የሙዚቃው ንጉሥ አስክሬን ከመስቀል አደባባይ እንዲነሳ ተወሰነ
(ልዩ ዘገባ)

- ከአስራ ስድስት ዓመት በኋላ፣ አንገቱ በታረደበት በዚያች ዕለት አረፈ - የቀብር ሥነሥርዓቱ ሐሙስ በዘጠኝ ሰዓት በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ይፈጸማል |
Ethiopia Zare (ሰኞ ሚያዝያ 12 ቀን 2001 ዓ.ም. April 20, 2009)፦ ሁሉም በአንድ ድምፅ “የሙዚቃው ንጉሥ” በማለት የሚያወድሱት የአንጋፋው ክቡር ዶክተር ጥላሁን ገሠሠ ሞት በመላው ዓለም የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን አሳዝኗል። ቤተሰቦቹ፣ ዘመድ ወዳጆቹ፣ የሞያ አጋሮቹ፣ ታዋቂ ኢትዮጵያውያንና አድናቂዎቹ በቤቱ እየተገኙ ኀዘናቸውን እየገጹ ነው።
የሙዚቃው ንጉሥ የክቡር ዶክተር አርቲስት ጥላሁን ገሠሠን የቀብር ሥነሥርዓት ለማከናወን አንድ ኮሚቴ የተቋቋመ ሲሆን፣ ኮሚቴው ዛሬ ከሰዓት በኋላ ተሰብስቦ በወሰነው መሰረት፤ የቀብር ሥነሥርዓቱ ሐሙስ በዘጠኝ ሰዓት በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ቤተ ክርስቲያን ይፈጸማል።
ከረቡዕ ጀምሮም የሙዚቃ ሥራውን በጀመረበት ሀገር ፍቅር ትያትር ቤት ቀደም ሲል “ጥላሁን ገሠሠ ‹ሀ›” በሚል ቅርጽ የተጻፈበት የሱ ኮርነር ላይ አድናቂዎቹ ኀዘናቸውን የሚገልጹበት የኀዘን መዝገብ፣ ሻማ ማብሪያ፣ የአበባ ጉንጉን ማስቀመጫ እንደሚዘጋጅና ሁሉም ሰው ወደዚያ ቦታ ሄዶ ኀዘኑን እንዲገልጽ ከኮሚቴው ጥሪ ቀርቧል። አስክሬኑም ከሀገር ፍቅር ትያትር ቤት እንዲወጣና የቀብር ሥነሥርዓቱ ወደሚፈፀምበት ወደቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ቤተክርስቲያን እንዲወሰድ ታስቦ ነበር።
የተቋቋመው ይሄው ኮሚቴ ሃሳቡን በመቀየር፣ አስከሬኑ ከመስቀል አደባባይ (አብዮት አደባባይ) ተነስቶ በማርሽ ታጅቦ ወደ ቀብሩ ቦታ እንዲያመራ ዛሬ ማምሻውን ውሳኔ ላይ መድረሱን ምንጮች ገልፀዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ለክቡር ዶ/ር አርቲስት ጥላሁን ገሠሠ ቤተሰቦች የኀዘን መግለጫ በደብዳቤ መላካቸው ታውቋል። በዚሁ የኀዘን መግለጫ ደብዳቤ ላይ “ሀገሪቱ ከምትኮራባቸው ስመ-ጥር ሰዎች አንዱን አጥታለች፤ … ለአርቲስቱ ቤተሰቦችና ዘመዶች መጽናናትን እመኛለሁ! …” በማለት ፊርማቸውን አስፍረው መላካቸው ታውቋል።
ከዚህም ሌላ ከሀገሪቱ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ውስጥ አቶ በረከት ስምዖን እና አቶ አዲሱ ለገሠ የአርቲስቱ ቤተሰቦች ጋር ለቅሶ ደርሰዋል። ኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ አርቲስቶች ቦሌ አካባቢ የሚገኘው የአርቲስ ጥላሁን ቤት ድረስ በመሄድ ለቤተሰቦቹ ኀዘናቸውን የገለጹና መጽናናትን ተመኝተዋል። ከእነዚህም ውስጥ ንዋይ ደበበ፣ አያሌው መስፍን፣ አለማየሁ እሸቴ፣ አብራር አብዶ፣ አስቴር አወቀ፣ … ይገኙበታል።
የኢትዮጵያ ዛሬ ምንጮች እንደገለጹት ከሆን ሼህ መሐመድ አል አሙዲንም ለቅሶ የደረሱ ሲሆን፣ ለቀብር ሥነሥርዓቱ ማስፈፀሚያ በሚል ለሙዚቃው ንጉሥ የቀብር ሥነሥርዓት ለማከናወን ለተቋቋመው ኮሚቴ 200 ሺህ ብር ሰጥተዋል። እንደ ምንጮቻችን ገለፃ ከሆነ ሼህ አል አሙዲን “የቀብር ሥነሥርዓቱ በጥሩ ሁኔታ ይፈጸም” በሚል ገንዘቡን ለግሰዋለው።
“አውሮፕላን መጣ እየገሰገሰ፣
በዘፈን አንደኛ ጥላሁን ገሠሠ”
“አውሮፕላን መጣ እየገሰገሰ፣ በዘፈን አንደኛ ጥላሁን ገሠሠ” ይቺን ግጥም አንድም ኢትዮጵያዊ አይረሳትም። ሕፃንት ሁሉ ለኢትዮጵያዊው ንጉሥ ጥላሁን ገሠሠ የሚሏት ነበረች።
የሙዚቃው ንጉሥ ከአስራ ስምንት ወራት በፊት ነበር ከባለቤቱ ወ/ሮ ሮማን ጋር ወደ አሜሪካ ያቀናው፤ “አንድ ዓመት ከስድስት ወር እዛ ስንቆይ ጤነኛ በመሆኑ አንድም ቀን ሆስፒታል ወስጀው አላውቅም ነበር። ነገር ግን ወደ ኢትዮጵያ የመመለስ ከፍተኛ ጉጉት ነበረው። ከዛም የፋሲካን በዓል ኢትዮጵያ ሄደን እንድናሳልፍ ጠየቀኝ። ትናንት የፋሲካ ዕለት አመሻሽ ላይ 2 ሰዓት ከ40 ላይ ወደ ኢትዮጵያ መጣን። በዓሉን እቤት በጥሩ ሁኔታ አሳለፍን። እራት በልተን ስንጫወት ቆየን፤ ከሌሊቱ ስድስት ሰዓት ላይ ግን በድንገት በላብ ተጠመቀና ‘የልቤ አመታቱ ትክክል አይደለም፤ ልቤን ያዥልኝ’ አለኝ።
“አንዳንዴ እንደዚህ ስለሚያደርገው ክፉ ነገር ይመጣል ብለን አልገመትንም። በጣም ሲንዘፈዘፍ ወደ ቤተዛታ ሆስፒታል ይዤው ሄድኩ። ቤተዛታ ሆስፒታል አዩትና ‘የልብ ሕክምና እኛ አንሰጥም’ ብለው ጎተራ ወደሚገኘው “ቦሌ ኢንተርናሽናል የልብ ሕክምና” እንድወስደው ጠቆሙኝ። እኔ ከኢትዮጵያ ከወጣሁ ዓመት ከስድስት ወር ስላለፈኝና መንገዱ እየተሠራ ስለነበር መንገዱ ስለጠፋኝ በአቅራቢያዬ ወዳገኘሁት “ሰናይ” ወደ ተባለ ክንሊክ ይዤው ገባሁ። ‘እባካችሁ እርዱኝ ጥላሁን ገሠሠ ነው’ እያልኩ ጮህኩ፤ ነገር ግን አልተረፈልኝም። ሕይወቱ ሌሊት ላይ አለፈ” ሲሉ ወ/ሮ ሮማን የባለቤታቸውን የአንጋፋውን ድምፃዊ አሟሟት ያወሱት።
አንጋፋው ድምፃዊ ክቡር ዶክተር ጥላሁን ገሠሠ ከእናቱ ወ/ሮ ጉቴ ጉርሙ እና ከአባቱ አቶ ገሠሠ ንጉሴ መስከረም 17 ቀን 1933 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ከተማ ተወለደ። የስድስት ወር ልጅ እያለ ቤተሰቦቹ ወደ ወሊሶ ይዘውት ሄዱ።
የአስራ አራት ዓመት ልጅ እያለ አያቱ እዛው ወሊሶ አስቀሩት። እናም ወሊሶ ከተማ በሚገኘው “ራስ ጎበና የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት” መማር ጀመረ ከሱዳናዊው አስተማሪው ጋር ስለሙዚቃ ፍላጎቱ ሲወያይ ወደሱዳን እንዲያቀና እንዲሞክር ቢመክረውም ጥላሁን እሱን ሳይቀበል ሌላ አንድ ዕድል ገጠመው። አርቲስት ንጋቷ ከልካይ፣ ኢዩኤል ዩሐንስ እና ሌሎች አርቲስቶች ከሀገር ፍቅር ትያትር ቤት እሱ ወደሚማርበት ትምህርት ቤት ሥራዎቻቸውን ለማሳየት ሄደው እዛው አገኛቸው። እናም ስለሙዚቃ ፍላጎቱ አወራቸውና እንዲዘፍን ጠየቃቸው። በዛን ወቅት እንዲዘፍን ባይፈቅዱለትም፤ ነገር ግን ወደ አዲስ አበባ እንዲመጣ ሞያውን እንዲለማመድ ገልጸውለት ተመለሱ።
በዚህ ንግግር ልቡ የተንጠለጠለው ጥላሁን ገሠሠ ከአያቱ እውቅና ውጭ ጠፍቶ በእግሩ ጉዞ ወደ አዲስ አበባ ጀመረ። አስራ አምስት ኪሎ ሜትር ተጉዞ “ቱሉ ቦሎ” የተባለች ከተማም ሲደርስ አክስቱ ጋር አረፍ አለ። ይህን የሰሙት አያቱ አስይዘው በማግስቱ ወደ ወሊሶ አስመለሱት። ጥላሁን ግን ከዛች ቀን በኋላ አያቱ ቤት የቆየው አንዲት ምሽት ብቻ ነበር። የጠራችው ጥበብ ጥሪዋን አላቆመችምና የአያቱን ቁጣ አሻፈረንኝ ብሎ ጠፍቶ አዲስ አበባ ገባ።
ጥበብ አላሳፈረችውምና በአስራ አራት ዓመቱ ሀገር ፍቅር መድረክ ላይ ቆሞ በወቅቱ የዕድሜ እኩያው ከነበረው ከድምፃዊ ፍሬው ኃይሉ ጋር “ኢትዮጵያ ሀገሬ” የሚለውን ዘፈን ለመጀመሪያ ጊዜ ዘፈነ። ያኔ ሁሉም በእጆቻቸው አጨበጨቡለት ከፍተኛ አድናቆትንም አተረፈ። ከአራት ዓመት የሀገር ፍቅር ቆይታው በኋላ የክቡር ዘበኛ ባንድን ተቀላቀለና “ኮከብ ድምፃዊ” የሚል ስያሜን አገኘ። ጥላሁን ገሠሠ በ1954 ዓ.ም. መፈንቅለ መንግሥት በተደረገበት ወቅትም በዘፈነው ዘፈን እስር ቤትም ገብቶ ነበር።
ከክቡር ዘበኛ በኋላ ወደ ብሔራዊ ትያትር ያቀናው ጥላሁን ገሠሠ፤ ታዋቂነቱ ወደር አልነበረውም። በወቅቱ የነበሩ ጋዜጦች “ጥላሁንን የሚተካ ድምፃዊ የሚፈጠር አይመስለንም” ሲሉ አወድሰውት ነበር። ጡረታ እስከወጣበት ድረስ በትያትር ቤቱ አገልግሏል። አርቲስት ጥላሁን ገሠሠ ከሀገር ፍቅር፣ ከብሔራዊ ትያትር ኦርኬስትራ እና ከክቡር ዘበኛ ባንዶች በተጨማሪ በዋሊያስ፣ ሮሃ፣ ዳዲሞስ፣ ኤይቤክስ ከተባሉና ከሌሎች ባንዶች ጋር ላለፉት 50 ዓመታት የሙዚቃ ሥራዎቹን ለኢትዮጵያ ህዝብ አቅርቧል።
ለዚህ ውለታውም የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የክብር ዶክትሬት ሲሰጠው የኢትዮጵያ የሥነ ጥበባትና የመገናኛ ብዙሃን የሽልማት ድርጅት “የሙሉ ዘመን” የሚል የክብር ሽልማት አበርክቶለታል።
ጥላሁን ገሠሠ የኢትዮጵያ ሙዚቃ በሸክላ መታተም ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ የሙዚቃ ሥራዎቹን ለአድማጭ ጆሮ ሲያደርስ የነበረ ሲሆን፣ በቅርቡም አዲስ ካሴት ለማውጣት ከሙዚቃ አቀናባሪው ከአበጋዙ ክብረወርቅ ሺፈታ ጋር እየሠራ እንደነበርና፤ ለአዲሱ የካሴት ሥራም እንዲያጠና ዜማና ግጥም አሜሪካን ሀገር አድርሶለት መምጣቱን በቀጣይም የመጨረሻ ቀረጻ ሊያደርጉ ቀጠሮ ይዘው እንደነበር የሙዚቃ አቀናባሪው አበጋዙ ተናግሯል።
አንጋፋው ድምፃዊ ክቡር ዶክተር ጥላሁን ገሠሠ የዛሬ አስራ ስድስት ዓመት ልክ የፋሲካ ዕለት ነበር ባልታወቁ ሰዎች አንገቱ የታረደው። እናም በማግስቱ ወደ ለንደን አቅንቶ ሕክምና ተደርጎለት አስራ ስድስት ዓመታትን በሕይወት የቆየው። አርቲስት ጥላሁን በስኳር ሕመም ምክንያት አንድ እግሩን አጥቶ የነበረና በልብ ሕመም ይሰቃይ የነበረ ሲሆን፣ ለሁለቱም ሕመሞቹ በሕክምና ሲረዳ ቆይቶ ከአስራ ስድስት ዓመት በኋላ - አንገቱ በታረደበት በዚያች ዕለት በልብ ሕመም ምክንያት ይችን ዓለም ለዘለዓለሙ ተሰናበተ።
የኢትዮጵያ ዛሬ ዝግጅት ክፍልም የኢትዮጵያውን የሙዚቃው ንጉሥ ክቡር ዶክተር አርቲስት ጥላሁን ገሠሠን ነፍስ እግዚያብሔር በገነት እንዲያኖር እየተመኘ፤ ለቤተሰቦቹና ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ መጽናናትን ይመኛል።