ዓድዋ - 124ኛ ዓመት

124ኛው የዓድዋ ድል በዓል በዓድዋ ከተማ
በተለየ ድምቀት የተከበረው የድል በዓል
ኢዛ (ሰኞ የካቲት ፳፫ ቀን ፳፻፲፪ ዓ.ም. March 2, 2020)፦ የዓድዋ ድል በዓል መከበር ከጀመረበት ጊዜ ወዲህ በድምቀት ከተከበሩባቸው ዓመታት ሁሉ በዛሬው ዕለት የተከበረው 124ኛው የዓድዋ ድል በዓል ደምቆ የታየበት ሲሆን፤ ወቅታዊ መልእክቶችም የተላለፉበት ነበር።
የዘንድሮው በዓል በተለይ በአዲስ አበባ በአፄ ምኒልክ አደባባይና ኢትዮጵያውያኖች ጣልያንን ድል ባደረጉበት ዓድዋ ከተማ ተከብሯል።

በተለይ በአዲስ አበባ ከዚህ ቀደም በዓድዋ በዓል ላይ ይታደም ከነበረው የከተማው ነዋሪ በእጅጉ የላቀ ሕዝብ በዛሬው በዓል ላይ የተገኘበት ነው። በዓሉን የሚያጸባርቁ አልባሳትና የዓድዋ ድል ፊትአውራሪ የኾኑትን የአፄ ምኒልክና የእቴጌ ጣይቱን ምስል ያሉባቸውን ቲሸርቶች በመልበስ ጭምር በዓሉ በድምቀት ተከብሯል። በተመሳሳይ በዓድዋ ከተማ በዓል ላይ ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ የተገኙበት ነበር።

በዓሉን አስመልክተው ባደረጉት ንግግር፤ የዓድዋ የድል በዓል ቅኝ ግዛትን ማሸነፍ እንደሚቻል ያበሰረና የነፃነት ጮራ እንዲፈነጥቅ ያደረገ መኾኑን ገልጸው፤ በዓድዋ ድል በዓል ከማንኛውም የውስጥ ችግር በላይ ለኢትዮጵያ ነፃነት ትኩረት በመሥጠት ነፃ አገር ማቆየት መቻሉንም የጠቀሱበት ነበር።
በዓድዋ በዓል ላይ የተገኙት የትግራይ ክልል ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር ደብረጽዮን ገ/ሚካኤል ደግሞ፤ በዓሉን አስታከው ሰሞናዊውን የህዳሴ ግድብና እየተደረገ ያለውን ድርድር በተመለከተ ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል የሚል መልእክት አስተላልፈዋል።
በኢትዮጵያ የግብጹ አምባሳደር፤ ዓድዋ የኢትዮጵያም የአፍሪካም ድል መኾኑን የሚያመለክት መልእክት በትዊተር ገጻቸው ላይ አስፍረዋል።

ፈረሰኞች በዓሉን ያደመቁበት ሲሆን፤ ከበዓሉ አከባበር ጋር ተያይዞ በዓሉን ለማክበር ከወጡ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ከዓባይና ከህዳሴ ግድብ ጋር በተያያዘ ከሰሞኑ የተፈጠረውን ለማስታወስ አሜሪካ ከኢትዮጵያ ላይ እጇን ታንሳ የሚል መልእክት የያዙ መፈክሮችን ይዘው ታይተዋል። በብሔራዊ ጉዳያችን አንደራደርም የሚልና ተመሳሳይ መልእክቶች በበዓሉ ላይ የተንጸባረቁ ሲሆን፣ ከበዓሉ በኋላ በሕብረት በመኾን ወጣቶች ሲያዜሙ ከነበረው ውስጥ ይህንኑ የዓባይ ጉዳይ የተመለከተ ነበር።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ዛሬ በፌስቡክ ገጻቸው በአጭሩ፤ “የዓድዋ ድል ብሔራዊ ድል ብቻ አይደለም። የአፍሪካ ነፃነት መልሶ የወለደ ድል ነው። ይህ በብርቱ ትግል የተገኘ ነፃነት፣ የአፍሪካን መጻኢ እድል እንዴት በሕብረት አዎንታዊ ማድረግ እንደምንችል ያሳያል” ብለዋል። (ኢዛ)


