በያዝነው ዓመት 12 የጐሣ ግጭት መከሰቱን ፖሊስ አመነ
Ethiopia Zare (ዓርብ ሰኔ 5 ቀን 2001 ዓ.ም. June 12, 2009)፦ ሀገሪቱን ብሔር ብሔረሰቦች ሸንሽኖ በሚገዛው በኢህአዴግ መንግሥት አስተዳደር ውስጥ በ10 ወራት ብቻ 12 ብሔር ብሔረሰቦችና የጐሳ ግጭቶች በኢትዮጵያ ተከስቶ እንደነበር የፌዴራል ፖሊስ ዋና ዳይሬክተር አቶ ወርቅነህ ገበየሁ አሳወቁ።
ዳይሬክተሩ ባለፈው ሳምንት ሐሙስ ለፓርላማ ቋሚ ኮሚቴ የ10 ወር የሥራ ውጤታቸውን ሲገልጹ ግጭቶችን ማስወገድ የክልሎች አቅም ሲዳከም ከየክልሉ በሚቀረብ ጥያቄ መሠረት የፌዴራል ፖሊስ አባሎች ወደ ግጭት ቦታዎች በመሄድ ግጭቶችን ሳይባባሱ ማስቆማቸውን ቢገልጹም በዘገባዎች ብቻ ዜጎች በጎሳ ግጭት ምክንያት በመቶዎች የሚቆጠሩ መሞታቸውና መቁሰላቸው መገለጹ አይዘነጋም።
አንድ የምክር ቤት አባል “በርካታ፣ የፌዴራል ፖሊስ አባላት ሥራ እየለቀቁ ነው በምን ምክንያት ነው?” በሚል ላቀረቡት ጥያቄ ዳይሬክተሩ ሲመልሱ “በዲስፕሊን ችግር የሚባረሩና የሥራ ባልደረባ አስቀየመን ብለው ሥራ የሚለቁ መኖራቸውን እንዲሁም ለፌዴራል ፖሊሶች መቀነስ ዋናው ምክንያት ግን አብዛኞቹ የፌዴራል ፖሊስ አባሎች ክልል ወደሚገኙ ቤተሰቦቻቸው ለመሄድ መፈለጋቸው ነው” በማለት ተናግረዋል።
ዳይሬክተሩ ይህን ይበሉ እንጂ የፌዴራል ፖሊሶች ካለባቸው የኑሮ ችግር የተነሳ ሥራ በመልቀቅ አንዳንዶቹ በተለያዩ የወንጀል ድርጊቶች ተሰማርተው እንደሚገኙና ያለውን የስልጣን ተዋረድ በመቃወም ስራቸውን ለመልቀቅ እንደሚገደዱ ለማዎቅ ተችሏል።
አቦይ ስብሃት ከቪኦኤ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ብሄር ብሄረሰቦችን አቀራርበናል ሲሉ የተደመጡ ሲሆን ይህ በፓርላማ የቀረበው የ10 ወር የፖሊስ ኮሚሽነሩ ሪፖርት 12 ግጭቶች በጎሳ ምክንያት የተከሰቱ ግጭቶች መኖራቸውን አምኗል።


