ICG የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝን ተቀበለ
የቀድሞው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በኒውዮርክ የቦርድ ስብሰባ ላይ
አቶ ኃይለማርያም የዓለም አቀፉ የግጭት ተቋም የባለአደራዎች ቦርድ አባል ኾነዋል
ኢዛ (ዓርብ ታኅሣሥ ፲ ቀን ፳፻፲፪ ዓ.ም. December 20, 2019)፦ የቀድሞው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ International Crisis Group በመባል በሚታወቀው ዓለም አቀፍ አጥኚ ተቋም ውስጥ የባለአደራዎች ቦርድ አባል ኾነው መሰየማቸው ተገለጸ።
የግጭት ምክንያቶችንና መከላከያዎችን የሚያጠናና መፍትሔዎችን የሚጠቁመው አጥኚ ተቋም ይፋ እንዳደረገው፤ የቀድሞ የአውሮፓ ሕብረት ኮሚሽን ምክትል ፕሬዝዳንትና የሕብረቱ የውጭ ግንኙነት ኃላፊ የነበሩት ፌደሪካ ሞግሔሪኒ በተመሳሳይ የተቋሙ የቦርዱ አባል ሆነው ተሾመዋል።
አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝና ፌደሪካ ለዚህ ሹመት የበቁት ከዚህ ቀደም በነበራቸው ሰፊ የፖለቲካ ልምድ ተመዝነው ነው። ሁለቱ ፖለቲከኞች የዓለም አቀፉን ተቋም መርኅ፣ ሥራና አሠራርን የሚወስነው ከፍተኛ አካል አባላት በመኾን ይሠራሉ።
አቶ ኃይለማርያም ከጠቅላይ ሚኒስትርነት ኃላፊነታቸው በፍቃዳቸው መልቀቃቸውን አሳውቀው፤ በዶ/ር ዐቢይ አሕመድ ከተተኩ በኋላ ከተለያዩ የዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር ሲሠሩ ቆይተዋል።
ባለፈው ዓመት በዙምባብዌ የተደረገውን አገር አቀፍ ምርጫ በአፍሪካ ሕብረት ተመርጠው የአፍሪካ ሕብረት ምርጫ ታዛቢ ቡድን መሪ በመኾን መሥራታቸው ይታወሳል። (ኢዛ)



