ለእርዳታ ወደ ትግራይ በረራ ተፈቀደ
መደበኛ የመንገደኞች በረራዎች እንደተቋረጡ ነው
ኢዛ (ረቡዕ ሰኔ ፴ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም. July 7, 2021)፦ በትግራይ ክልል የሰብአዊ ድጋፍ ለማድረግ ፍላጎት ያላቸው አካላት ወደ ትግራይ ለሚያደርጉት በረራ ፍቃድ መሰጠቱን የኢትዮጵያ መንግሥት አስታወቀ።
የበረራ ፈቃዱን በተመለከተ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የመረጃ ማጣሪያ ዛሬ ረቡዕ ሰኔ 30 ቀን 2013 ዓ.ም. እንዳስታወቀው፤ ለሰብአዊ ድጋፍ ወደ ትግራይ የሚደረገው በረራ የተፈቀደው ከሰኞ ሰኔ 28 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ ነው።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ወደ ትግራይ የሚደረጉ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በረራዎች እንደተቋረጡ ይታወቃል። ወደ ትግራይ የተለያዩ ከተሞች የሚደረጉ በረራዎች በኢትዮጵያ ውስጥ በቁጥር በርካታ በረራዎች የሚደረግበት እንደነበረ ይታወቃል።
አየር መንገዱ በረራውን ያቋረጠው ከጸጥታ ችግር አንጻር እንደኾነም ታውቋል። (ኢዛ)