የኢትዮጵያ ሶሺዮ ፖለቲካ ጉዞ፣ ተግዳሮቶቹና የመፍትሄ ሃሳብ
ገለታው ዘለቀ

ዴሞክራሲያዊ ተቋማትን ለመገንባት ምቹ የሆነ የሶሺዩ ፖለቲካ ሥርዓት ወደ መፍጠር
(ለአራተኛው የቪዥን ኢትዮጵያ ኮንፈረንስ የቀረበ ጽሁፍ)
የሰው ልጅ ማኅበራዊና ግላዊ ተፈጥሮ ስላለው ለማኅበራዊ ኑሮውና ለግላዊ ኑሮው የተለያዩ ጠገጎችን እያበጀ ይኖራል። እነዚህ የሚሰራቸው ጠገጎች ለግል ሕይወቱም ሆነ ለማኅበራዊ ሕይወቱ ወሳኝ ናቸው። ሰው የዚህን ዓለም ኑሮውን ለመግፋት ከሚያስችሉት መሳሪያዎች አንዱ እነዚህ ጠገጎቹ ናቸው።
የሰው ልጅ በሕይወቱ የሚፈጥራቸው እነዚህ ጠገጎች ሃይማኖታዊ ወይም ባህላዊ ወይም ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ትርፍ ያስገኙለታል። ታዲያ ይህ የሰው ልጅ በዓለም ላይ ከሚፈጥራቸው ጠገጎች መሃል ከፍተኛውና ጠንካራው አገር የሚባለው ጠገጉ ነው። በርግጥ ከዚህ አልፎ ዛሬ ጊዜ ሌላ ከፍ ያለ የጋራ የዓለም ጠገግ ሕዝቦች አበጅተው ስያሜውን ደግሞ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ብለውታል። ነገር ግን የሰው ልጅ ከቀን ተቀን ሕይወቱ ጋር በጣም የተሳሰረው ጠገግ አገር ሲሆን ለዚህ ጠገግ የተለያዩ ስምምነቶችን አስፍሮ በዚህ ጥግ ስር ይኖራል። አገር የሚባለው ጠገግ ጠባብ አይደለም። የሰው ልጅ በዚህ ጠገግ ስር ብዙ መለስተኛ ጠገጎችን ሊፈጥር ይችላል። ለምሳሌ የባህል የሃይማኖት ወይም ሌላ ዓላማ ያለውን ጠገግ በዚህ ሰፊ ጠገግ ውስጥ ሊሰራ ይችላል።
አገር የሚባለው ጠገግ እነዚህን ሁሉ አቅፎ መያዝ የሚችል ሰፊ አዳራሽና ከፍ ያለ ጠገግ ነው። እንደ ብሔር የሃይማኖት ስብስብ ያሉ ጠገጎች በተፈጥሯቸው ልዩነትን በውስጣቸው አይዙም። ልዩ ልዩ ቡድኖችን አቅፎ በውስጣቸው ለማስኖር የሚያስችል ተፈጥሮ የላቸውም። ከነዚህ ስብስቦች ከቡድናቸው ስምምነት ወይም ደንብ ውጭ የሆነ ቡድን ቢመጣ በውስጣቸው ያለ ቅራኔ ሊኖር አይችልም። በመሆኑም ነው አገር የሚባለው መዋቅር ከነዚህ የቡድን ጥጋጥጎች ተላቆ ሁሉን ማቀፍ የሚችል ጠገግ ሆኖ በዘመናዊቷ ዓለም የተሰራው።