ጮክ ብለህ ተናገር

ዳግማዊ ዳዊት This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.

ልቤ እስከሚሸበር - መልካው እስኪናጋ

ወፎች ግ … ር እስኪሉ -እስኪበተን መንጋ

ጀግና እስከሚፎክር - ፈሪ እስከሚያመልጠው

ልጆች እስኪሮጡ - መዓት መጣ ብለው

ቄሱ እስከሚያማትብ - እስኪል “በሥላሤ”

ሠባኪው እስከሚል - “በጌታ እየሱሴ”

ሸኹ “ያ - አላህ” ብሎ - አዛን እስኪያሰማ

ሾፌሩ ለመሄድ - ለመቆም ሲያቅማማ

እናት “ውይ!” እስክትል - ደረቷን ስትመታ

ሌባ እስኪበረግግ - እስኪሮጥ በአፍታ

እስከሚያስተጋባ - ሸንተረር ሸሎቆው

ተራራና ወንዙ - ዛፉና ቁጥቋጦው

ጮክ ብለህ ተናገር - እኔም ልበል አሜን

እስካዳነ ድረስ - ሀገሬን ወገኔን

ላይጠራ አይደፈርስ - ሣይጨልም አይነጋ

በለው ተናገረው - መልካው እስኪናጋ።

 

መነኩሴው ሲረሸን - ቤተመቅደስ ገብቶ

ዔሎሄ ሀገሬ - ወገኔ እሚል ጠፍቶ

ሚስት ስትገደል - ሥለባሏ ጮሃ

ወገኔ በሥደት ሲሞት በበረሃ

አዛውንት ሲታሰር - እህት ስትደፈር

ፍትህ ስትዛባ - ኃይማኖት ስትሻር

ዝምታው ምንድን ነው - ተናገር ላዳምጥህ

ወርቅ ነው እሚነጥር - አንጥረው ተናግረህ።

 

የውንድምህ ግጭት - ያኮረፍክበቱ

አያስደነግጥም - ቢታይም ውጤቱ

ሀገር አያጠፋ - አይገድል ወገን “ያዝ … ያዝ” መባባሉ ማውራት ይህንን

ለእኔ ይመስለኛል - ጊዜ ማባከን

እንኳንስ የሰው ልጅ - እኩይ ምላስ ያለው

ድንጋይም ይጋጫል - የማይናገረው።

 

ይልቅ፤

 

ሠላምን ሥትሻ - ፍትህ እና መብት

ፍቅርን በልብ ይዘህ - ስትል ለእኛ መንግሥት

ይህን ስትጠይቅ - በአንተ በፈረደ

አንተ ስትገነባ - እራሱ እየናደ

ያለውን ታገለው - “መለስ” የሚሉትን

ሀገር አፍራሽ ይጥፋ - ቅድሚያ ለእርሱ ይሁን።

ዝምታ ወርቅ ቢሆን - ቢያስከብር በወገን

አክባሪው ሲገደል - ዝምታ ምን ይሆን?

ድሮም ይባል ነበር - ለመሾም በመንበር

ዝምታ አይሆነውም - ከመናገር በቀር

መሾም አይገኝም - ደጃዝማችነቱ

በመናገር ጥረት - የምትገኝቱ።

 

ግና፤

መቋመጥ ለመውጣት - ከሥልጣን ኮርቻ

ላገር ሳይሞቱላት - ልክ እንደነ ባልቻ

እንደነ አባ ታጠቅ - እንደነ አባ ዳኘው

እንደነ አባ በዝብዝ - እንደነ አባ ዳጨው

እንደነ አባ መላ - እንደነ አባ ውቃው

እንደነ አባ ኮስትር - እንደነ አባ ነጋ

እንደ ዘረዓይ ድረስ - እንደነ አብዲሳ አጋ

ካላወጡ ወገን - ከጠላት መንጋጋ

መናገር ቧልት ነው - የመለፍለፍ ዓመል

ሐኪም የሚያሰኘው - ቃልቻ ወይ ፀበል

 

እና፤

 

ጮክ ብለህ ተናገር - እኔም ልበል አሜን

እስካዳነ ድረስ - ሀገሬን ወገኔን

አሳርግ ለፍትህ - ለሠላም ለመብት

ለሀገር ብልፅግና - ለወገን ለአንድነት

ላይጠራ አይደፈርስ - ሣይጨልም አይነጋ

ጮክ ብለህ ተናገር - ዙፋኑ እንዲናጋ።


 

ዳግማዊ ዳዊት This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.

ሐምሌ 2001 ዓ.ም.

 

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ