ላልታወቀ ብፃይ (ተስፋዬ ገብረአብ)
ላልታወቀ ብፃይ
ተስፋዬ ገብረአብ
(ይህችን ሥነግጥም ስማቸውን ሸሽገው የስድብ ደብዳቤ ለፃፉልኝና ለሚጽፉልኝ የወያኔ ብፆት (ጓዶች) ዘልዓለማዊ ሐውልት ትሆን ዘንድ ቋጥሬያታለሁ። የግጥም አፃፃፉ ከሎሬት ፀጋዬ ገብረመድኅን ‘ይድረስ ለማላውቅህ’ በሚለው ዜማ የዘለቀ ነው።)
ጌታው!
እስኪ ልጠይቅህ ከልብ፣
ዘገርህን ለነቀነቅህ ለስድብ፣
እባክህ ብፃይ ማነህ አንተ?
እንዳልነበረ ሰው ከምትከስም፣
ሳይበራልህ ከምትጨልም፣
እንደ ሊማሊሞ ከምትጠማጠም፣
ተናገር አንተነትክን …
ማን ይሆን የልጅነትህ የወተት ስም?
ጌታው ብፃይ!
ማንነትክን በነፃው ሁዳድ ላይ፣
መዘርጋት ያልቻልክ እንደ ጠኃይ፣
(የኔ ስም ይፋ ነው እንደ ሰማይ)
ማነህ ብዬ ካንተ ጋር ልወያይ?
ቀበሪቾ ነህ እምቧጮ?
ዳማከሴ ነህ ወይስ እምቧይ?
ማነህ አንተ ጓድ (ብፃይ?)
ተገላቢጦሹ ነህ ወይስ ተክሉ ተክላይ?
የማን እንበልህ በመላ?
ከደጋው ነህ ከቆላ?
የዋልዋ ነህ የካሱ ይላላ?
የስዩም ወይስ ያባዱላ?
ቃላችሁ እና ግብራችሁ …
ኮብላይ እንደ ሐምሌ ጥላ!
እና ማነህ አንተ ብፃይ?
ደላላ ነህ ወይስ ሃሜት አብሳይ?
በቃጅማው ጊዮርጊስ ይዤሃለሁ፣
ማነህ ብዬ ካንተ ጋር ልወያይ?
ሰድቦ ለሰዳቢ እንደሚሰጥ ብካይ፣
እጆቹ ሥራ እንደፈቱ ወሬ ቀቃይ፣
የገዛ ተስፋውን ሸጦ እንደበላ ደደብ፣
በፍርሃት ስር ተሸሽገህ እምትሳደብ፣
እንደሚያነፈንፍ አሳማ በየፍጉ፣
ከዋው፣ ረዋው፣ ሰዋው ከምትል በየጥጉ፣
እባክህ ዓይንህን ገልጠህ እይ! እንደወጉ፣
ተዋረድ!! ብትዋረድም!
ተሸነፍ!! ብትሸነፍም!
እንደ ኩሩው አያት እንደታሪካችን ፋና፣
በዚያ በምናውቀው ሁዳድ፣ በዚያ ባለፍንበት ጎዳና፣
ምንም ይሁን ምን ብፃይ! እባክህ …
በነፃነት ደረትክን ገልብጠህ ና!!!
ተስፋዬ ገብረአብ
This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.



