የሞት ዕኩልነት (ዳግማዊ ዳዊት)
የሞት ዕኩልነት
ዳግማዊ ዳዊት This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.
እግዜር በፈጠረው - ሰማይና ምድር
ተራራ ሸንተረር - ውቅያኖስ ባህር
ያገባኛል ብሎ - ሰው ባለቤት ሆኖ - ድንበር አበጅቶ
የከርሰ-ምድር ሀብት - በስፋት አካብቶ
አንተ ከዚያ ወዲህ - አንች ከዚህ ወዲያ - ብሎ ተከፋፍሎ
አንዱን እጅግ ደልቶት - ሌላው ተበድሎ
ይኖራል ይሞታል - የመኖር-ሕግ ሆኖ።
አንዱ ባለፀጋ - የተትረፈረፈው
ሌላው ምስኪን ደሃ - ይበላው ይጠጣው
- ይለብሰው የሌለው
የዓለም መልክ ሆነና - ሕይወት ዥንጉርጉሩ
የሰው ልጅ ይኖራል - ገንዘብ ሆኖ ነውሩ
ንብረት በለጠና - ከሰብዓዊ ክብሩ።
ሠራዊት መንግሥታት - አቤት ብለውለት
ሀብታሙ ይኖራል - ዓለም አድልታለት
ከውሻ አንሶ ደሃው - ማጣቱ ወንጅሎት
እሱም ኖረ ተብሏል - ዓለም አድማበት
የሰው ልጅ ኅሊና - እንዲህ ተመሳቅሎ
ፀጋን አመሥግኖ
ድህነት ኮንኖ
ለኃይል አቤት ብሎ
ደካማውን ገድሎ
ሕይወት ነው ይለናል - “መኖር” ስሙ ሆኖ።
ልክ እንደ እግዜር ሆኖ - ሰው ቢሠራውማ - ሰማይና ምድሩ
ደሃና ደካማ ባልኖሩበት ነበር - ገና ከጅምሩ
ጉልበታም ለብቻው - ልክ እንደሂትለር
ሞልቶ ከተረፈው - ከባለፀጋው ጋር
እኛ ብቻ እንኑር - ብሎ ባለን ነበር
ዳሩ አምላክ ሆነና - የዚህ ዓለም ንጉሥ
ደሃውም ሀብታሙም - ደካማና ኃይለኛ እኩል ባይወደስ
የሞት ቀን ሲመጣ - ሰው ሲመለስ ከአፈር
ዕኩል መሆናቸው - ያኔ ነው የማይቀር።
እናም ሂሳብ ሳስብ - አንድና አንድ ደምሬ
ዕልፍ አዕላፍ ብደርስ - ከአሃዱ ጀምሬ
አራት ነጥብ ሳደርግ - ስንኝ ቋጥሬ
መደምደሚያው ሆነ - የድምር ውጤቱ
ዕኩል የሚሆነው - ሰው በሰውነቱ
ሲሞት ብቻ ሆኖ - አፈርኩ በስሌቱ
በአንድዬ እምላለሁ - ቀፈፈኝ እውነቱ።
ዳግማዊ ዳዊት
This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.
ሰኔ 2002 ዓ.ም.



