ዘፍናችሁ ቅበሩኝ

ዳግማዊ ዳዊት መስከረም 2002 ዓ.ም. This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.

ሰውን ሰው አሳዶ - ቢያሳጣው መድረሻ

ጭንቅ ብርክ አስይዞ - ፍፁም መተንፈሻ

 

ሚሊዮኖች ቢያልቁ - በረሃብ በበሽታ

ጦርነት ቢመረጥ - በሠላሙ ፋንታ

 

መስማማት ተጠልቶ - መናቆር ቢሞገስ

ቅደሱ ቢረክስ - ርኩሱም ቢቀደስ

ሕግ የጉልበት ሆኖ - ፍትህም ተጠልፎ

አስታራቂ ጠፍቶ - ዳኝነት ተገፍፎ

መስገብገብ ሕግ ሆኖ - ሙስና ተለምዶ

ቅጥፈት ተሞካሽቶ - እውነትም ተዋርዶ

ቀማኛን ሆነና - የሚሰማ ጆሮ

ቁብ የሚለው ጠፋ - የደሃን እሮሮ

እጥፍ ድርብ ሆነ - ሰቆቃው ጨመረ

ዓይኔን እንባ ሞላው - ልቤ ተሰበረ።

 

አንገቴን ደፍቸ - መሬትን እየጫርኩ

መሞት እንደምሻ - ለአምላኬ እየነገርኩ

ፀሎቴ ተሰምቶ - አርጎ ሰማይ

ሞቴ ደረሰልኝ - ይህን እንዳላይ።

 

ዛሬ መሄጃዬ - ተራዬ ነውና

ከየመንደራችሁ - በጠዋት ውጡና

ሸኙኝ ጨፍራችሁ - በዘፈን በዜማ

ሞትን መርጫለሁ ይህን ከምሰማ።

 

እናቴ አታልቅሽ - አይመታ ደረት

አባቴም አትተክዝ - እኔስ ልሂድበት

ትቸው የምሄደው - የምተወው ዓለም

ከሞት የባሰ እንጅ - የተሻለ አይደለም።

 

ፅድቅና ኩነኔ - ቢኖርም ባይኖርም

ለእኔ እዚህ መኖሬ - ከሞት አይሻልም

እኔስ በፈጠረኝ - እመካለሁና

ሕይወት ይኖረኛል - ገነት እንደገና።

 

አልያም …

ሚካኤል ከበሩ - ባይቀበለኝም

አቡዬን ተክልዬን - ላያቸው ባልችልም

ገነት መግባት ቀርቶ - ገሃነም ብወርድም

ቁርጥ ያጠግባልና - አማረ አላማረም

ከመሞት መኖርን - በፍፁም አልመርጥም

የዚህ ዓለም ኑሮ - የአምሳያዬ ግፉ

ሞትን አስመረጠኝ - ተሽሎኝ ማረፉ።

 

እናም አታልቅሱ - አልሰማ ዋይ ዋይታ

በምትኩ አሳዩኝ - ዘፈንና እስክስታ

ክራር ጽናጽሉ - ከበሮው ይመታ

በገና ይደርደር - አስራ ሁለት ተርታ

ይነፋ ዋሽንቱ - ሳክስፎን እምቢልታ

ወንዶቹ በሆታ - ሴቶቹ በእልልታ

የዛሬን - የዛሬን - እኔን ደስ እንዲለኝ

ማልቀሱን ተዉና - ዘፍናችሁ ቅበሩኝ።


 

ዳግማዊ ዳዊት መስከረም 2002 ዓ.ም. This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ