ሌቱ እስኪነጋ

አንዱዓለም በቀለ - ከስዊዘርላንድ

ጆሮ አልሰማ አይል - ብዙ ጉድ ይሰማል፥

ቴዲ ታስሯል ብለው - ሲገርመኝ ሰንብቷል፥

ደግሞ አሁን ተፈታ - ብለው ይነግሩኛል፥

በቃ አሁን ይብቃ - ተዉ ዝም በሉ፥

“የሌባ ዓይነ ደረቅ” - ሆኖ እንጂ ነገሩ፥

ለኔ እንደሚገባኝ - ወዲ ነው ሚስጥሩ፥

 

እንዴት የታሰረ - ሰው አሰርኩኝ ይላል?!

እራሱን ያልፈታ - እንዴት ፈታሁ ይላል?!

ቴዲም ይገርመዋል - ይሄን አይነግረንም፥

ሀገር በእስር ሆና - ነፃ ወጣሁ አይልም።

ፍትህ በግረሙቅ - የፊጥኝ ተጠፍሮ፥

ሐቅ ገደል ገብቶ - ነፃነት ተቀብሮ፥

ነፃ ሰው ነኝ ብሎ - መች በነፃ ኖሮ፥

ከወገኑ ጋራ - ሁሌ አንጀቱ አሮ።

በልጅነት ዕድሜው - ሽማግሌ ሆኖ፥

ሲመክር ኖረ እንጂ - ፍቅር ሠላም ብሎ፥

ቢላችሁን ጣሉ - ሞፈር ያዙ ብሎ።

አንድነት እንዲሆን - መለያየት ቀርቶ፥

በዜማው አስውቦ - በቅኔ አዋዝቶ፥

እስላም ክርስቲያኑ - እንዲኖር ተስማምቶ፥

ቤቱ እንደማይጠበን - መከረ እንጂ ተግቶ፥

ላፍታ መች አረፈ - ቴዲ ተመቻችቶ?

ብርሃን እንዲሆን - ጨለማው ተገሎ፥

ከወገኑ ጋራ - ወትሮም ወህኒ ሆኖ፥

ወደ አምላክ ጮኸ እንጂ - አይነጋም ወይ ብሎ፥

ነፃ ሰው ነኝ ብሎ - ቴዲ መች ኮብልሎ!

 

እናም ወገግ እስኪል - ሌቱ እስኪነጋ፥

እስኪነጋ በጣም - ብርሃን እስኪወጣ፥

መለከት ተነፍቶ - ትንቢት እስኪፈታ፥

ወደ ምስራቅ ዞረን - እስኪሆን እፎይታ፥

አበባዬሆሽም - እስኪዜም በደስታ፥

“አሳሪ” ነኝ ባዩም - እራሱ እስኪፈታ፥

መቼ ሊዘናጋ - ቴዲ ለአንድ አፍታ፥

ድሮም አልታሰረ - ዛሬም አልተፈታ።


 

አንዱዓለም በቀለ ከስዊዘርላንድ

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ