የደመራ በዓል ለሁለተኛ ጊዜ በስዊድን ተከበረ
Ethiopia Zare (ዓርብ መስከረም ፲፮ (16) ቀን ፳፻፩ (2001) ዓ.ም. September 26, 2008)፦ በስዊድን ዋና ከተማ ስቶክሆልም ደብረሠላም መድኃኒዓለም ቤተክርስቲያን የደመራ በዓል በደማቅ ሁኔታ አከበረች። ሥነሥርዓቱ አመሻሹ 11፡00 ሰዓት (17፡00) ላይ ተጀምሮ እስከ ምሽቱ 2፡00 ሰዓት (20፡00) የዘለቀ ሲሆን፣ በስቶክሆልምና አካባቢው የሚኖሩ ምዕመናን ተገኝተዋል።
በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ኤልያስ ቡራኬ የተከፈተው የደመራው ሥነሥርዓት የካህናቱ እና የዲያቆናቱ ያሬዳዊ ዝማሬ ከፍተኛ ድምቀት ሰጥቶት አምሽቷል።
የደመራውን እሳት ከመለኮሳቸው በፊት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ኤልያስ የደመራን በዓል አመጣጥ፤ እውነተኛው ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት መስቀል ወደ ሀገራችን እንዴት እና መቼ እንደገባ እና የት እንደሚገኝም ታሪካዊ ትምህርት ለምዕመናኑ አስተምረዋል።
በመቀጠልም ስደተኛው የኢትዮጵያ ህዝብ ልባም ስደተኛ በመሆኑ ከስደት ሕይወቱ መንፈሣዊና ቁሳዊ ሀብቶቹን ማትረፍ እንደሚችል በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ለረዥም ዘመናት የተሰደዱ ህዝቦችን ምሳሌ በማድረግ ሰፋ ያለ ትምህርት ሰጥተዋል።
በሰንበት ትምህርት ቤቱ እና በሕፃናት የቀረቡት ዘማሪዎች ለበዓሉ ተጨማሪ ድምቀት ሰጥተውታል።
በስቶክሆልም የምትገኘው ደብረሠላም መድኃኒዓለም ቤተክርስቲያን የደመራን በዓል ማክበር የጀመረችው ባለፈው ዓመት ፳፻ ዓ.ም. ሲሆን፣ ይህ ለሁለተኛ ጊዜ መከበሩ ነው።