ኬሪያ ኢብራሒም እጅ በመስጠት የመጀመሪያ ኾኑ
የእስር ማዘዣ ከወጣባቸው 46 የሕወሓት ከፍተኛ ባለሥልጣናት አንዷ ነበሩ
ኢዛ (ማክሰኞ ኅዳር ፳፪ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም. December 1, 2020)፦ የሕወሓት ጁንታ ቡድን አባልና በሕግ ሲፈለጉ የነበሩት የቀድሞ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ወይዘሮ ኬሪያ ኢብራሒም እጅ በመስጠት የመጀመሪያዋ ኾኑ።
ወ/ሮ ኬሪያ ኢብራሒም የፌዴሬሽን ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባዔ ኃላፊነታቸውን የለቀቁት ለሥራ ብለው ወደ መቀሌ ከተጓዙ በኋላ ሰኔ 1 ቀን 2012 ዓ.ም. ነበር።
አዲስ አበባ እያሉ መደበኛ ሥራዎችን በመሥራት ላይ መኾናቸውን እያሳወቁ፤ መቀሌ ከደረሱ በኋላ ኃላፊነታቸውን መልቀቃቸውን ያስታወቁት ለድምፂ ወያኔ በሰጡት ቃለ ምልልስ ነበር።
በቴሌቭዥን የሥራ መልቀቂያቸውን በድምፂ ወያኔ በኩል በድምፃቸው የላኩት ወይዘሮ ኬሪያ፤ ከኃላፊነታቸው ለመልቀቅ በወቅቱ የሰጡት አንዱ ምክንያት፤ “ስድስተኛውን አገራዊ ምርጫ በተመለከተ የተሰጠው ሕገ መንግሥታዊ ትርጓሜ ትክክል ባለመኾኑ ነው” የሚል ነበር። ከዚህም ሌላ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ የሚመሩትን መንግሥት፤ “አምባገነናዊ መንግሥት ወደ መመሥረት ደርሰናል” በማለት ጭምር ከመቀሌ ገልጸው ነበር።
እርሳቸው ይመሩት የነበረውን የፌዴሬሽን ምክር ቤት፤ አሁን ባለው አምባገነናዊ አካሔድ ራሱን በራሱ እንዲያጠፋ የሚያደርግ ውሳኔ እያደረገ ነው በማለት መውቀሳቸውም አይዘነጋም። ወይዘሮ ኬሪያ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ከመኾናቸው ቀደም ብሎ በተለይ በትግራይ ክልል በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች ላይ የሠሩ መኾኑ ይታወቃል።
ወይዘሮዋ ከአዲስ አበባ ኃላፊነታቸውን ለቀው የጁንታውን ቡድን በመቀላቀል አብረው ሲሠሩ የቆዩ ሲሆን፤ ከሕወሓት ዘጠኝ የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት አንዷ በመኾን በሕወሓት ቡድን ውስጥ ወሳኝ ኃላፊነት ነበራቸው። መንግሥት የእስር ማዘዣ ካወጣባቸው 46 ከፍተኛ የሕወሓት አመራሮች መካከል አንዷ ናቸው። (ኢዛ)