ዶክተር ዐቢይ የሽግግር መንግሥት ይቋቋም የሚለውን ጥያቄ ውድቅ አደረጉ
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ከተፎካካሪ ፓርቲዎችና ሲቪክ ማኅበራት መሪዎች ጋር በምርጫና ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ውይይት ሲያደርጉ
ጥያቄውን የሽግግር ሳይሆን የብጥብጥብ ብለውታል
ኢዛ (ዓርብ ሚያዝያ ፳፫ ቀን ፳፻፲፪ ዓ.ም. May 1, 2020)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ “የሽግግር መንግሥት ይቋቋም” በሚል የሚቀርቡ ጥያቄዎችን፤ “የብጥብጥ መንግሥት ይቋቋም” እንደማለት እንደሚቆጥሩት ገልጸዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህንን የገለጹት ከትናንት በስቲያ (ረቡዕ ሚያዝያ 21 ቀን 2012 ዓ.ም.) በምርጫ 2012 እና በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር ባደረጉት የውይይት መድረክ ላይ ነው።
በዚህ ምክክር ላይ ቀጣዩን ምርጫ ለማድረግ አራት የመፍትሔ ሐሳቦች ቀርበው ማብራሪያ ተሰጥቶባቸው ውይይት የተደረገበት ቢሆንም፤ “የሽግግር መንግሥት ይቋቋም” በሚለው ጥያቄ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ “የሽግግር መንግሥት ይቋቋም ማለት የሽግግር ሳይሆን የብጥብጥ መንግሥት ነው የምለው” በማለት በዚህ ጥያቄ ዙሪያ ያላቸውን አቋም አንጸባርቀዋል።
ለዚህም የተለያዩ ምሳሌዎችን ያስቀመጡ ሲሆን፤ በተለይ ግን ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር እንኳን በጋራ መንግሥት ለመኾን ይቅርና፤ ተፎካካሪ ፓርቲዎች በጋራ ምክር ቤት ተወያይቶ አጀንዳ መወሰን ያልቻለ ስብስብ፤ በዚህ ክሪቲካል ጊዜ እንደዚህ ዐይነት ቀልድ መቀለድ አስፈላጊ ያለመኾኑን ገልጸዋል። ይህንን ለማድረግ ምርጫውን በሚያስችሉን ላይ ተወያይተን የምንወስንበት መንገድ መፈለግ ይበጃል ብለዋል። (ኢዛ)



