በሕገወጥ መንገድ የተከማቸው ሁለት ሚሊዮን ጄሪካን ዘይት ለሸማቾች እየተሰራጨ ነው
ሸሽጎ ያስቀመጠው ማን እንደኾነ እስካኹን አልተገለጸም
ኢዛ (ሰኞ የካቲት ፰ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም. February 15, 2021)፦ በአዲስ አበባ በአንድ ግለሰብ መጋዘን ውስጥ በሕገወጥ መንገድ ተከማችቶ የተገኘው ሁለት ሚሊዮን ጄሪካን ፓልም የምግብ ዘይት፤ ሸሽጎ ያስቀመጠው ማን እንደኾነ ሳይታወቅ ለሸማች ማኅበራት እየተሰራጨ መኾኑ ተገጸለ።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እንዳስታወቀው፤ በቁጥጥር ሥር የዋለው ፓልም የምግብ ዘይት በሁሉም ክፍለ ከተሞች በሚገኙ የሸማች ማኅበራት በኩል ለሕብረተሰቡ ተደራሽ እንዲኾን የከተማ አስተዳደሩ በወሰነው መሠረት በዛሬው ዕለት የማሰራጨት ሥራው ተጀምሯል ተብላል።
በሕገ ወጥ መንገድ ተከማችቶ የተያዘው ዘይት ለሸማች ማኅበራት መሰራጨቱ፤ በከተማዋ የተፈጠረውን የዘይት እጥረት እንደሚያቃልል የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወይዘሮ ነፃነት ዳባ ገልጸዋል። በሕገወጥ መንገድ ተገኘ የተባለው ዘይት ግን በማን እንደተከማቸ የተገለጸ ነገር የለም። (ኢዛ)