ኢትዮጵያ በ12 ዓመት ለነዳጅ ግዥ ከግማሽ ትሪሊዮን ብር በላይ ወጪ አድርጋለች
የአገሪቱ የነዳጅ ግዥ ወጪ በየዓመቱ እየጨመረ መጥቷል
አገሪቱ ከምታገኘው የውጭ ምንዛሪ ገቢ ላይ ግማሹ ለነዳጅ ግዥ ይውላል
ኢዛ (እሁድ የካቲት ፯ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም. February 14, 2021)፦ የኢትዮጵያ መንግሥት ከፍተኛ ወጪ ከሚያወጣባቸው ምርቶች መካከል አንዱ ለኾነው ለነዳጅ ግዥ ባለፉት 12 ዓመታት ከግማሽ ትሪሊዮን ብር በላይ ብር ወጪ አውጥቷል።
የአገሪቱን የነዳጅ ግዥ የተመለከተው የኢትዮጵያ ነዳጅ ድርጅት መረጃ እንደሚያመለክተው፤ የአገሪቱ የነዳጅ ግዥ ወጪ በየዓመቱ እየጨመረ በመምጣት በ2012 በጀት ዓመት 62 ቢሊዮን ብር ደርሷል። የአሥር ዓመቱ የነዳጅ ግዥ ወጪ እንደሚያሳየው ከፍተኛ የኾነ ለነዳጅ ግዥ የወጣበት ግን 2011 ዓ.ም. ነው። በ2011 ለነዳጅ ግዥ 69.9 ቢሊዮን ብር ወጪ ተደርጓል።
ይህ የአገሪቱ የነዳጅ ግዥ ወጪ በየዓመቱ እየጨመረ የመጣ ከመኾኑም በላይ፤ በየዓመቱ ወደ ውጭ ተልኮ ከሚገኘው የውጭ ምንዛሪ ገቢ ላይ ከግማሽ በላይ የሚኾነው ለዚሁ የነዳጅ ግዥ ለማዋል አስገድዷል።
የተከታታይ የነዳጅ ግዥ መረጃዎች እንደሚጠቁመው ከአሥር ዓመት በፊት አገሪቷ በዓመት ታወጣ የነበረው ወጪ ከ20 ቢሊዮን ብር ያነሰ ነው። ለአብነት ያህልም በ2000 ዓ.ም. የነዳጅ ግዥ ወጪው 19.1 ቢሊዮን ብር ነበር። (ኢዛ)



