የኢዜማ የአንድ የምርጫ ወረዳ ሊቀመንበሩ ተገደሉ
በተተኮሰባቸው ጥይት ሕይወታቸው ማለፉን ፓርቲው አስታውቋል
ኢዛ (ሰኞ የካቲት ፰ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም. February 15, 2021)፦ በቀጣዩ አገራዊ ምርጫ (ምርጫ 2013) በዋናነት ተፎካካሪ እንደሚኾኑ ከሚጠበቁት ተፎካካሪ ፓርቲዎች መካከል አንዱ የኾነው የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) በደብረዘይት (ቢሾፍቱ) ከተማ የአድአ ምርጫ ወረዳ 1 ሊቀመንበሩ እንደተገደለበት አስታወቀ።
ፓርቲው እንዳስታወቀው ሊቀመንበሩ አቶ ግርማ ሞገስ ለገሰ ትላንት እሁድ የካቲት 7 ቀን 2013 ዓ.ም. ምሽት በተተኮሰባቸው ጥይት ሕይወታቸው ማለፉን እና የኢዜማ አባላት እና አመራሮች ይህን ዜና ስንሰማ ከፍተኛ ኀዘን ይሰማናል በማለት አስታውቋል።
ኢዜማ በአባሉ ላይ የተፈጸመውን የግድያ ወንጀል በጽኑ የሚያወግዝ ስለመኾኑ በዚሁ መግለጫው አስታውቆ፤ ተጨማሪ መረጃዎችን ሰብስቦ እንደጨረሰ ዝርዝር ጋዜጣዊ መግለጫ የሚሰጥበት መኾኑንም አስታውቋል። (ኢዛ)