በደቡብ ስድስት የልዩ ኃይል እና ሦስት የፖሊስ አባላት ተገደሉ
በደቡብ ክልላዊ መንግሥት ቤንች ሸኮ ዞን
ሦስት ቆስለዋል
ኢዛ (ረቡዕ ግንቦት ፲፩ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም. May 19, 2021)፦ በደቡብ ክልላዊ መንግሥት ቤንች ሸኮ ዞን ውስጥ በጸጥታ ኃይሎች ላይ በተሰነዘረ ጥቃት ዘጠኝ ሲገደሉ፤ ሦስት መቁሰላቸው ተገለጸ።
ጥቃቱን ያደረሱት እስካሁን ማንነታቸው ያልታወቁ ታጣቂዎች ሲኾኑ፣ ትናንት በፈጸሙት ጥቃት ሕይወታቸው ካለፉ የጸጥታ ኃይሎች መካከል ስድስቱ የልዩ ኃይል አባላት ሲኾኑ፤ ሦስቱ ደግሞ የፖሊስ አባላት ናቸው ተብሏል።
የዞኑ የሰላምና ጸጥታ ጽሕፈት እንዳስታወቀው፤ የጥቃቱ አድራሾችን በአካባቢ የሚንቀሳቀሱ ፀረ ሰላም ኃይሎች ያላቸው ሲሆን፤ ጥቃቱን የፈጸሙትም የጸጥታ ኃይሉ አባላት ከግዳጅ ሲመለሱ መንገድ ተዘግቶባቸውና ተሽከርካሪያቸውን አስቁመው በከፈቱት ተኩስ ነው። (ኢዛ)



