Teddy Afro- ገቢው ለምኖ አዳሪዎችን ራሳቸውን ለማስቻል ይሆናል

- የኮንሰርቱን ወጪ ስፖንሰሮች ሊሸፍኑት ይችላሉ

- አጥጋቢ ስፖንሰር ካልተገኘ የባንዶቹን ወጪ ቴዲ ይሸፍናል

- ቀሪውን አዲካ እና ኤም.ጂ. ፕሮሞሽን ይሸፍኑታል

- አበበች ጎበና ለተባለ ሀገር በቀል የበጎ አድራጎት ድርጅት እርዳታም ይሠጣል

Ethiopia Zare (ሰኞ መስከረም 18 ቀን 2002 ዓ.ም. September 28, 2009)፦ ታዋቂው ድምፃዊ አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን ከእስር ከተፈታ ለመጀመሪያ ጊዜ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጥቅምት 1 ቀን 2002 ዓ.ም. የሙዚቃ ኮንሰርት ሊያቀርብ ነው። ከዝግጅቱ መግቢያ የሚገኘው ሙሉ ገቢ በልመና ላይ ለተሰማሩ ኢትዮጵያውያን ራሳቸውን ለማስቻል እንዲሆን ፈቅዷል።

 

አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን ዛሬ መስከረም 18 ቀን 2002 ዓ.ም. “ኢንተርኮንትኔታል” በተባለው ሆቴል በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገረው፤ ወላጆቻቸውን ያጡ ሕፃናትን የሚረዱ ድርጅቶችን ለማገዝ ሁሌም ፍላጎት እንዳለውና ከእስር ከተፈታ በኋላ ይህንን ሃሳቡን አንስቶ ለጓደኞቹ ሲያካፍል እንዲህ አይነት የእርዳታ ሥራዎችን መሥራት እንደሚቻል፤ ነገር ግን የተገኘው ገቢ በሚገባ ለተባለው ተግባር እንዲውል ለማድረግ ኢትዮጵያ ውስጥ በበጎ አድራጎት ሥራ ላይ ተሰማርተው ውጤታማ ለውጥ ያሳዩ ድርጅቶችን መምረጥ እንደሚያስፈልገው መረዳቱን ተናግሯል።

 

ከመታሰሩ በፊት አበበች ጎበና ለተባለው ሕፃናት ማሳደጊያ እርዳታ ለመስጠት ቃል ገብቶ የነበረ በመሆኑ፤ ለዛ ድርጅት ከግሉ እርዳታ ለመስጠት መወሰኑን ነገር ግን ፕሮጀክት ፕሮፖዛሉን የተመለከተው ኤልሻዳይ የተባለው ድርጅት እስካሁን የሠራቸውን ሥራ ተመልክቶ የበኩሉን አስተዋጽዖ ለማበርከት መወሰኑን ተናግሯል።

 

ከተለያዩ ክልሎች ወደ አዲስ አበባ በመምጣት በልመና ሥራ ላይ የሚሰማሩ ሕፃናት በርካቶች ሲሆኑ፤ ኤልሻዳይ የተባለው ድርጅት የሚሠራው እነዚህን ሕፃናቶች ወደየመጡበት መልሶ ማቋቋም ነው። ወላጆቻቸውን ያጡ ከሆነ ደግሞ ድርጅቱ ባቋቋመው ሕፃናት ማሳደጊያ ውስጥ እንዲታቀፉ ማድረግ ነው። በዚህ ተግባሩ እስካሁን 28 ሺህ ለምኖ አዳሪዎችን ወደየክልላቸው በመመለስ እራሳቸውን እንዲችሉ ማድረጉ ታውቋል። ድርጅቱ ራሳቸውን ካስቻላቸው በኋላ ተመልሰው ወደልመና ተግባር አለመሰማራታቸውና በውጤቱ ላይ የተሠራው ጥናት እንደሚያመለክተው ድርጅቱ የሠራው ሥራ 91 በመቶ የተሳካለት ነው።

 

ድርጅቱ ባስጠናው ጥናት ከዚህ በኋላ 100 ሺህ ለምኖ አዳሪዎችን ወደ የክልላቸው መልሶ ራሳቸውን ማስቻል እንደሚገባው ያረጋገጠ በመሆኑ ከኮንሰርቱ የሚገኘው ገቢ ለዚህ ተግባር እንዲያስች ለማድረግ የታሰበ ነው።

 

ኮንሰርቱን ለማዘጋጀት የሚያስፈልገውን ወጪ በሚመለከት ሁለት ድርጅቶች ኃላፊነቱን ወስደው ስፖንሰር እንደሚፈልጉ ቃል መግባታቸውንና ባለው ጊዜ አጥጋቢ የስፖንሰር ውጤት ካልተገኘ ከአሜሪካ ለሚመጣው “አቡጊዳ ባንድ” ወጪውን አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን እንደሚሸፍን ሌሎች ወጪዎችን አዲካ ቱር እና ትራቭል እንዲሁም ኤም.ጂ. ፕሮሞሽን በጋራ እንደሚሸፍኑ አብራርቷል።

 

አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን ይህ አጋጣሚ ከአድናቂዎቹ ጋራ የሚገናኝበት መድረክ እንደሚሆንና ኢትዮጵያውያን ራሳቸው ለራሳቸው በመድረስ የሚስተካከላቸው ባለመኖሩ ሁሉም በጋራ በልመና ሥራ ለሚተዳደሩ ኢትዮጵያውያን የበኩሉን አስተዋጽዖ እንዲያበረክት ተማጽኗል።

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ