ አብዛኛው ሙስሊም ያለፉትን አራት ሀገር አቀፍ ምርጫዎች ግንባሩን ከመምረጥ አልፎ በየመስጂዱ ከሶላትና ፀሎት በኋላ "ኢህአዴግን ምረጡ" የሚሉ ድምፆች በርክተው እንደነበር ዛሬ በአገዛዙ ላይ የመረረ ተቃውሞ ከሚያሰሙ ምዕመናን አረጋግጫለሁ። ... 'ታሪክ ራሱን ይደግማል' እንዲሉ የዘርፉ ምሁራን አገዛዙ እንደነገስታቱ ዘመን በእስልምና አስተምህሮት ላይ ጣልቃ በመግባቱ ከ2003 ዓ.ም. ታህሳስ ወር ጀምሮ በሚሊዮን የሚቆጠሩ የእምነቱ ተከታዮች "መንግሥት በሃይማኖታችን ጣልቃ መግባቱን ያቁምልን!" በማለት ላቀረቡት ጥያቄ ምላሹ በታጠቀው ኃይል በመሆኑ ለከፋ መስዋዕትነት ተዳርገዋል።

ይህ አይነቱ መንግሥታዊ ሽብርተኝነት ከቀን ቀን እየሰፋና እየጠነከረ በመሄድ ላይ ነው። እውነታውን የሚያብራራ አንድ ገጠመኜን እዚህ ጋ ላንሳ። ይኸውም ባለፈው ቅዳሜ (ነሐሴ 14 ቀን 1967 ዓ.ም.) ከጠዋቱ አራት ሰአት ተኩል አካባቢ የቤቴ በር ጠንከር ባለ መዳፍ ተደጋግሞ ሲቆረቆር ከፈትኩት፤ የፖሊስ መለዮ ከለበሰ ወጣት ጋር ተፋጠጥን፤ "ምን ነበር?"

"የቤቱ ባለቤት አንተ ነህ?"
"አይ! እኔ ተከራይ ነኝ"
"የሚሞላ ፎርም ስለያዝኩ ጥቂት ጥያቄዎችን ላቀርብልህ ነው!"

"ግባ!" ገብቶ ከተቀመጠ በኋላ ስለመጣበት ጉዳይ ከማውራቱ በፊት እንዲህ አለኝ፡-
"አንድ ነገር ልምከርህ፤ የደንብ ልብስ የለበሰውን በሙሉ መታወቂያ ሳታይ አመነህ ወደ ቤትህ አታስገባ!"
"ለምን?"
"አክራሪዎቹ የፖሊስ ልብስ ለብሰው ወንጀል እየፈፀሙ ነው"

... በጣም አዘንኩ፤ ይህ አገዛዙ ከእስልምና ውጪ ያለውን ህዝብ በእምነቱ ላይ በጥላቻ እንዲነሳሳ (እርስ በእርስ እንዲበላላ) ምን ያህል ዕርቀት እየተጓዘ እንደሆነ የሚያሳይ ኃላፊነት የጎደለው ድርጊት ነው። ...ሁሉም ጉዳይ ጊዜው ያለፈበት መሆኑ በጀ እንጂ፣ የባለሥልጣናቱ ፍላጎት ግልፅ ነው። ኩነቱ ግን ለግንባሩ መዳከም ከፍተኛ አስተዋፅኦ ሲያደርግ፣ ለለውጥ ፈላጊው ደግሞ ታላቅ ድል መሆኑ ነው።

 

፭. የምዕራብ ሀገራት ድጋፍ

በ1980ዎቹ መጨረሻ አካባቢ የአሜሪካ ዲፕሎማቶች መለስ ዜናዊን እና ኢሳያስ አፈወርቂን "አዲሱ የአፍሪካ መሪዎች ትውልድ" የሚል ካባ ይደርቡላቸው የነበረበት ያ "ደግ" ዘመን እንደዋዛ አልፏል፤ ኢህአዴግ፣ የሻዕቢያን ያህል ከምዕራባውያኑ ጋ ወደለየለት ጠላትነት ደረጃ ባይደርስም፣ እንደቀድሞ ባደናቀፈው ቁጥር "እኔን!" ብለው በሚነጠፉለት አይነት 'ፍቅር' ላይ አለመሆኑ ግን እርግጥ ነው፤ በተለይም የ1997ቱን ድህረ ምርጫ ተከትሎ ከቅንጅት አመራርና አባላት ጋር የተከሰተው አለመግባባት የፈታበት መንገድ፣ ሀገራቱ በኢትዮጵያ ላይ የሚከተሉትን የግንኙነት ፖሊሲ ቆም ብለው እንዲከልሱ አድርጓቸዋል። የአውሮፓ ህብረት፣ ስዊዲንና ኖርዌይ ደግሞ ጠንከር ያለ አቋም እንዲይዙ አስገድዷቸዋል። ይህ ሁኔታ ኢትዮጵያን በመሰለ ነጭ ደሀ ሀገር ላይ የሚያስከትለው ጉዳት 'በሌላ መንገድ እቀርፈዋለሁ' ወይም 'ራሴ እወጣዋለሁ' የሚሉት አይነት አይደለም (ከባጀቱም አብዛኛው በእነርሱ እርዳታ እና ብድር ላይ የተመሰረተ መሆኑ ሳይዘነጋ ማለት ነው)

ከአንድ ወር በፊት በአውሮፓ ህብረት ፓርላማ "የሰብዓዊ መብት ጉዳዮች ንዑስ ኮሚቴ"ን ወክለው በኢትዮጵያ ከሰብዓዊ መብት መጣስ ጋር ተያይዘው የሚሰሙ ችግሮችን ለመፈተሽ የአራት ሀገራት ተወካዮች ያሉበት አንድ የልዑካን ቡድን መጥቶ ነበር፤ ይህ ቡድን ከመንግሥት ባለሥልጣናት ጋር በተወያየበት ጊዜም ለፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር አንድ ጥያቄ አቀረበ። "ቃሊቲ ማረሚያ ቤት የሚገኙ የህሊና እስረኞችን መጎብኘት እችላለሁን?" የሚል። ጥያቄውም ተቀባይነት በማግኘቱ ቡድኑ ወዳዘው አመራ፤ ይሁንና ቃሊቲ ያሉ የፖሊስ ባለሥልጣናት የልዑኩን ቡድን ጉብኝት እንዳያደርግ በመከልከል 'ኩም' አድርገው በመጣበት እግሩ መልሰውታል። በሁኔታው በእጅጉ የተበሳጩት የቡድኑ አባላትም ዕለቱኑ "በሂልተን ሆቴል" በሚል ርዕስ በበተኑት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ በሥርዓቱ ተፈፅመዋል ያሏቸውን ወደ ስምንት የሚደርሱ አንኳር ችግሮች ከዘረዘሩ በኋላ፤ በእስር ላይ የሚገኙት ጋዜጠኞች፣ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና አባላት፣ እንዲሁም ከኃይማኖት ጋር በተያያዘ የታሰሩ ሰዎች እንዲፈቱ ጠንከር ባሉ ቃላት ጠይቀዋል። ይህ ሁኔታም ከአሜሪካ ጋር የነበረው የሲሲሊያ ማፊያ "የጡት አባት" አይነት ግንኙነቱ ወደ መናፈቅ እየተቀየረ ለሄደበት ሥርዓት ፍጻሜውን ለማቅረብ መልካም የሚባል አጋጣሚ ይመስለኛል።

 

፮. የዲሞክራሲ ተቋማት ያለመኖር

ዲሞክራሲን ባህል ባደረጉ ሀገራት የሚኖሩ ህዝቦች ለደህንነትም ሆነ ለህግ የበላይነት ዋስትና የሚያገኙት በምርጫ ካርድ ውስን ለሆነ ጊዜ በሥልጣን ላይ የሚፈራረቁ ፓርቲዎች ሳይሆን ቀድመውንም ተደላድለው በታነፁ የዲሞክራሲ ተቋማት ነው።

በኢትዮጵያ አስቸጋሪ ጉዳዮች አንዱ በዚህ በኩል የተሰራ ሥራ አለመኖሩ ነው። ኢህአዴግ ለዲሞክራሲ ተቋማት ያለመታከት እየሰራ እንደሆነ ለማደናገር ይሞክርበት የነበረው መክራከሪያው መክሸፉን ለማረጋገጥ፡- ህገ-መንግሥቱን ራሱ በጠራራ ፀሀይ ደጋግሞ መገርሰሱ፣ ነፃ የፍትህ ሥርዓት አለመኖሩ፣ ራሱ የፈጠረውን ነፃ ፕሬስ መልሶ መብላቱ፣ የነፃ ምርጫ ቦርድ እጦት፣ እያቆጠቆጠ የነበረው የብዙሃን ፓርቲ ሥርዓት በ2002ቱ ምርጫ በአውራ ፓርቲ መተካቱ፣ የሲቪክና ሙያ ማህበራት ከተፅእኖ ነፃ መሆን አለመቻል... ከበርካታ ማሳያዎቹ ጥቂቶቹ ናቸው (በነገራችን ላይ አገዛዙ ድሮውንም በአንደበቱ እንጂ በልቡ ግራ ዘመም በመሆኑ እነዚህ ተቋማት 'አስፈላጊ ናቸው' ብሎ ሊያምን የሚችልበት ምክንያት አይኖረውም፤ ምዕራባውያንን ሲሸነገል ካልሆነ በቀር ማለቴ ነው፤ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ደግሞ ሀሳዊ- መሲሂነቱ በመጋለጡ ለእንዲህ አይነት ጉዳዮች ብዙም ሲጨነቅ አይታይም)

 

፯. የመለስ ህልፈት

መቼም የመለስ ዜናዊ ህልፈት ለኢህአዴግ፣ አቦይ ስብሃት ነጋ እንዳሉት "በቀለ መጣ፣ በቀለ ሄደ፤ ፋጡማ መጣች ፋጡማ ሄደች፤... አይነት ፖለቲካ ነው" ብሎ የሚያምን የዋህ የሚኖር አይመስለኝም፤ እኛ ኢትዮጵያውያን ብቻ ሳንሆን፣ የፖለቲካ ጉዳዮቻችንን የሚከታተሉ የሌላ ሀገር ዜጎች በሙሉ መለስ ለድርጅቱ ሁሉም ነገር እንደነበር ጠንቅቀው ያውቃሉ፤ በሥልጣን ላይ ባሳለፋቸው ሃያ አንድ ዓመታትም የውስጥንም ሆነ የውጪን ተቃውሞ እና ጫናን ያለ ኪሳራ እንዴት መፍታት እንዳለበት ተክኖታል፤ ከምዕራቡ ሲኳረፍ ወደ ምስራቅ ምን ይዞ እንደሚሄድ ያውቃል፤ የሰጣቸውን ትዕዛዝ ያለአንዳች ማመንታት የሚቀበሉ እልፍ አዕላፍ ታጣቂዎቹንም የግል ታዛዦቹ ማድረግ ችሎ ነበር፤ ባልተመረጠበት አካባቢም የድምፅ ቆጠራው እንዴት እንደሚስተካከል ጠንቅቀው የተረዱ "ምርጫ አስፈፃሚዎች"ን ከጎኑ ማሰለፉ ተሳክቶለታል፤ ፍትህን እንዴት ማዛባት እንደሚችሉ የገባቸው ስፍር ቁጥር የሌላቸው ዳኞችም አሰልጥኗል፤ ... ግና!

(ምናልባትም ኢትዮጵያን አምላኳ ሲታደጋት) እነዚህን ሁሉ አንድ ላይ አጣምሮ የሚቆጣጠር እርሱን መሳይ ተተኪ አላስቀመጠም፤ ይህ ነው ሶስተኛውን አብዮት (ሕዝባዊ ንቅናቄ) የተሳካ ከሚያደርጉ (መደላድል እንደተፈጠረ ከሚያመላክቱ) ቁልፍ ጉዳዮች አንዱ። የፓርቲው ቀሳውስትና ዲያቆናትም 'የምፅአት ቀኑን በአርማጌዶ ዘመቻ ለመቀልበስ ማን ይመራናል?' የሚለው ጥያቄ ዕብሪት ያደነደነውን መንፈሳቸውን አልፈስፍሶታል።

በጥቅሉ ከላይ የተጠቀሱት ሰባቱ የሥርዓቱ "የማዕዘን ድንጋይ" በነበሩበት አለመገኘት ወይም የማጭበርበሪያ አጀንዳ መሆናቸው ተጋልጠው ከአገልግሎት ውጪ መሆን የለውጡን አብዮት የህዝብን ፍላጎት በመጨፍለቅ ሊገድብ የሚችል ኃይል እንዳይኖር ያደረገው ይመስለኛል። አገዘዙ እንደለመደው ዛሬም 'አርሶ አደሩ መረጠኝ'፣ 'ብሔር ብሔረሰቦች አከበሩኝ' 'የሃይማኖት ነፃነትን አስከብሪያለሁ'፣ 'ሀገሪቱን በልማት ባቡር አከነፍኳት' ... የመሳሰሉት ለተጭበረበረ ምርጫ መከራከሪያ ሆነው የሚቀርቡት 'ካርዶች' ተበልተውበታል።

 

የነፃነቱ ደውል

ከዚህ በኋላ በኢትዮጵያ ጠረቤዛ ላይ የተቀመጠው አማራጭ አንድ ብቻ ነው፤ በጥቂት ወራት አሊያም በአንድና ሁለት ዓመት ውስጥ ውጤቱን አስቀድሞ ማወቅ ከማይቻልበት ህዝባዊ ንቅናቄ የሚፈጥረው አብዮት ጋር መፋጠጥ ወይም ህዝብንና ህግን በማክበር የ2007ቱን ምርጫ ተዓማኒና ተቀባይነት ባለው መንገድ አካሄዶ ከታሪክ ጋር ማበር። በእኔ እምነት ሁለተኛው መንገድ በምንም መልኩ ከየትኛውም አማራጭ ጋር ሊነፃፀር አይችልም። ሀገሪቱን ማረጋጋት የሚችለውም ሆነ በእውነተኛው የለውጥ ባቡር የሚያሳፍረው ይህ ነው።

እርግጥ ነው እንዲህ አይነት ጉዳዮችን ደፍሮ በአደባባይ መነጋገሩ ከሥርዓቱ በኩል እንደተለመደው 'አመፅ ናፋቂ' ወደሚል ጠርዝ ያስገፋል፣ አገዛዙን አግዝፈው በሚያዩት ደግሞ ከምኞት የሰረፀ ባዶ-ተስፋ መምሰሉ አይቀሬ ነው፤ ይሁንና ኢህአዴግ እንደማንኛውም የፖለቲካ ድርጅት ከታሪክ ዑደት ውጭ ሊሆን የሚችልበት ተዓምር አለመኖሩን ወይም 'የምመጣበት ቀን አይታወቅምና ተዘጋጅታችሁ ጠብቁኝ' እንደሚለው የመፅሀፉ ትእዛዝ አይነት ድንገቴ በሚፈጠሩ ኩነቶች መፃኢ ዕድሉ የሚወሰን አይደለም ብሎ መከራከሩ ብዙ አያስኬድም፤ ምክንያቱም እንደ መንግሥት ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ በሥልጣን ላይ ስለቆየ ኃይል ነውና የምናወራው። የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር በአንድ ወቅት በምክር ቤት ውስጥ "መንግሥት ማየት የተሳነው አይደለም ያያል፤ መስማት የተሳነው አይደለም ይሰማል" ሲል እንደተናገረው ሁሉ መንግሥትም በግልባጩ ከስሩ ባደረ ህዝብ ይመዘናል፣ ይፈተናል፣ ውጤቱም በሰራው ልክ ይሆናል። ዘመኑን የኢህአዴግ የመጨረሻ ወቅቶች እንድለው የሚያስገድደኝ ከዚህ ግምገማ የተነሳ ነው።

የሆነ ሆኖ የዲሞክራሲን መሰረት የሚጥለው የአብዮት ምዕራፍ መከፈቻው ዕለት በጣም ተቃርቧል፤ የነፃነቱ ደውልም በጥሪው የተኙትን ሊያነቃ ከደጅ ደርሷል፤ በሀገሬ ተራሮችና ኮረብቶች የነፃነት ጅረት ያለ ከልካይ የሚፈስበት ያች የተቀደሰች ዕለት ደርሳለች፤ በርግጥም በሁሉም የሀገረ ጥቅም እና በሁሉም ዜጋ መብት በደል የፈፀመው የጉልበት አገዛዝን ከመሰረቱ ፈነቃቅለው ፍትህ የሚሰበክባቸው፣ ዲሞክራሲ የሚሰፍንባቸው፣ ሰብዓዊ መብት የሚከበርባቸው የሙክራቦቻችንን ቅፅር የሚገነባው የለውጥ ንፋስ፣ ከፍታቸው ሰማይ ጥግ ከሚደርሱት ተራሮቻችን፣ ቁልቁል ሊንደርደር ሲያኮቦኩብ ይታየኛል።

(ከለውጡ በኋላስ? የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ፣ ሊከሰት የሚችለውን 'ፖለቲካል ፓራዳየም' እና ራሳቸውን 'አማራጭ ኃይል' ያደረጉ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ተስፋ ሊጣልባቸው ይችላሉ? ወይስ ከዚህም ወደ ከፋ መከራ የሚያደርሱን 'የዳቢሎስ ፈረስ' ናቸው? የሚሉትን ጥያቄዎች ከፓርቲዎቹ ስንስክሳር ጭምር መፈተሹን ሳምንት እመለስበታለሁ፤ አንዳንድ ተቃዋሚ ፓርቲዎች እንደሚያስቡት ዓላማችን ኢህአዴግን ሽረን፣ እንርሱን ማንገስ እንዳለሆነ ይረዱ ዘንድ መምከሩ አስፈላጊ ነው፤ ይህ መፈንቅለ መንግሥት እንጂ አብዮት ሊሆን አይችልምና)

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ