የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሦስት አንቀጾች ትርጓሜ እንዲሰጣቸው ወሰነ
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ማክሰኞ ሚያዝያ 27 ቀን 2012 ዓ.ም. በምርጫ ጉዳይ ላይ የሕግ፣ የፍትሕና የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ መርምሮ ባቀረበው የውሳኔ ሐሳብ ላይ ተወያይቶ አጸደቀ
የፌዴሬሽን ምክር ቤት ሕገመንግሥት በአንድ ወር ይተርጉም ተባለ
ኢዛ (ረቡዕ ሚያዝያ ፳፰ ቀን ፳፻፲፪ ዓ.ም. May 6, 2020)፦ በቀጣይ የሚካሔደውን አገራዊ ምርጫ አስመልክቶ የተቀመጡ ሦስት አንቀፆች በሕገመንግሥታዊ ትርጓሜ እንዲሰጣቸው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ትናንት አጸደቀ።
ምክር ቤቱ ትናንት ማክሰኞ ሚያዝያ 27 ቀን 2012 ዓ.ም. ባጸደቀው መሠረት፤ ምክር ቤቱ የፌዴሬሽን ምክር ቤት በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 83 በተሰጠው ሥልጣን መሠረት ምርጫውን መራዘም በተመለከተ ትርጉም የሚያስፈልጋቸውን አንቀጾች በአንድ ወር ውስጥ እንዲተረጉ ውሳኔ አስተላልፏል።
ይህንን ውሳኔ ያሳለፈው የሕግ፣ ፍትሕና ዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምርጫን በተመለከተ የተቀመጡ ሦስት አንቀጾች ላይ የሕገ መንግሥት ትርጓሜ እንዲሰጥ የውሳኔ ካቀረበ በኋላ ነው።
የሕግ፣ ፍትሕና ዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በኮቪድ 19 ወረርሽኝ የተነሳ ስድስተኛው አገራዊ ምርጫ 2012 ለማከናወን አለመቻሉን አስመልክቶ ለምክር ቤቱ ያቀረበው የውሳኔ ሐሳብ በምክር ቤቱ መጽደቁን ተከትሎ፤ ቀጣይ ሕገ መንግሥታዊ የመፍትሔ ሐሳብ እንዲያቀርብ በተመራለት መሠረት ያቀረበውን ሪፖርትና የውሳኔ ሐሳብ መርምሮ ያጽደቀውም በአብላጫ ድምፅ ነው። በዕለቱ 25 የፓርላማ አባላት ውሳኔውን የመቃወም ድምፅ ሰጥተዋል። (ኢዛ)



