አስፋ ጫቦ

Ato Assefa Chabo. አቶ አስፋ ጫቦ

ትዝታ ነው የሚርበን

ላናገኘው ላይጠግብን ብሏል ወዳጄ የነበረው ጸጋዬ ገብረ መድኅን

ለመሆኑት ትዝታ ምንድነው? ዘፈፍን ነው? እንጉርጉሮ? ኩርኮራ? ማላዘን?ሐሳብ ልጓም የለውምና እንዳሻው ወደላይ ወደታች፤ ወደውስጥ ወደውጭ፤ ወደፊት ወደኋላ፣ ወደየሚታይ ወደሊታይ ወደማይቻል ይሔዳል፤ ይጓዛል፤ ይተናል፤ ይበናል፤ ይመላለሳል፣ ይመለሳልም። “ማን አለኝ ከልካይ!” መሆኑ ነው።

ከዚህ ውስጥ

አንድ ጊዜ፤ አንድ ወዳጄ በፊት ከኖርኩበት፤ ከሎስ አንጀለስ (Los Angeles, California)፣ ደውሎልኝ የልጆቹን ጤነነት ጠያይቄ “አያት አድርጉህ ወይ!?” አልኩት። “እረ የለም!” አለ። ”ምነው?” ብለው “ሚስት/ባል የሚሆን አጥተው!” አለኝ። “ምነው ከዚያ ሞልቶ ከተረፈው ኢትዮጵያዊ!?” ስለው ችግሩን ነገረኝ። ”በልጅነታቸው ለማቀራረብም ሲባል ይህች/ይሔ የአጎትህ/የአክስትህ ልጅ (your nephew,your niece) ብለን አስተዋወቅን። አሁን ተጋቡ ሲባሉ “እንዴት ተደርጎ የአጎቴን የአክስቴን ልጅ (my nephew, my niece) አገባለሁ ሆነና ችግር መጣ አለኝ።

“በልጅነት የተነገር አንድ አካል አንድ አምሳል ሆኖ ያድጋልና ተለዋጭ ማስረጃ ቢኖርም /ቢታይም ተቀባይነቱውሱን ነው” አልኩት። የሰፈር የስነልቡና ሊቅ (psychiatirist) መሆኔ ነው። አሁን በምን/ለምን አስታወስኩት?

* * *

ይሔ ደግሞ በ1983 ክርምት የሆነ ነው። የዚያን ጊዜ የኢትዮጵያ የሽግግር መንግስት ምክር ቤት አባል ነበርኩ። ዘመኑን ሳስበው የጥንት ታሪክ ይመስለኛል። የሽግግር የተባለው ያኔም ዛሬም ያሳስበኛል። ድልድይ እንደመሻገር ብለን ብንወስደው ያው በድልድዩ ላይ፤ ወደምስራቅ፤ ወደጸሐይ መውጫ፤ ወደምእራብ ወደጸሐይ መጥለቂያ መሻገርም መሻገር ነው። መሆኑ ነው!!

የዚያን ጊዜ አነጋግር የነበሩ ወያኔዎች መለስን ጨምሮ በጣም ጥቂት ነበሩ። ከነዚህ አንዱ ስዬ አብርሐ ነበር። ብቻ “አውቆታለሁ” ብሎኝም ሊሆን ይችላል። ትንሽ ወንድሙ አብሮን ማእከላዊ ታች ግቢ ነበር። ጥሩ ልጅ ይመስለኛል። መእከላዊን ለማሻሻል ገንዘብ ስንሰበስብ የሰዬ ወንድምና አቶ በየነ በርኸ በጣም ተባባሪ ነበሩ። አቶበየነ በርኸ አሁን ከኛ ጋር የሉም። ማእከላዊን ሊታመን በማይችል አይነት አሻሽለነው ነበር። ተለቪዥን ሁሉ ገዝተን!!

ታዲያ ስዬን ሳየው የደቡቡ ሰው የሚመስለው ነገር አለው። ማእከላዊ በቂ ትግሬ ስለነበር የትግሬዎችን ባህርይና ስነልቡና ደህና አድርጎ ለመታዘብ እድሉ ነበረኝ። ሌላውንም እንደማደርገው ሁሉ! ከዚያ ሞዴል ስዬ ወጣ ይላልና ነው የደቡብ ሰው ይመስላል ያልኩት። የሰራው፣ የተሰራበት፣ የተሰራለት እንደተጠበቀ ሁኖ ግልጽና ጮክ ብሎ የሚናገር ነው። እንደዶርዜዎቹ!ዶርዜ ተሰብስቦ ሲነጋገር ያየ እየተጣሉ ነው ሊል ይችላል። ቋንቋውን ካላወቀው!

ስዬን ባገኘሁት ቁጥር “ይህ አዲስ አበባ፤ አራት ኪሎ ነው!” እያልኩ ትከሻው ላይ መታ መታ አድርገው ነበር። ነገሩ “ከጫካው ውጥታችህ አዲስ አበባ ገብታችኋል፣ እኔም የአራት ኪሎ ነዋሪ ነኝና ተረጋጉ” ለማለት ነበር። በቀና መነፈስ! ያንን ያሰኘኝ ጥበቃ ስር ያሉ፤ የሚጠባበቁም፤ ገልመጥ ገልመጥ ብሎ የመቃኘት ሁኔታ በሁለንተኛቸው (Body Language) ይታይ ስለነበር ነው። ታዲያ አንዱን ቀን ስዬ ጮሔብኝ “አቶ አስፋ እኛ ሰዎች ነን፣ የዱር አውሬ አይደለንም“ አለኝ። በከፊል ቢሆን አልተረዳኝምና ይቅርታ ጠየኩ። በኔ ቤት ማረጋጋቴ ነበር!

* * *

ስዬን አንድ ቀን ታምራት ላይኔ ቢሮ ውስደኝ አልኩት። ቀጥሮኝ ነበር። ወይም “ሲመችዎት ምንም ጊዜ ብቅ ይበሉ”ብሎኝ ስለነበር ይመስለኛል። ታምራት ጠቅላይ ሚኒስቴር ነበር። “አውቆታለሁ፤ የሚጽፉትንም አነባለሁ፤ ገጣሚም ነኝ …”ያለኝ ይመስለኛል። ስዬ በመኪናው ይዞኝ ሔደ። ነገሩ ከፓርላ በእግርም ቢሆን ቅርብ ነበር። የታምራት ቢሮ የሆነውን በፊት አላውቀውም። እኔ ማእከላዊ ከውረድኩ በኋላ የተሰራ ነው። ከዚህ፤ ከአቧሬ በኩል ወደፓርላማው የሚያመጣው አቀበት ላይ ነው። ከአጥሩ ታምራት ቢሪ እስኪደረስ የሆነች ርቀት ያለው አጥር ግቢ አለ። አንድ አራት አምስት የሚሆኑ፤ ጠመንጃ ያነገቡ አጥሩ በር ላይ አስወርድውን፤ ከስዬ ጋር የሆነ ነገር ተነጋገረው ፈተሹንን አለፈን። አንድ 50 ሜትር እንደሔድን እንደገና ያው ተደገመ። ሌላ 50 ሜተር ያክል እንደሔድን ያው ተደገመ። ታምራት ቢሮ እስክንደርስ ድረሰ አራቴ ይሁን አምስቴ ወርደን ተፈተሽን። ነገሩ “ዲሞክራሳዊነት”ም የሚያጣ አይመስለኝም። ስዬ፤ የመከላካያ ሚኒስትሩ፤ ግንባር ቀደም ወያኔውም ልክ እንደኔው ነበር የሆነው።

* * *

ታምራት ቢሮ ስደርስ ደግሞ ያልጠብቅኩት ገጠመኝና ደነግጥኩ። ቢሮው ውስጥ ስድስት ሰባት የሚሆኑ፣ ጠመንጃ የያየዙ በየቦታው፣ በየሶፋውና ወንበሩ ቁጭ በለው ይጨዋወታሉ። ይሳሳቃሉም!! ታምራት “ቁጭ ይበሉ!” ብሎኝ፤ የመጣሁት ለመጎብኘት እንጅ የተለየም ስለአልነበር” በል እንግዲህ ሌላ ቀን እመለሳለህ” ብዬ ወጣሁ። ገረመኝ! ወይም አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስቴርነት እንዲህ ይሆን? አልኩኝ። ልራሴ! ከዚያ ስንወጣ” ለመሆኑ ይህ ሁሉ ምንድነው?” ብዬ ስዬን ጠየኩት። ”የሜዳው ሕግ ነው። ወጥቼ፤ ተፈተሼ፤ የለቱን/የሰአቱን ምስጥራዊ ቃል(code) ካልነገርኩ አያሳለፉም፣ ወይም እያዛለሁ አለኝ። ይህ አስራራ እስከ መቸ ቆይቶ ይሆን እላለሁ።

* * *

የኬላና ፍተሻ ነገር ሲነሳ አንድ ሌላ አስታወሰኝ። ከማእከላዊ በወጣህ በወሩ እኔና ባልቤቴ፤ እህቴና ባለቤተዋ ከአንድ ሾፌር ጋር ሆነን አርባ ምንጭ ወርደን ነበር። አርባ ምንጭ ከአማሮ ኬሎ የሚመጣ ቅባታማ ቡና አለ ተባለና አንድ 20 ይሆን 30 ኪሎ ገዛን። ሻሽመኔ ላይ በ”ቡና የኮንትሮባንድ ነጋዴ!”ነት ተያዝን። ዘመነ ደርግ ነበርና ፍተሻ እንደልብ ነበር። ታዲያ ከፈተሾቹ አንዱ የኔን መታወቂያ ሲያይ “አስፋ የቡና ኮንትሮባንድ ነጋዴ አይደለም!” ያለ መስለኝ ተለቀቅን። አንድ ሰው እኔን በስምም ቢሆን ማውቁ ተነግሮናልና!

* * *

ከዚያ በወሩ ይሆን እንዲያ ወዳጄ የነበረው የሐገር ደህንነት ሚኒስትሩ፤ ኮሎኔል ተስፋዬ ወልደሥላሴ እቤቱ ራት ጋብዞኝ በጫወታ ላይ ይህንንኑ፤ የሻሸመኔውን ነገርኩት። ”አስፋ የሚገርመው ነገር ኬላው ሁሉ እንዲነሳ መመሪያ ከተላለፈ ቆይቷል። እኔ ነኝ ያስተላለፍኩት። ታዲያ ከዚህ በላይ ምን ማድረግ የቻላል?” አለኝ። ”መመሪያ ማስተላለፍና ተፈጻሚ ማድረግ ሁለት የተለያዩ ነገሮች አይመስልሁም?” አልኩትና ተሳሳቅን። በደርርግም በወያኔም ውስጥ መደማመጥ የለም/አልነበረም ልበል?

* * *

የታምራት ላይኔ ነገር ከተነሳ አንድ ነገር ልጨምር መሰለኝ። መልስ ዜናዊ እንዳለው ከሆነ “ወራዳ ሌባ!” ተብሎ፤ በዚህም ፍርድ ቤት ፍርዶበት ውህኒ ማቆ ነበር የወጣው። ስረቀ ወይም ጉቦ ተቀበለ የተባለው ገነዘብ ወደ 20 ሚሊይቶን ዶላር የሚደርስ ነበር። ታምራት ደግሞ ዛሬ የጴንጤ ሰባኪ ሆኗል። 20 ሚልዮን ያለው ነጋዴ እንጅ ሰባኪ አይሆንም የሚል ግምት አለኝ። ዘረፈ፤ ጎቦ፤ ተቀበል ወይም በማንኛቸውም ሌላ ተሰማሚ ስም ይሆን ይህንን አካበተየተባለዉን ገነዘብ መልሶ መንግስት ካዝና አዝገብቷል የሚል አልሰማሁም፤ አላነበበኩም። ለነገሩ መልስ ዜናዊ የሚለጥፈው ታርጋ ምኑ ይታመናል?

ብቻ፤ ለሁሉም ለሁሉም ታምራት ላይኔ ጠቅላይ ሚኒስትራቸው ነበር። እዚያ ውስጥ ኢትዮጵያም አለችበት። ከማርክሲዝም እስከ መጽሐፍ ቅዱስ መንገዱ ሩቅ ይመስለኛል። ፍርድ ቤት ቀርቦ ተፈርዶበታል። እዚህ ሁሉ ውስጥ እውነት የትኛው ነው? ለመሆኑ እውነት የሚባልበት ነገርስ አለ? የሚለውን ጋዜጠኞች አንፍነፈው ቢያወጡ ጥሩ ንባብ የሚሆን ይመስለኛል። የቅርብ ታሪካችን ወይም የቅርብ ጊዜ ጉዳችን መሆኑ አይደል!!

የዚህ መሳይ፤ አልፎ አልፎ ብቅ-ጥልቅ የሚሊብኝ አይጠፋምና እመለስበታለሁ።

* * *

በዛወርቅ አስፋውን እወዳለሁ። አዲሱት ትዝታዋን የበለጠ እወዳለሁ

እስላም ክርስቲያኑን እንዲህ ያዋሐደው፤

ማተቡን ከጥንት አብሮ የገመነደው ትላለች።

ኢትዮጵያ ዓመቱን ሙሉ የዓመት በዓል ሀገር ናትና መልካም የዓመት በዓል!!

አስፋ ጫቦ Dallas,Texas USA

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ