ከ1,700 በላይ የኦሮሚያ የመንግሥት ኃላፊዎችና ሠራተኞች ላይ እርምጃ ተወሰደ
የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት
ኃላፊነታቸውን ባለመወጣትና በብጥብጡ ውስጥ በመሳተፍ የተጠረጠሩ ናቸው
ኢዛ (ማክሰኞ ነኀሴ ፭ ቀን ፳፻፲፪ ዓ.ም. August 11, 2020)፦ ከአርቲስት ሐጫሉ ሁንዴሳ ግድያ ጋር ተያይዞ በተከሰተው ኹከት ተሳትፎ ነበራቸው ተብለው የተጠረጠሩ ከ1,700 በላይ የመንግሥት ኃላፊዎችና ሠራተኞች ላይ እርምጃ መወሰዱን የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት አስታወቀ።
ክልሉ ዛሬ ማክሰኞ ነኀሴ 5 ቀን 2012 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ ከድርጊቱ ጋር በተያያዘ ተሳትፎ በማድረግና ኃላፊነታቸውን በአግባቡ ባለመወጣት ተጠናክረው እርምጃ ከተወሰደባቸው ውስጥ 1,200 የሚኾኑት የመንግሥት ኃላፊዎች ናቸው። ከ500 በላይ የሚኾኑት የመንግሥት ሠራተኞች ደግሞ ኃላፊነታቸውን ባለመወጣትና በብጥብጡ ውስጥ በመሳተፍ ተጠርጥረው ጉዳያቸው እየተጣራ ነው።
በክልሉ የኮምዩኒኬሽን ቢሮ በኩል በወጣው የዛሬው መግለጫ፤ በብጥብጡ ተጠርጥረው ሕጋዊ እና ፖለቲካዊ እርምጃ ተወስዶባቸዋል የተባሉት በቀበሌ፣ በወረዳና በዞን ደረጃ በመንግሥት ኃላፊነት ላይ የነበሩ ናቸው። ቀጣይ እርምጃዎች እንደሚወሰዱም በሰሞኑ የኦሮሚያ ቅርንጫፍ ብልጽግና ፓርቲ ስብሰባ ላይ አቅጣጫ መሰጠቱን መግለጫው አመልክቷል። (ኢዛ)



