ዶ/ር ያዕቆብ ታስረው ተፈቱ

አቶ ተመስገን በደቡብ አንድ ጽ/ቤት መዘጋቱን አረጋገጡ

Ethiopia Zare (ረቡዕ ጥር 20 ቀን 2001 ዓ.ም. January 28, 2009)፦ የአንድነት ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ አባላት፣ የብሔራዊ ምክር ቤት አባላትና የሀገር ውስጥና የውጭ ሀገር ጋዜጠኞች የተገኙበት ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ ለእስር የተዳረገችበትን አንደኛ ወር በማሰብ በፓርቲው ጽ/ት ቤት የሻማና የጧፍ ማብራት ስነሥርዓት ተካሄደ።

 

የፓርቲው የህዝብ ግንኑነት ኃላፊ የሆኑት ዶ/ር ኃይሉ አርኣያ በተለይ ለኢትዮጵያ ዛሬ እንደገለጹት ከ200 በላይ ሰዎች መገኘታቸውንና ስነሥርዓቱ የፓርቲውን ሊቀመንበር ወ/ት ብርቱካንን በሚያወሱ ስነጽሑፎችና ግጥሞች የተካተተ ከመሆኑም በላይ ወቅታዊ የሆኑ ሙዚቃዎች መሰማታቸውን ገልጸዋል።

 

"ተንበርክኮ ከመኖር ቆሞ መሞት" በሚል ርዕስ ጽሑፍ የተነበበ ሲሆን፣ እውቁ ድምጻዊ ሻምበል በላይነህ ለወ/ት ብርቱካን ያበረከተው ዜማ መሰማቱና በአንዲት ድምፃዊት የተዜመ "ይነጋል" የሚል ሙዚቃም በስነሥርዓቱ ላይ የተገኙትን ሰዎች ስሜት ተቆጣጥሮ እንደነበር ሪፖርተራችን ዘግቧል።

 

የድርጅቱ መሪ በእስር ላይ ብትሆንም ፓርቲው መሪዋ ከመታሰሯ በፊት አንግቦ የተነሳውን ዓላማ ያላቋረጠ መሆኑን የሚናገሩት ዶ/ር ኃይሉ፤ በዶ/ር ያዕቆብ ኃይለማሪያም የሚመራ ቡድን በጎጃምና በጎንደር አካባቢ አዳዲስ ቢሮዎችን በመክፈትና ቀደም ብለው የተከፈቱ ቢሮዎችን የሥራ እንቅስቃሴ በመጎብኘት የጎደሉትን በማስተካከልና የተሟሉትን በማበረታታት ላይ የሚገኙ ሲሆን፣ በስድስት ወረዳዎችና በአንድ ዞን በጠቅላላ ሰባት ጽሕፈት ቤቶችን ከፍቶ እንደሚመለስ ገልጸዋል።

 

ዶ/ር ያዕቆብ ስብሰባችሁን አላሳወቃችሁም በሚል ለሰዓታት ታስረው የነበረ ሲሆን፣ በአሁኑ ሰዓት ተለቅቀው ተልዕኳቸውን በመፈጸም ላይ መሆናቸው ታውቋል።

 

በሌላ በኩል በአቶ ተመስገን የሚመራው ቡድን በሀገሪቱ አንድነት ፓርቲ በብዛት ቢሮ ወደ ከፈተበት ደቡብ ክልል በመጓዝ የሥራ እንቅስቃሴዎችን የጎበኙ ሲሆን፣ በአካባቢው የሚገኙ የድርጅቱ አባላቶችና ተመራጮች ሥራቸውን በሚገባ እየተወጡ መሆናቸውን ያረጋገጡ ሲሆን፤ በወላይታ ዞን ቦዲቲ በተባለ ቦታ የነበረው የአንድነት ቢሮ በኢህአዴግ ባለሥልጣናት ተጽዕኖ የተዘጋና የድርጅቱ ማስታወቂያ ቦርድም ከቦታው እንደተነቀለ አረጋግጠዋል።

 

በአቶ ተመስገን የሚመራው ቡድን ሥራውን አጠናቆ አዲስ አበባ የተመለሰ ሲሆን፣ ሪፖርቱን በቅርቡ ለሥራ አስፈጻሚው እንደሚያሳውቅ ለመረዳት ችለናል።

 

በተያያዘ አንድነት ፓርቲ በአዲስ አበባ የብርቱካንን እስር በመቃወም የሚጠራውን ሰልፍ አስመልክቶ የተጠየቁት ዶ/ር ኃይሉ አርኣያ ሥራ አስፈጻሚው እየተወያየበት ያለ ጉዳይ መሆኑን ገልጸዋል።

 

አዲስ ቪዲዮ

ይከተሉን!

ስለእኛ

መጻሕፍት

ቪዲዮ

ኪነ-ጥበብ

ዜና እና ፖለቲካ